Quantcast
Channel: Ethiopian News | ዘ-ሐበሻ | Latest News Provider | News For All
Viewing all articles
Browse latest Browse all 15006

ኃይሌ ገብረሥላሴ የተቃርኖ – የስኬትና የውድቀት – ምልክት ሲሆን (በሀገሬ ክብሬ)

$
0
0

በሀገሬ ክብሬ

44በሀገራችን እርምጃው የሚያፈጥነው ሰው “እገረ ቀሊል” ይባላል። ይሄ የበርካታ ክብረወሰን ባለቤት ለሆነው የሩጫው ጀግና ኃይሌ ቢያንሰው እንጂ አይበዛበትም። ክፋቱ ግን እግዜሩ ሀይሌን ሲያድለውና ሲበድለው በእግሩ ሮጦ ለሚያገኘው ድል ሲከበርና ሲወደድ ከጭንቅላቱ የሚፈልቀው ሀሳብ አስተዋይነትና ጨዋነት ማጣቱ በኢትዮጵያና ዛሬ በአለም ህዝብ ፊት ቀላል ሰው አደረገው። “ቀሊል (ቀላል)” የሚለው አባባል ለእግሩም ለማሰብ አቅሙም መገለጫ መሆኑ ያሳዝናል።

ሀይሌ ስለህይወቱ ሲተርክ እንደሰማነው በልጅነቱ ያስሮጠው ምክንያት እንደ አብዛኛው ህዝባችን የሱም ቤተሰቦች የነበራቸው የነገን የማሰብ ሀብትና የነበረባቸው የገንዘብ ድህነት ነበር። አስተዋይ ባይሆኑ ትምህርትቤት አይልኩትም ነበር። የገንዘብ ደሀ ያባይሆኑ ደግሞ እንደየዛሬ ጓደኞቹ ዘራፊ ወያኔ ልጆች የግል አዳሪ ትምህርትቤት ይላክ ነበር ወይንም ሞግዚት ምሳና ደብተሩን ተሸክሞለት በሹፌር ከቤት ትምህርትቤት በተመላለሰ። ድህነት ረዳውና ያቺ ወደትምህርትቤት ሲሮጥ ደብተሩን ያቅፋበት የነበረችውን እጅ ቆልመም አድርጎ በመሮጥ ድህነትን እንደበቆሎ እሸት ገለባ ከላዩላይ ገሽልጦ በመጣል ተፈትልኮ አመለጣት። እሰየው የሚያስብል ነበር ይሄ ስኬቱ ጥጋብና ማናለብኝ ባይነት የአመለካከቱን ኋላቀርነት አደባባይ ለማውጣት ድፍረቱን ባያበዛበት።

ታድያ ይሀው ዛሬ በፊልም አስቀርጾ ያሳየን እኔም እንደተቀረው ወገኔ በችግርነው ያደኩት የሚለው ትረካ ተረሳና ሸገር ከፍ ያለ መሬት ላይ ቪላ ሰርቶ ከህዝብ የሚቀማ መሬት  ላይ ሀብት እያካበተ በህዝቡ መከራ እያላገጠ ቀን ይገፋል።  ይኖራል ማለቱ ይከብደኛል ምክንያቱም አጠገቡ በረሀብ የሚረፈረፈውና በፍትህ እጦት የሚሰቃየው ህዝብ መከራ የማይከነክነው ፍጡር “ኖረ” ማለት ቀርቶ ሰውም ነው ማለቱ ይከብዳል።

ችግሩ ኃይሌ መበልፀጉ አይደለም። እንኳን እሱ ብዙ ጊዜ ባንዲራችን በዓለም ላይ ከፍ ብሎ እንዲውለበለብ ያደረገና ለሀብቱ መነሻው የራሱ ጥረት የሆነ ኢትዮጵያዊ ቀርቶ ሀገራችንን ከማጥፋትና ባንዲራችንን ከማዋረድ የተለየ ነገር በህይወታቸው አንድም ቀን ሊያደርጉት ቀርቶ ሊያልሙትም የማይቻላቸው በርካታ የወያኔ ማፈሪያዎችስ በህዝባችን ጫንቃ ላይ በልፅገው የለ? ሀይሌ የግፉ ተባባሪና የግፈኞቹ ጠበቃ ለመሆን ከአፉ ቀደም ቀደም ማለትን አለቅጥ ማብዛቱ ነው የሚያሳዝነው።

“የማያድግ ልጅ ሽቀብ ይቀ..ል” እንደሚባለው ኃይሌ ዛሬ አፋፍ ላይ ካለው ቪላ ቤቱ መናፈሻ ውስጥ እየተንጎራደደና ህዝባችንን ቁልቁል እያየ “ስንጠግብ እጃችንን ጠረግ ጠረግ ያደርግንበትን የሼራተን ትርፍራፊ በጉርሻ መልክ እየገዛህ ረሀብህን ማስታገስ ከቻልክ መቼ አነሰህ? ዲሞክራሲስ ላንተ ምንህ ነው” እያለ በኢትዮጵያውያን ላይ ብቻ ሳይሆን በመላው አፍሪካውያን ላይ ማላገጥን እንደ አስተዋይነት ቆጠሮት ይህን ሰንካላ አስተሳሰብ (ማሰብ ከተባለ) አደባባይ ይዞት ወጣ። እንዴት ነው ጋዜጠኛው እንኳን ይታዘበኛል የማይለው? ከኛዋ ኢትዮጵያ እጅግ በጣም የተሻለ የዲሞክራሲ ስርዓት ያለበት ሀገር ያሉት ጓደኞቹስ ምን ይሉኛል እንኳን አይልም?

ኃይሌ ቀደም ሲል በ”ከማን አንሼ” አስተሳሰብ በዘመነ ወያኔ የደንቆሮ መፈንጫ የሆነችው ኢትዮጵያ መሪ መሆን እፈልጋለሁ እችላለሁም እንዳለው ነገ ለተባበሩት መንግስታት መሪም ልሁን ይል ይሆናል። እንዳለውም ከመቶ ሀገር በላይ መሂዱና ሮጦ መመለሱ አለምን አውቃለሁና ለአለም መሪነት የሚያበቃ እውቀትና ብቃትም ተጎናፅፈያለሁ ይልም ይሆናል። ሲያልቅ አያምር እንዲሉ።

የኃይሌ ባህሪይ እናቴ በልጅነት ዘመኔ የነገረችኝን ምሳሌ አስታወሰኝ። አንዱ አርሶአደር የሽምብራ ማሳው ውስጥ እንቅስቃሴ ያይና ዝንጀሮ መስሎት ለማባረር ሲሄድ አንዱ ሰውዬ የሽምብራ እሸቱን እየዘነጠለ ከነገለባው ሲቅም ያየዋል። አርሶአደሩም የተራበ ሰው አላስደንግጥም ብሎ በትዕግስት ከርቀት ማየቱን ቀጠለ። እንደዝንጀሮ የሰው ማሳ የወረረው ሰውዬም ረሀቡ ጋብ ሲልለት ሽምብራውን ከነውጪ ገለባው መቃሙን አቁሞ እየጠረጠር ከበላ በኋላ በመጨረሻ የእያንዳንዱን ሽንብራ ስስ ቆዳ ሳይቀር እየላጠ ማላመጡን ቀጠለ። በዚህ ያልተደሰተው ባለማሳውም ሰውዬውን ጠጋ ብሎት “እንደ መጀመሪያውም አይደል አንደመጨረሻው እንደመሀከለኛው ብላ” አለው። ሀይሌም እንደዱሮው የነጣ ድህነቱ ጊዜ ሳይሆን አንደዛሬም የሱ የቀድሞ ጎረቤቶችና ዘመዶች ሳይቀሩ መሬታቸውን እየተቀሙ ለስደትኝነት፣ ለለማኝነትና፣ እስር ሲዳረጉ ይህን አልሰማሁም አላየሁም ቢሆንስ ምናለበት አፍሪካ ነው ያለነው እያለ ማላግጡን አቁሞ በህዝብ ዘንድ ያለውን የተሟጠጠ ክብርና ፍቅር ጭራሹን ሳያጣ ሞቴንና ታሪኬን ያሳምረው ብሎ ህልፈት ህይወቱን ቢጠብቅ ይሻለዋል። እምብዛም ጥጋብና የህዝብ ንቀት ለመለስ ዜናዊም አልበጀው። ከህዝቡ የዘረፈውን በቢሊየን የሚቆጠር ብር ሳይበላው “አረመኔ ጨቋኝ” ተብሎ በአደባባይ በመዘለፉ ደንግጦ ሞቷል። ለመለስ ሞት አደባባይ የታየው የውሸት ለቅሶ ትዕይንት የፍቅር መገለጫ ነው ብሎ እራሱን ካላሞኘ ከአሁን ባህሪው ካልታረመ የሱም እጣፋንታ በሆዱ “እንኳን ወሰደው” በአፉ “ውይ ኃይልዬ ተቀጨ” የሚል ለቀስተኛ አስክሬኑን በፌዝ ለቅሶ አጅቦ እንደሚሸኘው አይዘንጋ።

ለሱም አደብ ግዛ የሚል መካሪ ይስጠው።  እኛም ከማሰብ አቅሙ በላይ እንዲያስብ እየጠበቅን የብቃቱን ውስኑነት ባሳየን ቁጥር መበሳጨቱ ይብቃን። ፈረንጅኛውን እንደተማረው የሰውልጅ በዳቦ ብቻ አይኖርም የሚልውንም ሀሳብ ከራሱ ጋር እንዲያዋህድ ሁሉን አውቃለሁ ከሚያሰኝ አባዜም አጽድቶ ትንሽ የማንበብና አዋቂዎች የሚሉትን የመስማት ትእግስትና ብልህነት ይስጠው።  አሜን!

 

The post ኃይሌ ገብረሥላሴ የተቃርኖ – የስኬትና የውድቀት – ምልክት ሲሆን (በሀገሬ ክብሬ) appeared first on Zehabesha Amharic.


Viewing all articles
Browse latest Browse all 15006

Trending Articles



<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>