“እርጎዬዎች” በመባል በሚታወቁትና በአንድ ወቅት በኢትዮጵያ ሙዚቃ ውስጥ ገናና ከነበሩት 5 እህትማማች ድምጻውያን መካከል አንዷ የነበረችው ድምጻዊት እናና ዱባለ ከዚህ ዓለም በሕይወት መለየቷ ተዘገበ። በ1971 ከእናቷ ወ/ሮ እርጎዬ ጸጋውና ከአባቷ ዱባለ ታርፋለህ በጎንደር አዘዞ እንደተወለደች የሕይወት ታሪኳ የሚያስረዳው ድምጻዊት እናና “ጭር ሲል አልወድም” በሚለው ዘፈኗ ትታወቃለች።
አራት ኪሎ ወደ ካሳንቺስ መውረጃ አካባቢ እርጎዬዎች በሚለው አዝማሪ ቤት ከቤተሰቦቿ ጋር በመሆን ስታገልግል እንደቆየች የሚነገርላት ድምጻዊት እናና በ8 ዓመቷ ከጎንደር ወደ አዲስ አበባ ሙዚቃ እንዳሰደዳት የሕይወት ታሪኳ ይናገራል።
የሙዚቃ አልበም በ1982 ዓ.ም “አምስቱ እርጎዬዎች” በሚል ከቤተሰቦቿ ጋር በማውጣት ወደ ሙዚቃው ሕይወት ጠልቃ የገባቸው እናና ከእህቶቿ ጋር ሶስት፣ ለብቻዋ ሁለት ሙሉ ካሴት ያሳተመች ሲሆን ከድምጻዊ አበበ ፈቃደ ጋር በሁለት የሙዚቃ ስብስቦች በቅብብሎሽ ያቀረበቻቸው ዜማዎቿ በሕዝብ ዘንድ ተወዳጅ እንደሆኑላት የሙዚቃ ሰዎች ለዘ-ሐበሻ ይገልጻሉ።
የዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች እንደሚሉት እናና ዱባለ አዲስ የሙዚቃ አልበም ለማውጣት በዝግጅት ላይ የነበረች ቢሆንም በድንገተኛ ህመም አዲስ አበባ ቤተዛታ ሆስፒታል ገብታ ህክምና ስትረዳ የቆየች ቢሆንም ይህችን አለም ተሰናብታለች።
በድምጻዊቷ እረፍት የተነሳ ዘ-ሐበሻ የተሰማትን ሐዘን እየገለጸች ለቤተሰቦቿና ለአድናቂዎቿ መጽናናትን ትመኛለች።