Quantcast
Channel: Ethiopian News | ዘ-ሐበሻ | Latest News Provider | News For All
Viewing all 15006 articles
Browse latest View live

በመቀሌ የባጃጅ ሹፌሮች የሥራ ማቆም አድማ መቱ

0
0

mekele
(ዘ-ሐበሻ) በመቀሌ ከተማ የወጣውን አዲስ የባጃጅ ሕግ በመቃወም ሹፌሮች ከዛሬ ማርች 23, 2016 ጀምሮ የሥራ ማቆም አድማ መምታታቸው ተሰማ::

ከመቀሌ ለዘ-ሐበሻ የደረሱ መረጃዎች እንደጠቆሙት ሹፌሮቹን ለሥራ ማቆም አድማ መምታት ምክንያት የሆናቸው ምክንያት “እንደሚኒባስ ታክሲዎች ታፔላ አበጅታችሁ በስምሪት ብቻ መሥራት አለባችሁ” የሚለው አዲስ ህግ ከወጣ በኋላ ነው::

በመቀሌ ከተማ ከ2500 በላይ ባጃጆች አሉ ተብሎ የሚገመት ሲሆን እነዚህ ሁሉ ዛሬ ሥራ በማቆማቸው ከተማዋ ጭር ብላ እንደዋለች ለዘ-ሐበሻ የደረሰው መረጃ አስታውቋል;:

The post በመቀሌ የባጃጅ ሹፌሮች የሥራ ማቆም አድማ መቱ appeared first on Zehabesha Amharic.


ዘሐበሻ ጋዜጣ ቁጥር 83 |ለዓለም አቀፍ አንባቢዎች በPDF የቀረበ

Health: ያለክኒን በቤትዎ ሊያድኗቸው የሚችሉ 5 የጤና ችግሮች

0
0

ከኢሳያስ ከበደ

የአያትና እናቶቻችን የቤት ውስጥ ህክምና የምናደንቅና የምንጠቀም ሰዎች ሳይንሳዊ መሰረቱን ስንጠራጠር ኖረን ይሆናል፡፡ በቅርቡ የወጡት የጥናት ውጤቶች ግን ግዴላችሁም አታስቡ፣ የእናቶቻችሁ የቤት ውስጥ ቀላል ባህላዊ መፍትሄዎች በጥናት ድጋፍ አግኝተዋል፣ ክኒኖችን ከመውሰዱም ያድናችኋል የሚል ምክርን እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ ከሳል ሽሮፕ የሚሻል ሌላ አማራጭ፣ ለጀርባ ህመም፣ ለድብታ፣ ለማይቆም ራስ ምታት፣ ለሆድ ድርቀት፣ የእንቅልፍ እጦትንና ሌሎችንም ዘመናዊ መድሃኒት ለሚፈልጉ ችግሮች ተፈጥሯዊ ፈውሶችን ለማግኘት ትችላላችሁ ይላሉ ጥናቶቹ፡፡ የተወሰኑትን ተመልክተናቸዋል፡፡
home
– ከሳል ሽሮፕ ማር ሲመረጥ

– ክኒን የተመረጠው የጀርባ ህመም መፍት

– ራስ ምታት አልቆም ብለዎታል? የተፈጥሮ መፍት አለው.::- ድብርትዎ ማስለቀቂያው የፀረ ድብርት መድሃኒት አይደለም

– የሆድ ድርቀት ያለመድሃኒት

ከሳል ሽሮፕ ማር ሲመረጥ

ማር ከማስቀመጫው አውጥተን ወደ ዳቦ መቀባት ስንፈልግ ከዕቃው ዘለግለግ ብሎ ለመውረድ ምን ያህል ጊዜ እንደሚፈጅበት አስተውላችኋል? ረዘም ያለ ጊዜ ይፈጃል፡፡ ይህ ወፍራም ፈሳሽ ይህ ተፈጥሮው ከሳል ሽሮፖች የበለጠ አስመርጦታል፡፡ የሁለቱም ስራ አንድ ነው፡፡ ሁለቱም ጉሮሮን በመሸፈን የዚያ አካባቢ ህዋሳት እንዳይቆጡ ያደርጋሉ፡፡

አርካይቭስ ኦፍ ፔዲያትሪክስ ኤንድ አዶለሰንት ሜዲስን የተሰኘው የምርምር መጽሔት አንድ ማንኪያ ማር እና ለሳል የሚወሰደውን ዴክትሮሜቴርፋንን ሲያወዳድሩ ማር ከሽሮፑ የተሻለ ሳልን የመግታት አቅም እንዳለው መረጋገጡን አስፍሯል፡፡ በፔንሲልቫኒያ ዩኒቨርሲቲ በህፃናት ላይ በተደረጉ ጥናት ይህ ውጤት መገኘቱ የገለፁት የጥናቱ መሪ ዶ/ር አያን ፖል በአዋቂዎችም ውጤቱ ተመሳሳይ ይሆናል ብለዋል፡፡ የሽሮፑ መድሃኒት ራስን የመክበድ የጎንዮሽ ጉዳት ስላለው ለምን ሳልዎት በማር አያስታግሱም ይላሉ ፕሮፌሰሩ፡፡ ታዲያ ማር ሁሉ እኩል አይደለም፡፡ ጠቆር ያለው ማር ከነጩ ይልቅ የተሻለ ብዙ ፀረ መርዛማ ኬሚካሎች /አንቲኦክሲዳንትስ/ ስላሉት ጠቆር ያለውን ይምረጡ፡፡ ከመኝታ በፊት ሁለት ማንኪያ ማርዎትን ይውሰዱ፣ ለውጡን ያዩታል ብለዋል ባለሙያዎቹ፡፡

ከክኒን የተመረጠው የጀርባ ህመም መፍትሄ

እጅግ አስጨናቂ የሚባል ህመም ከሚያስከትሉ ህመሞች መካከል የጀርባ ህመም አንዱ ነው፡፡ አንዳንዶቻችን ህመሙ ሲሰማን ክንዶቻችንን በመወጠርና ሰውነታችንን በማፍታታት መጠነኛ እረፍት ለማግኘት እንሞክራለን፡፡ ጥረቱ አይከፋም፣ የሳይንስ መሰረትም አለው ያ ባለሙያዎች ለታችኛው የጀርባ ክፍል ህመም ዮጋ ፍቱን ነው ብለዋል፡፡ ዮጋ የጀርባ ህመምን ለማስታገስ ተብለው የሚወሰዱ እንደ አይቡፕሮፊንና አስፕሪን መድሃኒቶ ለማራቅ ይበጃል ባይ ናቸው፡፡ እነዚህ መድሃኒቶች በጉበት ላይ ከፍተኛ ጉዳት የማስከተል የጎንዮሽ ጉዳት ስላላቸው ዮጋ በመፍትሄነት መምጣቱ ከብዙ ሃሳብ እንደሚጠብቅ አናልስ ኦፍ ኢንተርናል ሜዲስን የተሰኘው የጥናት መጽሔት ላይ የሰፈረው ውጤት ያወሳል፡፡

በጥናቱ ላይ የተሳተፉት ሰዎች በሳምንት ለ75 ደቂቃዎች በዮጋ እየተፍታቱ ህመሙን ለማስታገስ ሞክረው ውጤታማ ሆነዋል፡፡ የዮጋ ስፖርት ጀርባ ህመሙን ከማስታገሱ ባሻገር ሰውነትን ቀልጣፋ፣ ተጣጣፊና ጤናማ ያደርጋል ይላሉ የጥናት ወረቀቱን ያቀረቡት በአሜሪካ የሲያት ግዛት ግሩፕ ሄልዝ ሪሰርች ኢንስቲትዩት ተመራማሪ ዶ/ር ካረን ሸርማን፡፡

ራስ ምታት አልቆም ብሎዎታል? የተፈጥሮ መፍትሄ አለው…

አንዳንድ መነሻውን ያላወቅነው ራስ ምታት ሲወቅጠን ይውላል፡፡ ምክንያቱን ከስር መሰረቱ መፈተሽ አስፈላጊ ቢሆንም ለጊዜያዊ ማስታገሻነት የራስ ምታት ክኒኖችን መውሰዱ የተለመደ ነው፡፡ በአንዳንድ ሰዎች ዘንድ ክኒንም ሳይሰራ ራስ ምታቱ ሳይቆም የሚተርፋቸው ተጨማሪ ራስምታትና የጎንዮሽ ጉዳት ብቻ ይሆናል፡፡ የካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ግን ሰዎች ብዙ ሳይርቁ ራስ ምታቱን ወግድ ማለት ይችላሉ ብለዋል፡፡ መፍትሄውም ብዙ እንቅልፍ እና በጣም ጥቂት የራስ ምታት ክኒን ነው ብለዋል፡፡

በዩኒቨርሲቲ የህመም ጉዳዮ ጥናት ማዕከሉ ዳይሬክተር ፒተር ጎድስቢ እንደሚሉት ምንም ያል የራስ ህመም ቢደጋግምዎ ወደ ክኒኑ አይፍጠኑ፣ መውሰድ ካለብዎትም በሳምንት ቢበዛ ሁለት ክኒን ብቻ ይጠቀሙ፡፡ ከክኒኖቹ ይልቅ እንቅልፍ ያብዙ፡፡ ‹‹በራስምታት የሚጠመደው የጭንቅላት ክፍል የእንቅልፍ ማዕከል ነው፡፡ በየዕለቱ የማይቀያየር ቋሚ የእንቅልፍ ሰዓትን በመጠበቅ ከራስ ምታቱ መገላገል እንደሚቻል ጥናቶቻችን አሳይተውናል፡፡ የራስ ምታት ሁነኛ መፍት ጤናማ እና የተረጋጋ እንቅልፍ ነው›› ይላሉ ዶክተሩ፡፡

ድብርትዎን ማስለቀቂያው የፀረ ድብርት መድሃኒት አይደለም

ድብርት አንዳንድ ጊዜ ሲከሰት ብዙ አያሰጋም፡፡ በቃ አየሩ፣ ሰው፣ ስራው ሁሉ ሊደብረው ይችላል፡፡ ነገር ግን በህመም ደረጃ ተፈርጆ ዲፕሬሽ ሲባል ለዚህ ተብለው የተሰሩ መድሃኒቶች ይታዘዛሉ፡፡ ሳይንሳዊ መሰረት ያላቸው አዳዲስ ጥናቶች ግን ከመድሃኒቶቹ የሚልቅ አስተሳሰብን ዳግም በማሰልጠን የሚገኝ መፍት አለ እያሉ ነው፡፡ ይህ ስልጠና አሉታዊ ምልከታዎችን መንቅሎ ማስወገድና ሃሳብና ስሜቶችን ከጊዜዊ ሁኔታዎች ራቅ አድርጎ የሚከናወን እና የሚደብቱ ሃሳቦችን የሚያስወጣ ነው፡፡ በቅድሚያ ልክ በአሁኑ ሰዓት ሰውነትዎ ምን እየተሰማው እንዳለ እና እርስዎም ምን እየተሰማዎት እንደሆነ ትኩረት ሰጥተው ያድምጡ፡፡ ከዚያም ትኩረትዎን ወደ አተነፋፈስዎ ይመልሱ እና ወደ አሁኑ ቅጽበት ራስዎን ይመልሱ፡፡ ወደ ውስጥ እና ውጪ በመተንፈስ የአሁን ቅጽበት ስሜት በመላ ሰውነትዎ እንዲሰራጭ ትንፋሽዎን በመላ ሰውነትዎ ያሰራጩት፡፡ ቀላል ነው አይደል? ያዝናናል፣ ክፉ ስሜትንና ድብርትንም ያስወግዳል፡፡

The post Health: ያለክኒን በቤትዎ ሊያድኗቸው የሚችሉ 5 የጤና ችግሮች appeared first on Zehabesha Amharic.

ቤተ አምሃራ የወልቃይት ጠገዴ ጠለምትን ትግል በማስመለከት ብአዴንን አስጠነቀቀ –“ከአማራ ህዝብ ቁጣ ለመትረፍ ከህዝባችሁ ጎን ቁሙ”

0
0

bete amhara
ቀን: መጋቢት 13 2008 ዓ. ም
ወቅታዊውን የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የማንነት ትግልን በማስመልከት ከቤተ አማራ የተሰጠ መግለጫ ፦

የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የትግሬ – ወያኔ ሽፍታ ስርዓት በጉልበት የጫነባቸውን ባዕድ ማንነት በመቃወም የተፈጥሮ ማንነታቸው የሆነውን አማራነት ጥያቄ ያቀረቡት እጅግ ሰላማዊ በሆነ መንገድ እንደነበር ይታወቃል::
ይህም የታላቁ አማራ ህዝብ ለዘመናት የኖረበትን ከፍተኛ የሞራል ደረጃ ማሳያ ሆኖ ተመዝግቧል:: ምንም እንኳ በወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ ላይ የደረሰው እና አሁንም በመተግበር ላይ ያለው ግፍ እና የዘር ማጥፋት እርምጃ ለበቀል ሊያነሳሳ የሚችል የአረመኔዎች ተግባር ቢሆንም ሰፊው የአማራ ህዝብ በአስደናቂ ትዕግስት እና ሆደ ሰፊነት ለሁለት አስርት አመታት ጉዳዮን ታግሶት ቆይቷል::

ሰላማዊ እና ዲሞክራሲያዊ የመብት ጥያቄዎች የሚያስደነግጡት የትግሬ-ወያኔ አስተዳደር የእኛን ወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የማንነት ጥያቄ ለማዳፈን ያልጎነጎነው ሴራ የለም:: እስራት፣ ማዋከብ፣ አስገድዶ መድፈር፣ ማፈናቀል እና ግድያ በተለያዮ ጊዜያት በወገኖቻችን ላይ የተፈጸመ እና እየተፈጸመ ያለ ሲሆን በተቀነባበረ ወያኔያዊ ሰላማዊ ሰልፍም ያለምንም ሃፍረት በሃገሪቱ ቴሌቪዥንም በተዘገበ ፕሮግራም በወገኖቻችን ላይ የተለመደውን የጅምላ ግድያ እርምጃ ይወሰድ ዘንድ ሲለፍፉ ሰፊው የአማራ ህዝብ በአግራሞት ተከታትሎታል:: ከሶስት ቀናት በፊት በዳንሻ እና ሶሮቃ ተጠናክሮ የቀጠለው አፈና፣ እስር እና ግድያም የዚሁ በዕብሪት የተሞላው የፀረ – አማራ እቅዳቸው አካል ነው::

በመሆኑም የትግሬ-ወያኔ አስተዳደር ይህ ሁለቱን ህዝቦች ወደማይበርድ እልቂት ሊወስድ ከሚችለው ሰይጣናዊ ድርጊት ባስቸኳይ በመታቀብ የሚከተሉትን እርምጃዎች እንዲወስድ ቤተ አማራ በጥብቅ ያሳስባል::

1. በደህንነት አሽከሮቻችሁ ታፍነው የተወሰዱት የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የማንነት ኮሚቴው አባል አቶ ሊላይ ብርሃኔ እና ሌሎች አማሮች ያለምንም ማንገላታት ባስቸኳይ እንዲፈቱ::

2. የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የማንነት ጥያቄ የማይቀለበስ የመላው አማራ ጥያቄ መሆኑን ተገንዝባችሁ ከያዛችሁት እራስን የማጥፋት አካሄድ እንድትቆጠቡ::

3. በተለያዩ ቦታዎች በአማራ ወገኖቻችን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ማንገላታት፣ እስር እና ግድያ ባስቸኳይ እንዲቆም::

ወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ ሆይ ፦

የመላው ቤተ አማራ ወገኖቻችሁ ማንነታችሁ ማንነታችን፣ ጉዳታችሁ ጉዳታችን ፣ ጠላታችሁ ጠላታችን ብለን በተጠንቀቅ ከጎናችሁ የተሰለፍን መሆናችንን ልናረጋግጥላችሁ እንወዳለን::

መላው አማራ ሆይ ፦
የትግሬ – ወያኔ የደገሰልንን የዘር ማጥፋት ዘመቻ ለመመከት በጀግኖች አባቶቻችን መንፈስ በአማራነት ተደራጂተን በአንድነት እንድንቆም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን::

በዕርቅ ስም የህዝባችንን ትግል ለመቀልበስ ለምትንቀሳቀሱ ሃሳዊ ሽማግሌዎች እና የሃይማኖት አባቶች ፦
ሰላማዊ የሆነውን የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራነት ጥያቄ ለማዳፈን እውነተኛ ባልሆነ የሽምግልና ስም እየተንቀሳቀሳችሁ ያላችሁ ግለሰቦች ከአንዴም ሁለት ጊዜ ድብቅ ማንነታችሁን ህዝባችን ስልተረዳ ከዚህ መጥፎ ግብራችሁ እንድትታቀቡ በጥብቅ እናስጠነቅቃለን::

እንዲሁም የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ ለሃይማኖቱ ያለውን ቀናዒነት ተጠቅማችሁ የህዝባችንን የማይቀለበስ የማንነት ጥያቄ ለማዳከም እየጣራችሁ ያላችሁ የስርዓቱ ጥገኛ የሃይማኖት መሪዎች ከዚህ መሰሪ ተግባራችሁ እጃችሁን እንድትሰበስቡ በጥብቅ እናሳስባለን።

ለብአዴን ባለስልጣናት እና ካድሬዎች ፦

ከመጨረሻው የአማራ ህዝብ ቁጣ ለመትረፍ ከህዝባችሁ ጎን ከመቆም ውጭ ሌላ አማራጭ እንደሌላችሁ አውቃችሁ አስላለፋችሁን ታስተካክሉ ዘንድ በጥብቅ እናሳስባለን። ታላቁ የአማራ ህዝብ እንደ ንስር ሃይሉን ያድሳል ! ቤተ አማራ ወደፊት !

The post ቤተ አምሃራ የወልቃይት ጠገዴ ጠለምትን ትግል በማስመለከት ብአዴንን አስጠነቀቀ – “ከአማራ ህዝብ ቁጣ ለመትረፍ ከህዝባችሁ ጎን ቁሙ” appeared first on Zehabesha Amharic.

የትርፍ አንጀት ሕመም (APPENDICITIS)

0
0

(በዶ/ር ሆነሊያት ኤፍሬም ቱፈር)

የትርፍ አንጀት ሕመም የምንለው የህመም ዓይነት የሚከሰተው ከትልቁ አንጀት ቀጣይ በሆነው እና የ3 ½ inch ርዝመት ባለው የአንጀት ክፍል ነው፡፡
እስካሁን ድረስ የትርፍ አንጀት ጥቅም በእርግጠኝነት ያልታወቀ ሲሆን ያለ ትርፍ አንጀት ጤናማ ኑሮንም መምራት እንደሚቻል የሚታወቅ ነው፡፡
የትርፍ አንጀት ሕመም በአፋጣኝ ሕክምና ማግኘት ያለበት ሲሆን ሕክምና ካልተደረገለት ግን በሰውነት ውስጥ ይፈነዳና ኢንፌክሽን አምጪ ተዋስያንን በሆድ ዕቃ ውስጥ የከፋ ኢንፌክሽን እንዲፈጥሩ ያደርጋል፡፡
አንዳንድ ጊዜ መግል የያዘ ኢንፌክሽን ከሌላው የሰውንት ክፍል ራሱን ለይቶ ስለሚቆይ በጣም አጣዳፊ ባይሆንም እንኳን በእርግጠኝነት ለመለየት ግን ቀዶ ጥገና አስፈላጊ ስለሆነ ሁሉም የትርፍ አንጀት ሕመሞች የቀዶ ጥገና ሕመምና ያስፈልጋቸዋል፡፡
✔ የትርፍ አንጀት ሕመም በምን ይከሰታል?
የትርፍ አንጀት ሕመም የሚመጣው በትርፍ አንጀትና በትልቁ አንጀት መካከል የሚገኘው አንገት ሲዘጋ ነው፡፡ ይህ በሠገራ፣በቁስ አካል ወይንም በካንሰር አልያም በኢንፌክሽን ምክንያት ሊዘጋ ይችላል፡፡
✔ የትርፍ አንጀት ሕመም ምልክቶች
• ከእምብርት አካባቢ ጀምሮ ወደ ታችኛው የቀኝ የሆድ ክፍል የሚወርድ የህመም ስሜት
• የምግብ ፍላጎት ማጣት
• ማቅለሽለሽና ማስመለስ ከሆድ ሕመሙ በመቀጠል ይከሰታል
• ትኩሳት
• አየር ለማስወጣት መቸገር
• ለመንቀሳቀስ መቸገር
ከላይ የተጠቀሱትን ዓይነት የህመም ስሜት ከተሰማዎ በአፋጣኝ ወደ ሕክምና ቦታ መሄድ ተገቢ ነው፡፡ ይህም የሚሆነው በአፋጣኝ ሕመሙ ታውቆ ሕክምና ሊደረግ ስለሚገባው ነው፡፡

appendicitis-600x330
ምንም ዓይነት ምግብ ወይንም መጠጥ ወይንም ሕመም ለማስታገስ የሚወሰዱ የቤት ውስጥ መድኃኒቶች እንዳይወሰዱ ይመከራል፡፡ ይህም ያበጠው ትርፍ አንጀት እንዳይፈነዳ ያደርጋል፡፡
✔ የትርፍ አንጀት ሕመም ምርመራዎች
በምልክቶች ብቻ የትርፍ አንጀት ሕመምን በእርግጠኝነት ለማወቅ ስለሚያስቸግር ሌሎች በመሳሪያ የታገዙ ምርመራዎች ማድረግ ተገቢ ነው፡፡
• የሆድ አልትራሰውንድ
• የደም እና የሽንት ምርመራዎች የመሳሰሉት ናቸዉ፡፡
✔ የትርፍ አንጀት ሕክምና ምንድን ነው?
• በቀዶ ጥገና የትርፍ አንጀቱን ቆርጦ ማውጣት ይህም በህክምናዉ (Appendectomy) የምንለዉ ዋነኛው ሕክምና ሲሆን መግል የያዘ ትርፍ አንጅት መጀመሪያ መግሉን በማስወገድ አልያም ፀረባክቴሪያ መድኃኒቶችን በመጠቀም የቀዶ ጥገና ጊዜው የሚራዘምበት ሁኔታ ሊኖር ይችላል፡፡
✔ ቀዶ ጥገናው ከተደረገ በ12 ሰዓት ውስጥ እቅስቃሴ መጀመር የሚቻል ሲሆን፣
• የማይቆም ማስመለስ
• ከፍተኛ የሆድ ሕመም
• ራስ ማዞር
• ደም የቀላቀለ ማስመለስና ሽንት ከጋጠምዎ
• በስፌቱ ላይ ሕመም እና መቅላት ካመጣ
• ትኩሳት እና መግል ከቁስሉ የወጣ ከሆነ በአፋጣኝ ወደ ሐኪምዎ በመሄድ እንዲያማክሩ ይመከራል፡፡
የትርፍ አንጀት እንዳይመጣ ለመከላከል የማይቻል ቢሆንም፣ ጥናቶች እንደሚሳዩት ከሆነ ግን በፋይበር የበለፀጉ ምግቦችን (ፍራፍሬዎችና አትክልት) የሚመገቡ ሰዎች ላይ የመከሰት ዕድሉ እንደሚቀንስ ነው፡፡
ጤና ይስጥልኝ

The post የትርፍ አንጀት ሕመም (APPENDICITIS) appeared first on Zehabesha Amharic.

የመቐለ ባለ ባጃጆች ኣድማ መትተዋል። ሁለት የዓረና ከፍተኛ ኣመራሮች ታሰሩ

0
0

Andomanከዛሬ 14 / 07 / 2008 ዓ/ም ረፋድ የጀመረው የባለ ባጃጆች ኣድማ “እንደ ሚኒባስ ታክሲዎች ታፔላ ኣበጅታቹና በስምሪት ብቻ መስራት ኣለባቹ” የሚል ኣዲስ ኣሰራር በመቃወም የተመታ ኣድማ ነው።

ዛሬ እሮብ መቐለ ከተማ ባጃጆች ምንም ዓይነት እንቅሴቃሴ ኣይታይባቸውም።

ከሁለት ሺ ኣምስት መቶ በላይ የሆኑት ባለ ባጃጆች “እምቢ ለመብቴ” ብለው በውሳኔያቸው ፀንተዋል።

መቐለ ከተማ ከፍተኛ የህዝብ ትራንስፖርት ችግር ተከሰቶ ይገኛል።

 

የዓረና የህዝብ ግኑኝነት ሓላፊው ዓንዶም ገብረስላሴና Amdom Gebreslasie የድርጅቱ ፅህፈት ቤት ሓላፊ ዘነበ ሲሳይ ZENEBE SISAY በፖሊሶች ታስረው ተወስዶዋል፡፡ ከኣስር ደቂቃ በፊት የትግራይ ክልል ልዩ ሓይል ፖሊስ ለሁለቱም በመቐለ ወደ ሓወልቲ ክፍለ ከተማ ተወስዷል፡፡

The post የመቐለ ባለ ባጃጆች ኣድማ መትተዋል። ሁለት የዓረና ከፍተኛ ኣመራሮች ታሰሩ appeared first on Zehabesha Amharic.

ፍትሕ ሚኒስቴርን የሚያፈርስ ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ ቀረበ

0
0

injustice_minisitry21377381254በምትኩ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ሊቋቋም ነው

  • ፀረ ሙስና ኮሚሽን ሥነ ምግባር ላይ ብቻ እንዲያተኩር ይገደዳል
  • ፌዴራል ፖሊስ ተጠሪነት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ሊሆን ነው

የፍትሕ ሚኒስቴርን የሚያፈርስ ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ ቀረበ፡፡ በምትኩ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ተቋምን ለመመሥረት የሚያስችል ሌላ ረቂቅ አዋጅም ለፓርላማ ማክሰኞ መጋቢት 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀርቧል፡፡

ፓርላማው ከቀረቡለት በርካታ ረቂቅ አዋጆች መካከል በቅድሚያ የተወያየው፣ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዴሪ) አስፈጻሚ አካላትን ለማቋቋም የወጣውን አዋጅ ቁጥር 916/2008 ለማሻሻል በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ ነው፡፡

ይህ አዋጅ በመስከረም ወር 2008 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ካቢኔያቸውን ባዋቀሩበት ወቅት በፓርላማው የፀደቀ ሲሆን፣ መጋቢት 13 ቀን 2008 ዓ.ም. የቀረበበት ረቂቅ ማሻሻያም ሦስት አንቀጾችን የያዘ ነው፡፡

የመጀመሪያው ረቂቅ ማሻሻያ የአዋጅ ቁጥር 916/2008 አንቀጽ 16 መሰረዙን የሚገልጽ ነው፡፡ አንቀጽ 16 ማለት የፍትሕ ሚኒስቴር ሥልጣንና ተግባርን ሙሉ በሙሉ የሚዘረዝር ነው፡፡

ሌሎች ረቂቅ ማሻሻያዎቹ የሚመለከቱት የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ተጠሪነት አሁን ከሚገኝበት የፌዴራልና የአርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስቴር ወጥቶ፣ ተጠሪነቱ ለጊዜው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ መሆኑን የሚገልጽ ነው፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ የፍትሕና የሕግ ምርምር ኢንስቲትዩትና የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ተጠሪነት በቅርቡ ይቋቋማል ተብሎ ለሚጠበቀው የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ እንዲዘዋወር የሚያደርጉ ማሻሻያዎች ናቸው፡፡

ፓርላማው ረቂቅ ማሻሻያውን ለዝርዝር ዕይታ ለሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርቶታል፡፡ ይህ ቋሚ ኮሚቴ የቀረቡትን ማሻሻያዎች ተቀብሎ ለፓርላማው የውሳኔ ሐሳቡን የሚያቀርብ ከሆነ፣ በዚህ መሠረትም ፓርላማው ካፀደቀው በሥራ ላይ የሚገኘው ፍትሕ ሚኒስቴር ይፈርሳል፡፡

በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ እንዲሰጡ በስልክ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የፍትሕ ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው አምባዬ፣ ‹‹›ፓርላማው ማሻሻያውን ካፀደቀው ፍትሕ ሚኒስቴር ምን ይዞ ይቆማል?›› በማለት እንደሚፈርስ አረጋግጠዋል፡፡

ይሁን እንጂ በምትኩ የፍትሕ ሚኒስቴርን ሥልጣንና ኃላፊነት እንዲሁም ሌሎች ተጨማሪ ጉዳዮችን በኃላፊነት የሚረከብ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ እንደሚቋቋም ገልጸዋል፡፡

ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው እንዳሉት፣ ይህንኑ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የሚያቋቁም ረቂቅ አዋጅ በተመሳሳይ ዕለት ለፓርላማው ቀርቦ ውይይት ተካሂዶበታል፡፡

የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ ጋር አባሪ የተደረገው ማብራሪያ የሕግ ማስከበር ተግባር በዓቃቤ ሕግ የሚከናወን መሆኑን፣ ነገር ግን ይህ የዓቃቤ ሕግነት ሥራ በተለያዩ ተቋማት ተበታትኖ እየተሠራ የሚገኝ በመሆኑ የሕግ ማስከበር ሥራውን ውጤታማና ቀልጣፋ እንዳይሆን ማድረጉን ይገልጻል፡፡

እስካሁን ባለው አፈጻጸም የዓቃቤ ሕግነት ሥራ በተለያዩ የፌዴራል ተቋማት ማለትም በፍትሕ ሚኒስቴር፣ በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን፣ በሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን፣ እንዲሁም በንግድ ውድድርና የሸማቾች ጥበቃ ባለሥልጣን ተበትኖ የሚገኝ መሆኑን ያስረዳል፡፡

‹‹ይህ አፈጻጸም ወጥነት የሌለውና የሕዝብን ጥቅም በአግባቡ የማያስከብር ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ስለሆነም የተበተነውን የዓቃቤ ሕግነት ሥራ በአንድ ተቋም በማሰባሰብ በወጥነትና የሕዝብን ጥቅም ማዕከል ባደረገ መልኩ መፈጸም እንዲያስችል፣ የመመርመር ሥራ ወደ ፌዴራል ፖሊስ እንዲሰበሰብ ማድረግና የመክሰስ ሥልጣን የሚኖረው የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ተቋም ማደራጀት አስፈልጓል፤›› ይላል የረቂቅ ማቋቋሚያ አዋጁ ማብራሪያ፡፡

የሚቋቋመው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በሕግ ጉዳዮች የፌዴራል መንግሥት ዋና አማካሪና ተወካይ ሆኖ እንደሚሠራ ረቂቅ አዋጁ ይገልጻል፡፡

የወንጀል ምርመራ እንዲጀመር ፌዴራል ፖሊስን ማዘዝ፣ የተጀመረ የወንጀል ምርመራ ላይ የክትትል ሪፖርት እንዲቀርብ፣ እንዲሁም ምርመራው በአግባቡ ተከናውኖ እንዲጠናቀቅ፣ በሕዝብ ጥቅም መነሻ ወይም በወንጀል የማያስጠይቅ ሁኔታ መኖሩ በግልጽ ሲታወቅ እንዲቋረጥ፣ ወይም የተቋረጠው እንዲቀጥል የሚያደርግ መሆኑን ረቂቁ ያስረዳል፡፡

ፖሊስ በራሱ የጀመረው ምርመራ ካለ ለጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የማሳወቅ ግዴታ ሲኖርበት፣ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በበኩሉ በምርመራ መዝገብ ላይ የሰጠውን ውሳኔ ወይም ፍርድ ቤት በመዝገቡ ላይ ስለተሰጠው ውሳኔ ለፖሊስ እንደሚያሳውቅ ረቂቁ ይገልጻል፡፡

ምርመራ የማድረግ፣ ማስረጃ የማሰባሰብ፣ ኤግዚቢት የመያዝ፣ ተጠርጣሪን የማቅረብና የመሳሰሉት ተግባራት የፖሊስ መሆናቸውን የረቂቁ ማብራሪያ ያስረዳል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ደግሞ ምርመራውን የመምራት ሥልጣን እንደሚኖረው፣ በተጨማሪም የማኅበረሰብ አገልግሎት ቅጣቶችን የሚያስፈጽም አደረጃጀትን ማመቻቸት፣ ፍርድ ቤቶች በወንጀል ጉዳይ የሚሰጧቸው ውሳኔዎችና ትዕዛዞች መፈጸምና መከበራቸውን መከታተል፣ ሳይፈጸሙ ከቀሩ ወይም አፈጻጸማቸው ሕግን ያልተከተለ ከሆነ ጉዳዩን ላየው ፍርድ ቤት በማመልከት የእርምት ዕርምጃ እንዲወሰድ የማድረግ ኃላፊነት እንደሚኖረው በረቂቅ አዋጁ ተገልጿል፡፡

የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ተቋም ተጠሪነትም ለጠቅላይ ሚኒስትሩና ለሚኒስትሮች ምክር ቤት እንደሚሆን፣ የፌዴራል ዋና ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በፓርላማው እንደሚሾም ረቂቁ ይገልጻል፡፡

የረቂቁ አንቀጽ 26 ደግሞ ስለ ዓቃቢያነ ሕግ የወጣው አዋጅ ቁጥር 74/1986 የሚሻር መሆኑን፣ እንዲሁም ከረቂቅ አዋጁ ጋር የሚቃረኑ ማናቸውም ሕጐች በረቂቅ አዋጁ በተሸፈኑ ጉዳዮች ላይ ተፈጻሚነት እንደማይኖራቸው ይገልጻል፡፡

በመሆኑም የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ረቂቅ አዋጅ የሚፀድቅ ከሆነ የፌዴራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና የተጠረጠሩ ግለሰቦችን የመክሰስ ሥልጣኑ ተቀንሶ፣ መልካም ሥነ ምግባርን በማስረፅ ተግባር ላይ ብቻ እንዲያተኩር ይገደዳል፡፡

ፓርላማው ከአንድ ወር በፊት የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽንን በሥነ ምግባር ትምህርት ላይ ብቻ ጊዜውን እያጠፋ እንደሆነ በመግለጽ እንደተቸው ሪፖርተር መዘገቡ ይታወሳል፡፡

በረቂቅ አዋጁ አንቀጾች ዙሪያ በስልክ አጭር ማብራሪያ የሰጡት የፍትሕ ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው አምባዬ፣ ‹‹የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ቀድሞም ቢሆን በዋናነት የተቋቋመው ሙስናን የማይሸከም ዜጋን ለመፍጠር እንዲሠራ ነው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹በሙስና ወንጀሎች ላይ ክስ መመሥረት ተጨማሪ ኃላፊነቱ ነበር፡፡ ነገር ግን በኅብረተሰቡ ዘንድ ጐልቶ የሚታወቀው የመክሰስ ኃላፊነቱ ነው፤›› በማለትም አክለዋል፡፡

ፓርላማው የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ማቋቋሚያ ረቂቅንም ለሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርቶታል፡፡

አንዳንድ የፓርላማው አባላት የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ተጠሪነት ለጠቅላይ ሚኒስትሩና ለሚኒስትሮች ምክር ቤት መሆኑ የሚፈለገውን የሙያ ነፃነት ሊነፍገው አይችልም ወይ? የፌዴራል ፖሊስ ተጠሪነት በጊዜያዊነት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የተሰጠበትንና ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ያልሆነበት ምክንያትና ሌሎችንም የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በዝርዝር እንዲመለከትላቸው ጠይቀዋል፡፡

ምንጭ – ሪፖርተር

The post ፍትሕ ሚኒስቴርን የሚያፈርስ ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ ቀረበ appeared first on Zehabesha Amharic.

ከ180 ሚሊዮን ብር በላይ በማጭበርበር የተጠረጠረው ዙና ትሬዲንግ ሠራተኞች ታሰሩ

0
0

ከ400 ሚሊዮን ብር በላይ ይዞ የተሰወረው ተጠርጣሪም መያዙ ተጠቆመ

zuna_tradingከ150 በላይ ግለሰቦች ላይ ከ180 ሚሊዮን ብር በላይ በመሰብሰብ መሰወራቸው የተገለጸው የዙና ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ ባለቤት ተባባሪ ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ አራት የድርጅቱ ሠራተኞች፣ ታስረው ፍርድ ቤት ቀረቡ፡፡
የድርጅቱ የማርኬቲንግ ሥራ አስኪያጅን ጨምሮ አራቱ ተጠርጣሪዎች በፖሊስ በቁጥጥር ሥር ውለው፣ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቦሌ ምድብ ችሎት የቀረቡት መጋቢት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. ነው፡፡
ተጠርጣሪዎቹ የድርጅቱ ባለቤት መሆናቸው የተገለጸው አቶ ዘሪሁን ጌታሰው፣ የተለያዩ የኮንስትራክሽን ማሽነሪዎችንና በተለይ ሲኖትራክ የጭነት ተሽከርካሪ በግማሽ ክፍያና የባንክ ብድር በማመቻቸት እንደሚያቀርቡ፣ በተለያየ ሁኔታ ሲያስነግሩ መክረማቸው ተገልጿል፡፡
ከድርጅቱ ጋር ውል የፈጸሙ ተበዳዮች ዕምነት እንዲኖራቸው ለተወሰኑት ሰዎች ተሽከርካሪዎቹን በውላቸው መሠረት በማቅረብ ያስረከቡ ቢሆንም፣ ተመሳሳይ ዕድል ለማግኘት ሙሉ ዕምነት በመጣል በርካታ ሰዎች ግማሽና ሩብ ክፍያ በድምሩ ከ180 ሚሊዮን ብር በላይ በመክፈል ውል ከፈጸሙ በኋላ፣ በገቡት ውል መሠረት ሊፈጸምላቸው አለመቻላቸውን መርማሪዎች ለፍርድ ቤት አስረድተዋል፡፡
የድርጅቱን ባለቤት በቁጥጥር ሥር ለማዋል የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ወጥቶ እየተፈለጉ መሆኑንና በርካታ ቀሪ ምርመራዎች እንደሚቀሩ ለፍርድ ቤቱ በማስረዳት፣ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ ፖሊስ ጠይቆ ተፈቅዶለታል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ዋስትና እንዲፈቀድላቸው የጠየቁ ቢሆንም ፍርድ ቤቱ አልተቀበላቸውም፡፡
በሌላ በኩል ያገለገሉ ተሽከርካሪዎችን በማምጣት በግማሹ ክፍያ እንደሚሸጥ በመግለጽ በ19 ከተሞች ከሚገኙ ነዋሪዎች፣ ከ400 ሚሊዮን ብር በላይ ሰብስቦ በመሰወር የተጠረጠረው ግለሰብ ከነግብረ አበሮቹ በአማራ ክልል ደሴ ከተማ ውስጥ በቁጥጥር ሥር ውሎ በምርመራ ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡
‹‹ኢንተርናሽናል የመኪና አስመጪና መተባበር ዕቁብ›› የሚባል ድርጅት ባለቤት መሆኑ የተገለጸውና ራሱን ‹‹አማኑኤል አዲሱ መተባበር›› በማለት የሚጠራው ግለሰብ፣ በተለያዩ ከተሞች 19 ቅርንጫፎች በመክፈት የተጠቀሰውን ገንዘብ መሰብሰቡም ተገልጿል፡፡ ግለሰቡ የድርጅቱን ቅርንጫፎች በሻሸመኔ፣ በዝዋይ፣ በመቂ፣ በሐዋሳ፣ በወላይታ ሶዶና ደሴን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች 19 ቅርንጫፎች ከፍቷል፡፡ በዚህም መሠረት የተለያዩ ማስታወቂያዎችን በመጠቀም ማናቸውም ዓይነት ያገለገሉ ተሽከርካሪዎችን በቅናሽ ዋጋ እንደሚያቀርብ በመግለጹ፣ ተበዳዮቹ ሊጭበረበሩ መቻላቸውን የደሴ ከተማ ፖሊስ መምሪያ የወንጀል ምርመራ ዋና የሥራ ሒደት ኃላፊ ዋና ኢንስፔክተር የሺወርቅ ላቀው ለመገናኛ ብዙኃን ገልጸዋል፡፡
የድርጀቱ ባለቤት ባጃጅን ጨምሮ ትልልቅ የጭነት ተሽከርካሪዎችን እንደሚያቀርብ በመግለጽ፣ ከ50 ሺሕ እስከ 800 ሺሕ ብር ግማሽ ክፍያ በመቀበል ከ400 ሚሊዮን ብር በላይ ሲሰበስብ፣ ተሽከርካሪዎቹን እስከሚያስረክብ ድረስ መተማመኛ በማለት ደረቅ ቼክ ፈርሞ በመስጠት ሊያታልላቸው እንደቻለ ተበዳዮቹ ለፖሊስ አስረድተዋል፡፡ ግለሰቡ ገንዘቡን ከሰበሰበ በኋላ በመሰወሩ የጻፈላቸውን ደረቅ ቼክ ይዘው ወደ ባንክ የሄዱ ቢሆንም፣ በባንከ ውስጥ በቂ ገንዘብ እንደሌለው ሲነገራቸው ተበዳዮቹ ለፖሊስ አመልክተዋል፡፡ ፖሊስ የፍርድ ቤት መያዥያ በማውጣት ሲከታተል ከርሞ፣ ሰሞኑን ከነግብረ አበሮቹ በቁጥጥር ሥር ማዋሉን፣ አራት ተባባሪዎቹ ደግሞ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ መያዛቸውን ዋና የሥራ ሒደት ኃላፊዋ አስረድተዋል፡፡

ምንጭ – ሪፖርተር

The post ከ180 ሚሊዮን ብር በላይ በማጭበርበር የተጠረጠረው ዙና ትሬዲንግ ሠራተኞች ታሰሩ appeared first on Zehabesha Amharic.


“መለስ ካረፉ በኋላ በእርግጥም ለውጥ አለ”–ልደቱ አያሌው

0
0

Lidetu ayalew
አቶ ልደቱ አያሌው ከሃገር ቤት ከሚታተመው ሪፖርተር ጋዜጣ ጋር ያደረጉትን ቃለምልልስ ለዘ-ሐበሻ አንባቢዎች ግንዛቤ ይረዳ ዘንድ እንደወረደ አቅርበነዋል::
ልደቱ አያሌው የኢትዮጵያዊያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) መሥራች ናቸው፡፡ ኢዴፓን ለበርካታ ዓመታት የመሩት አቶ ልደቱ በአወዛጋቢው ምርጫ 97 የኢሕአዴግ ብርቱ ተፎካካሪ በነበረው የአራት ፓርቲዎች ጥምረት ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ በፓርቲያቸው ተወክለው ባሳዩት አመራር ዝናቸው ጫፍ ደርሶ ነበር፡፡ ይሁንና ከምርጫው በኋላ የቅንጅት አመራሮች ሲከፋፈሉ አቶ ልደቱ ላይ የተሰነዘሩት ወቀሳዎች ተቀባይነታቸው ላይ ጥያቄ እንዲነሳባቸው አድርገው ነበር፡፡ አቶ ልደቱ በእሳቸውና በፓርቲያቸው ላይ የቀረበው ወቀሳ አሉባልታ እንጂ ተጨባጭ መረጃና ማስረጃ የሚቀርብበት ሀቅ እንዳልሆነ በሚጽፏቸው መጻሕፍትና መጣጥፎች፣ ለተለያዩ ሚዲያዎች በሚሰጧቸው ቃል ምልልሶች ሲሞግቱ ቆይተዋል፡፡ አቶ ልደቱ እስከ 2003 ዓ.ም. በኢዴፓ ፕሬዚዳንትነታቸው በፖለቲካው መድረክ ጉልህ ሚና መጫወታቸውን ቢቀጥሉም፣ ከዚያ በኋላ ግን በመድረኩ ላይ ብዙም አይታዩም፡፡ የኢዴፓ መሪነቱን ለአቶ ሙሼ ሰሙ ያስረከቡት አቶ ልደቱ በእንግሊዝ ለንደን ዩኒቨርሲቲ በዴቨሎፕመንት ስተዲስ የማስተርስ ዲግሪ አጠናቀዋል፡፡ ከዚያ በፊት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በታሪክ ትምህርት የመጀመሪያ ዲግሪ አግኝተዋል፡፡ ከእንግሊዝ መልስ ‹‹ቲያትረ ፖለቲካ›› በሚል ርዕስ ባለፈው ዓመት መጽሐፍ ማሳተማቸውም ይታወሳል፡፡ ‹‹በሕይወት እስካለሁ ድረስ ራሴን ከፖለቲካ ማግለል ፈጽሞ አይታሰብም!›› የሚሉት አቶ ልደቱ፣ የኢዴፓ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ባይሆኑም የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል በመሆን አሁንም የሚጠበቅባቸውን ተግባር እየተወጡ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ኢሕአዴግ የሠራውን በጎ ተግባር ዕውቅና በመስጠት እንዲሁም ያጠፋውንና ድክመት ያሳየበትን ጉዳይ በግልጽ በመጠቆም የሚተነትኑት አቶ ልደቱ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የገዥው ፓርቲ ዋነኛ አጀንዳ የሆነው የመልካም አስተዳደር ችግሮች ላይ የሚሰማቸውንም አካፍለዋል፡፡ ሰለሞን ጎሹ በወቅታዊ ጉዳዮችና በመልካም አስተዳደር ዙሪያ አቶ ልደቱን አነጋግሯቸዋል፡፡

ሪፖርተር፡- የመልካም አስተዳደር ችግር በስፋትና በጥልቀት የአገሪቱን ህልውና እየተፈታተነ ነው የሚል ግምገማ በራሱ በመንግሥት ቀርቧል፡፡ ብዙ የኅብረተሰብ ክፍሎችም በዚህ ይስማማሉ፡፡ ዋነኛው የልዩነት ምንጭ የችግሩ መነሻ ምንድነው የሚለው ነው፡፡ በእርስዎ ግምገማ የዚህ መጠነ ሰፊ ችግር ዋነኛ ምንጭ ምንድነው?

አቶ ልደቱ፡- አንዱ መግባባት ያቃተን በችግሩ ክብደት ላይ ነው፡፡ ኢሕአዴጎች እንደተባለው ችግሩ የህልውና ጉዳይ ስለሆነ በከፍተኛ ዘመቻ ችግሩን ለመፍታት ቆርጠን ተነስተናል እያሉ ነው፡፡ በተቃዋሚዎች ዘንድና በአንዳንድ የኅብረተሰብ ክፍሎች ይኼ እንደ እውነት አልተወሰደም፡፡ ኢሕአዴግ እንደተለመደው ዘመቻ መልክ ቴአትር አሳይቶ የሚተወው የማስመሰያ እንቅስቃሴ ነው የሚል አስተሳሰብ አለ፡፡ እኔ ኢሕአዴግ ይኼ ችግር የህልውና ጉዳይ ነው፣ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ ነው ብሎ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ የቀልድ ነው ብዬ አላምንም፡፡ የምር ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ኢሕአዴግ የምር እየተንቀሳቀሰ ያለው ይኼ ችግር ሳይፈታ ከቀጠለ የሥርዓቱን ህልውና እንደሚፈታተንና አደጋ ላይ እንደሚጥለው ስለገባው ይመስለኛል፡፡ ሥርዓቱ ላይ ያለው አንዱም ችግር ይኼ ነው፡፡ ችግሮች ሳይጠነክሩ፣ ሳይሰፉና ሥር ሳይሰዱ ለሕዝብና ለአገር ጥቅም ሲባል በተገቢው ወቅትና ሁኔታ መፈታት ሲገባቸው፣ አንዳንድ ጊዜ ዘመቻዎቹ ጠንከር ብለው የሚመጡት በራሱ ህልውና ላይ ችግሩ ሲመጣ ነው፡፡ ይኼ ችግር የሥርዓቱን ህልውና ብቻ አይደለም የሚፈታተነው፡፡ አጠቃላይ የአገር ጥቅምና ደኅንነትን የሚፈታተን ጉዳይ ነው፡፡ ኢሕአዴግ ማየት የነበረበት ከአገር ጥቅም እንጂ ከራሱ ጥቅምና ደኅንነት አንፃር መሆን አልነበረበትም፡፡ ዞሮ ዞሮ በዚህ ጉዳይ ላይ ኢሕአዴግ እየቀለደ አይደለም፡፡ እርግጥ በኢሕአዴግ በኩል መልካም አስተዳደር ምንድነው በሚለው ጉዳይ ላይ ልዩነት አለ፡፡ ከተለያዩ መድረኮች እንደተረዳነው በኢሕአዴግ አስተሳሰብ መልካም አስተዳደር የቢሮክራሲ ውጣ ውረድ ነው፡፡ ኅብረተሰቡ ወደ መንግሥት ቢሮዎች አገልግሎት ፈልጎ ሲሄድ የሚገጥመው ውጣ ውረድና የመጉላላት ችግር ተደርጎ ነው የሚታየው፡፡ በእርግጥም ይኼ አንዱ የመልካም አስተዳደር ችግር መገለጫ ነው፡፡

ነገር ግን መልካም አስተዳደር የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት ጥያቄም ነው፡፡ በአጠቃላይ የመንግሥትንና የሕዝብን ግንኙነት የሚመለከት ጉዳይ ነው፡፡ በምርጫ አማካይነት ከሕዝብ ጋር የገባውን ውል መንግሥት በአግባቡ እየተወጣ ነው ወይስ አይደለም የሚለው ጥያቄ ነው የመልካም አስተዳደር ጥያቄ፡፡ ገዥው ፓርቲ ግን የመልካም አስተዳደር ጥያቄን በዋናነት ከኢኮኖሚ ጉዳይ ጋር አስተሳስሮ ያያል፡፡ በዚህ መልኩ የሚደረግ ዘመቻ ችግሩን ከምንጩ ያደርቃል ብዬ አላምንም፡፡ ሁለተኛ በዚህ ጠባብ ማዕቀፍም ውስጥ ቢሆን የችግሩ መሠረታዊ ምንጭ ምንድነው የሚለው ላይ በግልጽ ውይይት ሲደረግበት አይታይም፡፡ እርግጥ ችግሩ ምን ያህል ከባድ እንደሆነና በሁሉም የአገሪቱ አካባቢ ያለ መሆኑ ላይ የፖለቲካ አመራሩ ስምምነት ላይ የደረሰ ይመስላል፡፡ ለምንድነው ይኼ ሥርዓት በዚህ መጠንና ሁኔታ የመልካም አስተዳደር ችግር ውስጥ የተዘፈቀው ብሎ መሠረታዊ የሆነውን ምክንያት ማወቅና ችግሩን ከምንጩ የማድረቅ አቅጣጫ ግን አይታይም፡፡ እኔ ከዚህ በፊት በጋዜጣችሁ ላይ ይኼ ዘመቻ የሚከሽፍ መሆኑ ከወዲሁ የታወቀ ነው ብዬ ለመደምደም ያስገደደኝ ይኼ ምክንያት ነው፡፡ ለእኔ ምንጩ የፖለቲካ ሙስና ነው፡፡ የኢኮኖሚ ሙስናው የፖለቲካ ሙስናውን ተከትሎ የመጣ ነው፡፡ ሥርዓቱ ለፖለቲካ ሥልጣን የበላይነት ብሎ ከፍተኛ የሆነ የፖለቲካ ሙስና የሚፈጽም በመሆኑ የኢኮኖሚ ሙስናው ይኼን ተከትሎ የመጣ ነው፡፡ በቢሮክራሲው ውስጥ የሚቀጠሩት ሰዎች በሙያ ብቃታቸው፣ በትምህርት ደረጃቸውና በሥነ ምግባራቸው አይደለም በዋናነት የሚመለመሉት፡፡ በዋናነት የሚቀጠሩት ለሥርዓቱ ባላቸው ታማኝነት ነው፡፡ ይኼ የፖለቲካ ውሳኔ ነው፡፡ የፖለቲካ ሙስናም ነው፡፡ ከሚኒስትር ጀምሮ እስከ ጥበቃና ፅዳት ሠራተኛ ድረስ ሰዎች የሚቀጠሩት በፖለቲካ ታማኝነታቸው ነው፡፡ የአገሪቱን ቢሮክራሲ የሚያመርቱት ዩኒቨርሲቲዎች ሲመረቁ ሳይሆን ገና ሲገቡ ነው ተማሪዎቹ የኢሕአዴግን የመታወቂያ ካርድ በእጃቸው የሚይዙት፡፡ ምክንያቱም በሥራ የመቀጠር ዋስትናቸው እሱ ነው፡፡ በዚህ መልኩ በፖለቲካ ሙስና የተሰባሰበ ቢሮክራሲ የኢኮኖሚ ሙስና ቢፈጽምና የመልካም አስተዳደር ችግር ውስጥ ቢዘፈቅ የሚደንቅ አይደለም፡፡

Lidetu

አንድ ሥርዓት የፖለቲካ የሥልጣን የበላይነቱን ለማስጠበቅ ብሎ ምርጫን የሚያጭበረብር ከሆነ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን የሚያፍን ከሆነ፣ የሕዝብን ሰብዓዊ መብት የሚያፍን ከሆነ፣ የፕሬስ መብትን የሚያፍን ከሆነ፣ ይህን የሚያደርገው በካድሬዎቹ አማካይነት ነው፡፡ አባላቱ እንዲህ ዓይነት የፖለቲካ ሙስና ሲፈጽሙ የማይቀጣ መንግሥት የኢኮኖሚ ሙስና ሲፈጸም ሊደንቀው አይገባም፡፡ በተለይ በዝቅተኛ እርከን ላይ ያሉ ካድሬዎች ናቸው በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ዳታ የሚያዘጋጁት፡፡ የሚቀርበው ዳታ አለቆችን የሚያስደስት እንጂ እውነታውን የሚያንፀባርቅ አይደለም፡፡ የበላይ አመራሮች የሚቀርብላቸውን ዳታ እንዳለ በግርድፉ ከመቀበል ይልቅ ዳታ ኦዲት ማድረግ ተገቢ እንደሆነ ለዓመታት ተከራክሬያለሁ፡፡ ይህ እንደ ጠቃሚ ሐሳብ አሁንም ድረስ አይወሰድም፡፡ እኔ ከ20 ዓመታት በላይ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ተሳትፎ ቢኖረኝም ይህ ካድሬ ይህን የፖለቲካ ሙስና ፈጽሟል ተብሎ ዕርምጃ ሲወሰድበት አላየሁም፡፡ አባላቱን ለመቅጣት አለመፈለግ ብቻ ሳይሆን አንዳንድ ጊዜ እነዚህ የፖለቲካ ሙስናዎች በመንግሥት ትዕዛዝ የሚፈጸሙ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ በቢሮክራሲው ውስጥ የተሰባሰበውን ካድሬ ካየህ የሕዝብ አገልግሎትን አጀንዳ አድርጎ የተሰበሰበ ኃይል አይደለም፡፡ በተለይ ከምርጫ 97 በኋላ በኢሕአዴግ ዙሪያ የተሰበሰበው ኃይል ጥቅም ፈላጊ ኃይል ነው፡፡ ስለዚህ የፖለቲካ ሙስናን ስትዋጋ የኢኮኖሚ ሙስናን ማድረቅ አትችልም፡፡ ስለዚህ ይህን ችግር ለመቅረፍ መሠረታዊና ሥር ነቀል የሆነ የፖለቲካ አስተሳሰብ ለውጥ ያስፈልጋል፡፡

ሪፖርተር፡- የኢትዮጵያ የፌዴራል ሥርዓት ማንነት ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ይህ ለብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በፍትሐዊነት የአገሪቱን ሀብትና ሥልጣን ማከፋፈልን ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡ ነገር ግን ይኼ አቅምን መሠረት ካደረገ ቢሮክራሲ ጋር አብሮ ይኼዳል?

አቶ ልደቱ፡- መሠረታዊው ነገር በአንድ የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ በቋንቋና በዘር ማንነታቸው ካደራጀህ ሌሎች ለሥራ፣ ለአስተዳደርና ለኢኮኖሚ ዕድገት አስፈላጊ የሆኑት ነገሮች ሁሉ ወደ ጎን ይገፋሉ፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ አሁን ያለው የመልካም አስተዳደር ችግር ከዚሁ የሚመነጭ ነው፡፡ ሰዎች ወደ አንድ የመንግሥት መሥሪያ ቤት አገልግሎት ፈልገው ሲሄዱ ምን ዓይነት ተቋም አለ? ምን ዓይነት ሕግ አለ? ብለው አይደለም የሚሄዱት፡፡ ማን አለ? ብለው ነው የሚሄዱት፡፡ የራሴ የሚሉትን ሰው ነው ፈልገው የሚሄዱት፡፡ ይኼ በአብዛኛው የሚመዘነው በዘር ማንነትና በፖለቲካ አመለካከት መቀራረብ ነው፡፡ ይኼ ዜጎች በእኩል ዓይን የማይታዩበትን ሁኔታ ፈጥሯል፡፡ እኛና እነሱ የሚል አስተሳሰብ በየመንግሥት ተዋረድ ባሉ መዋቅሮች ውስጥ ተፈጥሯል፡፡ በዚህ ምክንያት በተለይ በገጠር ወደ መንግሥት መዋቅር የሚመጣው ትምህርትና እርሻ ጠል የሆነው የኅብረተሰብ ክፍል ነው፡፡ በከተማም አብዛኛው ወደ መንግሥት መዋቅር ገብቶ ሲሠራ የምናየው ሰው መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች ውስጥ ተቀጥሮ መሥራት የማይችል፣ ወይም በግሉ ካፒታል ኖሮት መነገድ የማይችል፣ ወይም በግሉ ክፍለ ኢኮኖሚ መሥራት የማይችል ሰው ነው፡፡ እዚያ ውስጥ የሚገባው ለኑሮዬ የሚበቃ ጥቅምና ደመወዝ አገኛለሁ ብሎ ሳይሆን የሕግና የአሠራር ክፍተቶችን ተጠቅሜ ከኅብረተሰቡ ጉቦና የተለየ ጥቅም ተቀብሎ ኑሮዬን እደጉማለሁ ብሎ ነው፡፡ ሥርዓቱ የራሱን የፖለቲካ የበላይነት ለማስጠበቅ ታማኝ የሆነ፣ ጥያቄ የማይጠይቅና ታዛዥ የሆነ ቢሮክራሲ ነው መሰብሰብ የሚፈልገው፡፡ መንግሥት ይህን ችግር ለመዋጋት የሚያደርገው ጥረት ሁሉ በራሱ መዋቅር ተሸናፊ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ራሱን በራሱ ነው የሚታገለው፡፡

ሪፖርተር፡- አንዳንድ የፌዴራሊዝም ምሁራን ግን ማንነትን መሠረት ያደረገ የፌዴራል ሥርዓት አቅምን መሠረት ያደረገ ቢሮክራሲ ለማዋቀር ችግር እንደማይፈጥር ይከራከራሉ፡፡ የብሔር ተዋፅኦው እንዳለ ሆኖ በእዚያው ብሔር አባላት መካከል አቅምን መሠረት ያደረገ ምልመላ ማድረግ ይቻላል ሲሉም ይጠቁማሉ፡፡ እርስዎ በዚህ ይስማማሉ?

አቶ ልደቱ፡- ይኼ አስተሳሰብ ችግር ውስጥ የሚገባው በክልሎች ደረጃ ነው፡፡ ለምሳሌ በአማራ ክልል በየቢሮክራሲው ተቀምጦ የመልካም አስተዳደር ችግር እየፈጠረ ያለው ከሌላ ብሔር የመጣው ሳይሆን ራሱ አማራው ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በፌዴራል መንግሥት ደረጃስ?

አቶ ልደቱ፡- ችግሩ ሕዝቡን በማማረር ላይ ያለው በፌዴራል ደረጃ ነው? ከሕዝቡ የዕለት ተዕለት ኑሮ ጋር የተገናኘው ችግር እየተፈጸመ ያለው በክልሎች ደረጃና ከሕዝቡ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ባለው ቢሮክራሲ ነው፡፡ እላይ ያሉት ችግራቸው ተገቢ የሆነ የአሠራር ሥልት ዘርግተው ይህ የመልካም አስተዳደር ችግር መጀመሪያውኑ እንዳይስፋፋ አላደረጉም፡፡ መስፋፋት ሲጀምር ደግሞ በአጭሩ እንዲቀጭ ዕርምጃ አልወሰዱም፡፡ የአመራር ሚናቸውን በአግባቡ ባለመጫወታቸው ጉዳዩ አገራዊ ችግር እንዲሆን አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡ አለበለዚያ በራስህ ተወላጅ ስለተመራህ ብቻ ችግሩ አይቀረፍም፡፡ ለእኔ የብሔረሰቦችን መብት እያከበሩ ግን ደግሞ የአስተዳደር ሥራን በአቅም መሠረት እንዲያዝ ማድረግ የሚጋጭ ነገር አይደለም፡፡ ችግሩ የፖለቲካ ድርጅቶቹ ወደ ቢሮክራሲው እንዲመጣ የሚመለምሉት ሰው በብሔር ብቻ አይደለም በፖለቲካ ወገንተኝነትም ነው፡፡ በኦሮሚያ የኦሕዴድ፣ የኦነግ ወይም የኦፌኮ ደጋፊ የሆነ ሰው አለ፡፡ ሦስቱም ኦሮሞዎች ናቸው፡፡ ወደ ቢሮክራሲው አንድ ሰው የሚመጣው በኦሮሞነቱ ብቻ አይደለም፡፡ በኦሕዴድ ደጋፊነቱ ነው የሚያመጡት፡፡ ነገር ግን ተገቢ የሆነ ሕግና ሥርዓት አስቀምጠህ ኃላፊነቱን በአግባቡ እስከተወጣ ድረስ የኦፌኮን አባል ቢሮክራሲው ውስጥ እንዲሠራ ብታደርገው ችግር የለውም፡፡ ፌዴራሊዝም ተግባር ላይ የሚውለው መብትን ለማክበር ብቻ አይደለም፡፡ የኢኮኖሚ ልማትን ለማሳደግና አስተዳደራዊ ፍትሕንም ለማምጣት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፌዴራሊዝም ጥቅም ላይ የዋለው በዋነኛነት አለ ተብሎ የታመነውን የብሔር ጭቆና የመፍቻ መሣሪያ ሆኖ ነው፡፡ ፌዴራሊዝም የመጣው ከዚህ ጥያቄ በፊት ነው፡፡ ስለዚህ በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ፌዴራሊዝም ሊፈታቸው የሚችላቸውን ሌሎች ጥያቄዎች ማስተናገድ አልተቻለም፡፡ ለምሳሌ የአስተዳደር አመችነትና የኢኮኖሚ ልማት ጉዳይ ከፍተኛ የሆነ ትኩረት ማግኘት ነበረባቸው፡፡ የብሔር ጥያቄም ስለመመለሱ አጠያያቂ ነው፡፡ ለምሳሌ በኦሮሚያ ከፍተኛ የሆነ የመብት ጥያቅ ይነሳል፡፡ በክልሉ ግን የፌዴራል አደረጃጀት ተግባራዊ ሆኗል፡፡ ክልሉን የሚያስተዳድሩት የኦሮሞ ብሔር አባላት ናቸው፡፡ ችግሩን ግን ፈቱት ወይ? አልፈቱትም፡፡

ሪፖርተር፡- ከአመራር ዘይቤ አንፃር ኢትዮጵያ ከአቶ መለስ ሕልፈተ ሕይወት በኋላ መሠረታዊ ለውጥ አሳይታለች ብለው ያስባሉ?

አቶ ልደቱ፡- አቶ መለስ ካረፉ በኋላ በእርግጥም ለውጥ አለ፡፡ ምን ዓይነት ለውጥ ነው ያለው የሚለው እንደየአስተሳሰባችን ሊለያይ ይችላል፡፡ በእኔ በኩል ከአቶ መለስ ሞት በኋላ ከፍተኛ የሆነ የአመራር ክፍተት አያለሁ፡፡ አጠቃላይ የኃይል ማዕከሉ የት እንደሆነ የጠፋበት ሁኔታ ነው የተፈጠረው፡፡ ይኼ ስሜት የሚሰማው ከኢሕአዴግ ውጪ ለሆነው ሰዎች ብቻ አይመስለኝም፡፡ ኢሕአዴግም ውስጥ ራሱ ይኼ ግልጽ ያልሆነላቸው ሰዎች ያሉ ይመስለኛል፡፡ አቶ መለስ እያሉ በተለይም ከሕወሓት መከፋፈል በኋላ የፖለቲካ ሥልጣኑ ተጠቃሎ ሊባል በሚችል መጠን በእሳቸው እጅ ነበር፡፡ ከእሳቸው መሞት በኋላ በግለሰብ ደረጃ ያንን ሚና የተካ ሰው የለም፡፡ በቡድን ደረጃ ያ የኃይል ሚዛን ማን ላይ ነው ያለው የሚለው ግልጽ ሳይሆን የቀጠለ ነው፡፡ አሁን ኢሕአዴግ ሥልጣኑን እያጠናከረ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ያ ሒደት አልቆ ሥልጣን በአንድ ግለሰብ ወይም ቡድን በግልጽ ተይዞ አይታይም፡፡ ስለዚህ አንዳንድ ጊዜ መመርያዎች፣ ትዕዛዞችና ውሳኔዎች ከየት አቅጣጫ እንደሚመጡ ለማወቅ አስቸጋሪ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በይፋ መንግሥት አራምዳለሁ የሚለው አቋም ሌላ ነው፣ መሬት ላይ በተግባር ሲተረጎም የሚታየው ደግሞ ሌላ ነው፡፡ በድርጅቱ ውስጥ ግጭቶች ተፈጥረው በሒደት አንድ ግለሰብ ወይም ቡድን አሸናፊ ሆኖ መውጣት አለበት፡፡ እንደዚያ ዓይነት ሒደት አሁን ኢሕአዴግ ውስጥ የተፈጠረ አልመሰለኝም፡፡ የሚፈጠርበት አዝማሚያ ግን ያለ ይመስለኛል፡፡ ሌላው ለውጥ በተለይ በቅርቡ በአገሪቱ በተፈጠሩ ችግሮች እየጎላ የመጣው ጉዳይ በኢሕአዴግ ዘንድ አንድን ውሳኔ በደንብ ሳያጤኑ ወስኖ፣ ነገር ግን የሕዝብ ተቀባይነት ሲያጣ ወዲያው የመቀልበስ አሠራር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ የውሳኔው ትክክለኛነት ላይ ማተኮር ሳይሆን ሕዝቡ ለውሳኔው ያለው አመለካከት ላይ የማተኮር አዝማሚያ ይታያል፡፡ ለዚህ እንደ አብነት በኦሮሚያ ማስተር ፕላንና በቅርቡ ደግሞ ከታክሲ ሾፌሮች ጋር በተያያዘ የተወሰኑትን ውሳኔዎች መጥቀስ ይቻላል፡፡ ውሳኔ ወስኖ ተግባራዊ የማድረግ አቅም እያጣ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በቅርቡ በፓርላማ ባደረጉት ቆይታ የማንነት ጥያቄዎች ኢትዮጵያ ውስጥ ተመልሰው አልቀዋል ብለዋል፡፡ ይኼ እንደ መሠረታዊ ለውጥ ሊወሰድ አይችልም?

አቶ ልደቱ፡- የጠቅላይ ሚኒስትሩን የፓርላማ ንግግር ተከታትየዋለሁ፡፡ እውነቱን ለመናገር ስሰማው ደንግጫለሁ፡፡ በእውነት ታስቦበት የተነገረ ንግግር ነው ወይስ በድንገት በስሜት የተነገረ ንግግር ነው የሚለውን እስካሁን መለየት አልቻልኩም፡፡ ታስቦበት የተነገረ ንግግር ከሆነ በጣም አከራካሪ ይመስለኛል፡፡ እኔ እስከሚገባኝ ድረስ ሕገ መንግሥቱ ከዚህ በኋላ የብሔር ብሔረሰቦች ችግር ተፈቷል አላለም፡፡ የሚፈታበትን አካሄድ አስቀምጧል፡፡ ሁለተኛ የማንነት ጥያቄ አንድ ወቅት ላይ ተነስቶ አንድ ወቅት ላይ ሙሉ በሙሉ ተፈቷል የሚባል አይደለም፡፡ በመቼውም ሁኔታና ጊዜ ሊከሰት ይችላል፡፡ ሕገ መንግሥቱ ያን የመፍቻ መሣሪያ ነው የሚሆነው፡፡ የማንነት ጥያቄ በውሳኔ ከዚህ በኋላ ተዘግቷል ሊባል አይችልም፡፡ አንዱ መጀመሪያም ሕገ መንግሥቱ ሲረቀቅና የፌዴራል ሥርዓቱ ሲዋቀር ግምት ውስጥ መግባት የነበረበት ይኼ ነው፡፡ የማንነት ጥያቄ አንድ ጊዜ ከቋንቋና ከብሔረሰብ ማንነት ጋር ከተያያዘ ማቆሚያ የሌለው እንደሆነ ግምት ውስጥ መግባት ነበረበት፡፡ ስለዚህ ይኼ ውሳኔ ራሱን ሕገ መንግሥቱን የሚቃረን ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም አስበውበት ተናገሩ ብዬ አላምንም፡፡ አስበውበት የተናገሩ ከሆነና ከጀርባም የድርጅታቸው ውሳኔ ከሆነ ይኼ ትልቅ ለውጥና ሽግግር ነው፡፡ በፓርላማ እንደ ቀልድ ተነግሮ ብቻ መታለፍም የለበትም፡፡ ይኼ ለውጥ ለአገር ይጠቅማል ወይስ አይጠቅምም የሚለው ለውይይት ቀርቦ ሁላችንም ሐሳብ መስጠት ያለብን ይመስለኛል፡፡ ይኼ ኢሕአዴግን እንደገና የመፍጠር ጥያቄ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በቅርቡ ከዘመን መጽሔት ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የኢትዮጵያ ቢሮክራሲ መንግሥት ሊቋቋመው ያልቻለና መንግሥትን የማይፈራ ነው ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል ቢሮክራሲው ታማኝና ታዛዥ ነው እያሉ ነው፡፡ ይኼ እርስ በርሱ አይጋጭም?

አቶ ልደቱ፡- አይጋጭም፡፡ ሥርዓቱ ቢሮክራሲውን ሲያሰባስብ የራሴ የሚለው ጥቅም እንዲያገኝ ፈልጎ አይደለም፡፡ መንግሥት የራሴ የሚለው የፖለቲካ ጥቅም ስላለው ነው፡፡ እኔን የሚመስል፣ የእኔን አስተሳሰብ የሚደግፍና ለእኔ ታማኝ የሆነ ቢሮክራሲ አሰባስቤ የፖለቲካ የበላይነቴን አስጠብቄ እቀጥላለሁ ብሎ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ዓይነት ሠራዊት ሲፈጥር ነገ ከነገ ወዲያ የራሱን ጥያቄ ይዞ ሊመጣ እንደሚችል ማሰብ ነበረበት፡፡ የኢኮኖሚ ጥቅም መፈለግ የሚጀምረው ኋላ ላይ ነው፡፡ አሁን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሙስናው ተመጋጋቢ ሆነዋል፡፡ ተቃራኒ በመሆናቸው ጦርነት ውስጥ ናቸው፡፡ አንድ ሰው ሙስና ውስጥ የሚገባው ደሃ ስለሆነ አይደለም፡፡ ይበልጥ ሙስና ውስጥ የሚገባው ሙስናውን ማጣጣም ከጀመረ በኋላ ነው፡፡ ከሥር ከመሠረቱ የመልካም አስተዳደር ችግርን ነቅሎ የሚጥል ዘመቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡ ችግሩ መዋቅራዊ መሆኑን አምኖ መቀበል ይጠይቃል፡፡ በለብ ለብ ዘመቻ አሸናፊ የሚሆነው ቢሮክራሲው ነው፡፡ ከዚህ ቀደም መቀጣጫ እንዲሆኑ የተወሰኑ ሰዎች ሲታሰሩ አይተናል፡፡ ችግሩ ግን አልተፈታም፡፡ የቢሮክራሲው ኃይል አሁን ገዝፏል፡፡ ቢሮክራሲውና ሙስና አሁን አንድ ሆነዋል፡፡ ሙስናን ብታቆም ቢሮክራሲው በደመወዝ ብቻ ሊተዳደር አይችልም፡፡ ጥሎት ስለሚወጣ መንግሥት ተንገራግጮ ይቆማል፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ችግር ለመፍታት አንደኛ ሁሉን አቀፍ የሆነ መፍትሔ መፈለግ አለብህ፡፡ ዋናው የፖለቲካ መፍትሔ ነው፡፡ ቀጥሎ ደግሞ ይኼ ቢሮክራሲ ራሱን፣ ቤተሰቦቹን፣ ልጆቹን የሚያስተምርበትና የሚመግብበት ደመወዝና ጥቅማ ጥቅም እንዲያገኝ ማድረግ አለብህ፡፡ የሥርዓቱ አብዛኛው አካል ተበክሏል፡፡ ይኼን አካል ቆርጦ መጣል ቀላል ውሳኔ አይደለም፡፡ ግን ደግሞ አማራጭ የለም፡፡ ይኼንን የተገነዘቡ የኢሕአዴግ አመራሮች ያሉ ይመስለኛል፡፡ ነገር ግን ከችግሩ ጋር ደግሞ እጅና ጓንት የሆኑና የተያያዙ አካላት አሉ፡፡ አንዳንዳቹ እኮ የኢሕአዴግ ድርጅቶች በትክክል በሙስና የተዘፈቀ ሰው ሁሉ ይጠየቅ ቢባል ድርጅቶቹ እንደ ድርጅት ሊፈርሱ ይችላሉ፡፡ የሚያስከትለው የፖለቲካ ጣጣ ሊኖር ይችላል፡፡ ግን ደግሞ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ግን ይጠይቃል፡፡

ሪፖርተር፡- በኢሕአዴግ ዲስኩር ውስጥ ፓርቲው ራሱን የሚያስተዋውቀው ለሕዝብ ጥቅም የሚኖሩና ለዚህ ዓላማ መስዋዕት ለመሆን ዝግጁ በሆኑ አባላት እንደተሞላና ጥቂት ከዓላማው ውጪ የሚሠሩ አባላትን የማክሰም ብቃት እንዳለው ነው፡፡ በሌላ በኩል ሙስናን ለመዋጋት ከአስተዳደራዊና ከሕጋዊ ዕርምጃዎች ይልቅ ፖለቲካዊ መፍትሔዎች በቅድሚያ መወሰድ እንዳለበት የመንግሥት የፖሊሲ ሰነዶች ይጠቁማሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች አብረው የሚሄዱ ናቸው?

አቶ ልደቱ፡- ሁለቱም የመፍትሔው አካል ናቸው፡፡ ተቀናጅተው ተግባራዊ መሆን አለባቸው፡፡ ኢሕአዴግ የሚታገለው አንደኛውን ነጥሎ ለመፈጸም ነው፡፡ ነገር ግን በኢሕአዴግ ዙሪያ የተሰባሰበው በትክክል የአገር ፍቅር ያለውና ለሕዝብ አገልግሎት ጊዜውን፣ ጉልበቱንና ዕውቀቱን መስዋዕት ለማድረግ የተሰባሰበ ኃይል ነው ወይ? በዚህ መንፈስ ወደ ኢሕአዴግ የተቀላቀሉ ሰዎች የሉም ልል አልችልም፡፡ በተለይ በትጥቅ ትግሉ ወቅት ይኼን ዓይነት አመለካከት ይዘው የገቡ ሰዎች አሉ ብዬ አምናለሁ፡፡ ግን አሁን ይኼ ሥርዓት በሥልጣን ላይ ከ20 በላይ ዓመታት ከቆየ በኋላ በዙሪያው ያሰባሰባቸው ኃይሎች እነማን ናቸው የሚለውን ካየን ግን በትክክል ለሕዝብ አገልግሎት የቆሙ አይደሉም፡፡ ያለ ምንም ማጋነን ከ95 በመቶ በላይ የሆነው ኅብረተሰብ ለዚያ ብሎ የተሰባሰበ አይደለም፡፡ ከአምስት ወይም ከስድስት ዓመታት በፊት ኢትዮጵያ ውስጥ የነበረው የሙስና መጠን በጣም ዝቅተኛ ነበር፡፡ አሁን ለማመን በሚከብድ መጠን ጨምሯል፡፡

ሪፖርተር፡- ከቀድሞ መንግሥታት በተቃራኒ ኢሕአዴግ የዘረጋሁት የአስተዳደር መዋቅር 1 ለ 5ን ጨምሮ በእያንዳንዱ ቤት የሚደርስ ነው በማለት በኩራት ይገልጻል፡፡ ከዚህ አንፃር ይህን ለአገሪቱ ህልውና የሚያሰጋ ችግር እስካሁን እንዴት ሳይገነዘበው ቀረ?

አቶ ልደቱ፡- ችግሩን ከተገነዘበው ቆይቷል፡፡ በመሠረቱ ኢሕአዴግ ሥልጣን ከያዘ ጀምሮ የመዋቅር ማሻሻያ ያልተሞከረበት ጊዜ የለም፡፡ ከፍተኛ የሆነ የመልካም አስተዳደር ችግር አለ የተባለው ዛሬ አይደለም፡፡ በሌላው አገር አንድ ችግር ተፈጠረ ብሎ ከሥልጣን የሚለቅ ሚኒስትር የተለመደ ነው፡፡ መንግሥት በአግባቡ ሥራዬን አልተወጣሁም ብሎ ሲያስብ የመተማመኛ ድምፅ ይጠይቃል፣ ሕዝበ ውሳኔ ያደርጋል፡፡ ይኼ የሚያሳየው ችግሩ ከፍተኛ ከሆነ የፖለቲካ ህልውናህን ሊፈታተን እንደሚችል ነው፡፡ ኢሕአዴግ ግን የራሱን የፖለቲካ የበላይነት አስጠብቆ ነው ችግሮችን መፍታት የሚፈልገው፡፡ የፖለቲካ ህልውናውን የሚነካኩ ከሆነ ሊነካቸው አይፈልግም፡፡

ሪፖርተር፡- ኢሕአዴግ የመልካም አስተዳደር ችግርን ለመቅረፍ የተለያዩ ዕርምጃዎችን እንደሚወስድ ሲገልጽ ቆይቷል፡፡ ለዚህ የዴሞክራሲ ተቋማት የሚባሉት እንደ ፓርላማ፣ ፀረ ሙስና ኮሚሽን፣ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን፣ እንባ ጠባቂ ተቋምና ሚዲያ የራሳቸው ሚና እንደሚኖራቸው ተገልጿል፡፡ እስካሁን የተወሰዱትን ዕርምጃዎችና የተቋማቱን ሚና እንዴት ያዩታል?

አቶ ልደቱ፡- ይኼን ችግር በብቃት ለመዋጋት ነፃ የሆኑ ተቋማት ያስፈልጉ ነበር፡፡ ነገር ግን እነዚህ ተቋማት የተፈጠሩት የፖለቲካ ወገንተኝነት ባላቸው ወገኖች ነው፡፡ ነፃ ሆነው ሥርዓቱ አቅጣጫ ሲስት የሚገዳደሩና የሚጠይቁ ሰዎች አይደሉም በተቋማቱ የተሰባሰቡት፡፡ የፖለቲካ ታማኝነት መመዘኛ ሆኖ የሥርዓቱ ደጋፊና ታማኝ የሆኑ ሰዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ተቋማቱ አሁን ነፃነት አላቸው ማለት አይቻልም፡፡ በሥርዓቱ ውስጥ ያለውን ችግር ታግሎ ለመፍታት የሚያግዝ ጉልበት አላቸው ማለት አይቻልም፡፡ መንግሥትን ከጥቃት የሚከላከሉ ናቸው፡፡ የእኔ ጠላት ናቸው የሚላቸውን አካላት እንዲያጠቁለት የተቋቋሙ ናቸው፡፡ ስለዚህ ጥርስ የሌለው አንበሳ ሆነዋል፡፡ ፀረ ሙስና ኮሚሽን ከተቋቋመ በኋላ ሙስና እየጨመረ ነው የመጣው፡፡ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ከተቋቋመ በኋላ የኅብረተሰቡ የሰብዓዊ መብት ችግር የበለጠ እየተባባሰ ነው የመጣው፡፡

ሪፖርተር፡- ባለፈው ግንቦት ወር በተካሄደው ጠቅላላ ምርጫ መቶ በመቶ ያሸነፈው ገዥው ፓርቲ፣ በጥቂት ወራት ልዩነት ውስጥ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ተቃውሞ ሲነሳበት እንዴት አዩት?

አቶ ልደቱ፡- ኢሕአዴግ መቶ ፐርሰንት እንዳሸነፈ በምርጫ ቦርድ ሲነገረው መደሰት ሳይሆን መደንገጥ ነው የነበረበት፡፡ ምክንያቱም የተለያየ የፖለቲካ አስተሳሰብና የፖለቲካ ቅራኔ ባለበት አገር አንድ ፓርቲ በብቸኝነት ከቀበሌ እስከ ፓርላማ ያለውን መዋቅር መቶ በመቶ አሸንፎ የሚይዝበት ሁኔታ የለም፡፡ መቶ በመቶ አሸንፏል ከተባለ በኋላ እንደዚህ ዓይነት በጣም ከፍተኛ የሆነ የኅብረተሰብ ብሶቶችና ግጭቶች መፈጠራቸው የምርጫው ውጤቱ በፍፁም ነባራዊ ሁኔታውን የማይገልጽ መሆኑን ነው የሚያሳየው፡፡ ኢሕአዴግ ቆም ብሎ ማሰብ ያለበት አሁን ነው፡፡ መቶ ፐርሰንት የምርጫ ውጤት የሚያሳየው በኢትዮጵያ ውስጥ የሐሳብ ብዝኃነት ቦታ ማጣቱን ነው፡፡ ብዝኃነት የሚገለጸው በቋንቋ፣ በሃይማኖትና በብሔረሰብ ማንነት ብቻ አይደለም፡፡ እንዲያውም በዋናነት ብዝኃነት የሚገለጸው በአስተሳሰብ ነው፡፡ በኢትዮጵያ እየነገረና እየተሳበበ ያለው፣ በተግባር እየዋለ ያለው የአንድ ፓርቲ ብቸኛ አስተሳሰብ ነው፡፡ ሌሎች አስተሳሰቦች ተደፍቀዋል፡፡ ኅብረተሰቡ ብሶቱን፣ ተቃውሞውንና ቅሬታውን የሚገልጽበት መድረክ አጥቷል፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በተፈጠረበት አገር አሁን የምናያቸው ዓይነት አላስፈላጊ የሆኑ ግጭቶች መከሰታቸው ተፈጥሯዊ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ደረጃና በማንፈልገው መጠን በአገሪቱ ውስጥ ግጭቶች እየታዩ ያሉት በዋናነት የአስተሳሰብ ብዝኃነት በመታፈኑ ነው፡፡ መንግሥት ሁለት ወዶ ሊሆን አይችልም፡፡ በአንድ በኩል ሰላማዊ መድረኩን ሙሉ በሙሉ ዘግቶ፣ በሌላ በኩል ደግሞ አመፅን መዝጋት አይቻልም፡፡ የአመፅን መንገድ መዝጋት የሚቻለው ሰላማዊ መድረኩን በመክፈት ነው፡፡ አሁን ባለንበት ተጨባጭ ሁኔታ ቁልፉ ጥያቄ የአስተሳሰብ ብዝኃነት አለመከበር ነው፡፡ በቅርቡ ትልቅ ችግር ውስጥ የገቡት እንደነ ግብፅ፣ ሊቢያና ሶሪያ ያሉ አገሮች ራሳቸውን ለረጅም ዓመታት ከለውጥ አርቀው ነበር፡፡ የአስተሳሰብ ብዝኃነትን ማስተናገድ አቅቷቸው ነው መጨረሻ ላይ ወደማይፈለግ ግጭትና ብጥብጥ የገቡት፡፡ ይኼ ችግር የማይፈታ ከሆነ የኢትዮጵያም ዕጣ ፈንታ ወደዚያ ነው የሚያመራው፡፡

ሪፖርተር፡- በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች የተቃውሞ እንቅስቃሴ መጀመሪያ ሲነሳ መንግሥት የውጭ ፀረ ሰላምና ፀረ ልማት ኃይሎች እጅ ነው ብሎ ነበር፡፡ አሁን ግን ችግሩ በዋነኛነት በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያሉ ሰዎች እንደሆነና እነዚህ ኃይሎች የማቀጣጠል ሚና መጫወታቸውን የሚገልጽ ነው፡፡ በእርስዎ ግምገማ የውስጣዊና የውጫዊ ምክንያቶች ድርሻ እንዴት ይገለጻል?

አቶ ልደቱ፡- በዋናነት ችግሩ የተፈጠረው ውስጥ ባለው ሁኔታ ነው፡፡ ሕዝቡ ውስጥ ባለ ተጨባጭ ብሶት ነው፡፡ ነገር ግን የዚህን ጉዳይ መገለጫዎች ስናይ ብቻውን የቆመ ነው ማለት አይቻልም፡፡ እነዚህን ብሶቶች ከጀርባ ሆነው ለራሳቸው የፖለቲካ አጀንዳ የሚጠቀሙባቸው የውጭ ኃይሎች የሉም ማለት አይቻልም፡፡ ግን እነዚህ ኃይሎች ይህን ዕድል ያገኙት የውስጡን ችግር በአግባቡ፣ በተገቢው ጊዜና ሁኔታ ለመፍታት ስላልተቻለ ነው፡፡ መነሻው ግን የአገር ውስጡ ችግር ነው፡፡ የውጭ ኃይሉ የተመቸ ሁኔታ አግኝቶ ይህችን አገር ወደ መጥፎ አቅጣጫ እንዳያስገባት መፍትሔው ማውገዝና ፕሮፖጋንዳ አይደለም፡፡ መፍትሔው ውስጥ ላለው ኅብረተሰብ ብሶት መነሻ የሆነውን ችግር ከምንጩ ማድረቅ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- ኢሕአዴግ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የጥቂቶችን ጥቅም ለማስከበር የቆሙና የሕዝብ ፍላጎትን መሠረት አድርገው የማይሠሩ ናቸው ሲል ሁሌም ይተቻል፡፡ በቅርቡ በተከሰተው የተቃውሞ እንቅስቃሴም አንዳንድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የውጭ ኃይሎችን አጀንዳ ለማስፈጸም ተንቀሳቅሰዋል ሲል ከሷል፡፡ ችግር ላይ ያለችውን ኢትዮጵያን ለመታደግ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ምን ሚና ሊጫወቱ ይገባል?

አቶ ልደቱ፡- የፖለቲካ ፓርቲዎች የማይተካ ሚና አላቸው፡፡ መንግሥት ዝም ብሎ በአገሪቱ ውስጥ ያሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጅምላ አጀንዳ የለሽ አድርጎ ከማየት፣ ፀረ ሕዝብና ፀረ ልማት አድርጎ ከማየት የተለየ አመለካከት ያላቸው የፖለቲካ ኃይሎች አሉ ብሎ መውሰድ የተሻለ ነው፡፡ እነዚህ ኃይሎች ደግሞ አነሰም አደገም የሚወክሉት ኅብረተሰብ መሬት ላይ አለ ማለት የተሻለ ነው፡፡ ይህን ኃይል የሚያስተናግድ ሥርዓት መገንባት ግድ ነው፡፡ ኢሕአዴግ አማራጭ እኔ ብቻ ነኝ ብሎ የትም ሊሄድ አይችልም፡፡ የተለያዩ የኅብረተሰቡን ፍላጎት የሚወክሉ የፖለቲካ ድርጅቶች ያስፈልጋሉ፡፡ እነዚህ ኃይሎች የሚወከሉበት መድረክ ያስፈልጋል፡፡ በፖሊሲ ውሳኔና በሕግ ማውጣት ጉዳይ ላይ ትርጉም ያለው ተሳትፎ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ በሌላ በኩል ተቃዋሚዎች እስካሁን የሄዱበትን አስተሳሰብ መፈተሽ አለባቸው፡፡ አካሄዳቸውን ማስተካከል አለባቸው፡፡ በሰሞኑ ግርግር እንኳን ስናይ ግርግሩ ወዴት ያደርሰናል? የግርግሩ መነሻ ምንድነው? ተጠያቂው ማነው? ብለው ሳይገመግሙ የተፈጠረውን ችግር ሁሉ ለማባባስና በዚህ ግርግር የመንግሥት ለውጥ እንዲመጣ ሲጠብቁ አይተናል፡፡ ይኼ ስህተት ነው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሰከን ብለው አጀንዳቸውን ከሕዝብና ከአገር ጥቅም ጋር አያይዘው መንቀሳቀስ አለባቸው፡፡ እንቅስቃሴያቸውም ሰላማዊና ሕጋዊ መሆን አለበት፡፡ መንግሥትንም በምክንያት መተቸት አለባቸው፡፡ አስተሳሰባቸው ከመንግሥት ለውጥ ጋር ሁልጊዜ መንጠልጠል የለበትም፡፡ ተጨባጭ የሆነ የፖሊሲ አማራጭ ይዘው ቀርበው መንግሥት የመሆን ዕድል እንኳን ባያገኙ፣ በመንግሥት ላይ ትርጉም ያለው ተፅዕኖ አሳድረው የፖሊሲ ለውጥ ማሻሻያ እንዲመጣ ማድረግ አለባቸው፡፡ የዚህ ዓይነት ባህል ካላቸው ብቻ ነው በሒደት በኅብረተሰቡ ውስጥ ተቀባይነት እያገኙና እምነት እያገኙ ወደ መንግሥትነት ደረጃ የሚበቁት፡፡

ሪፖርተር፡- ፓርቲዎ ኢዴፓ አላምደዋለሁ የሚለውን የሊበራል አስተሳሰብ ለጥቂቶች ጥቅም የቆመና ኢትዮጵያዊ መሠረት የሌለው አድርጎ ገዥው ፓርቲ ያቀርበዋል፡፡ ይህን አቀራረብ እናንተ እንዴት ነው የምታዩት?

አቶ ልደቱ፡- የግራ ፖለቲካ አስተሳሰብ ኢትዮጵያ ውስጥ ማቆጥቆጥ ከጀመረበት ካለፉት 50 ዓመታት ወዲህ የሊበራል አስተሳሰብ ቦታ እያጣ ነው የመጣው፡፡ በጣም ፅንፈኛ የሆነ ወይ ከእኔ ነህ ወይ ከእነሱ ነህ የሚል የፖለቲካ ባህል ነው የሰፈነው፡፡ ነገሮችን ከተለያየ አቅጣጫ አይቶ ሚዛናዊ አስተሳሰብ መያዝ ነውር እየሆነ የመጣበት ባህል ነው የተስፋፋው፡፡ ገዥው ፓርቲ የግራ ፖለቲካ ውጤት ነው፡፡ የሊበራል አስተሳሰብ በዓለም ገዥ የሆነ አስተሳሰብ ነው፡፡ ዛሬ የምንቀናባቸውና ዕርዳታ እንዲሰጡን የምንለምናቸው የሊበራል አስተሳሰብ የሚያራምዱ ናቸው፡፡ የሊበራል አስተሳሰብ በኢትዮጵያ ውስጥ ሕዝባዊ መሠረት እንዳለው ወይም እንደሌለው ሊረጋገጥ የሚችለው ነፃና ፍትሐዊ ምርጫ ስታካሂድ ብቻ ነው፡፡ የሊበራል አስተሳሰብ የሚያራምድን አካል እንደ ሕዝብ ጠላት ፈርጀህ፣ መድረክ አሳጥተኸው፣ አምቀኸው፣ ሐሳቡን ለኅብረተሰቡ እንዳይሸጥ አድርገህ አይጠቅምም ማለት ዋጋ የለውም፡፡ ሁለተኛ አሁን ባለው የኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ የሊበራል አስተሳሰብ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ይሆናል ብለን አናምንም፡፡ የሊበራል አስተሳሰብ በሩቅ ግብ እንደርስበታለን ብለን የምናምንበት ነው፡፡ በሒደት የሚመጣ ነው፡፡ ነገር ግን እዚያ ለመድረስ ከአሁኑ ነገሮች መጀመር አለባቸው፡፡ ገዥው ፓርቲ ኢዴፓ የሚያነሳውን ሐሳብ ሁሌም ሲያጥላላ ነው የኖረው፡፡ ነገር ግን ይኼ ስህተት እንደሆነ የሚያሳዩ ከወቅታዊ የአገራችን ሁኔታ ጋር የተያያዙ ሦስት ምሳሌዎችን ላንሳልህ፡፡ ከኢኮኖሚ አንፃር ደግመን ደጋግመን ስንናገር የነበረው መሠረታዊ የሆነ መዋቅራዊ ሽግግር በኢኮኖሚያችን ካልተፈጠረና በአስቸኳይ ከእርሻ ጥገኝነት ራሳችንን ካላወጣን ያለው ኢኮኖሚ ዝናብ ቀጥ ቢል ችግር ውስጥ እንደሚገባ ነበር፡፡ ዘንድሮ የታየው ይኼ አገር አሁንም በምግብ እህል እንኳን ራሱን እንዳልቻለ ነው፡፡ ሁለተኛ ፌዴራሊዝም የአገሪቱን የብሔር ብሔረሰቦች ጥያቄ ፈቷል፣ ከዚህ በኋላ አንድነታችን የበለጠ ጠንክሯል ተብሎ ሲነገር ነበር፡፡ እኛ ስንል የነበረው ይኼ የፌዴራሊዝም አደረጃጀት በዋናነት ትኩረት ያደረገው ልዩነት ላይ ስለሆነ በሒደት የኅብረተሰቡን አንድነት እያላላው እንደሚመጣ ነበር፡፡ ግጭት እያዳበረ፣ ጤናማ ያልሆነ ፉክክርን ያዳብራል ነው ስንል የነበረው፡፡ አሁን መንግሥት እያስተናገደ ያለው ምንድነው? በብዙ የአገሪቱ አካባቢዎች በታሪክ አይተነው የማናውቀው ግጭት ነው የተከሰተው፡፡ ሦስተኛ ከመሬት ጥያቄ ጋር በተያያዘ መሬት በመንግሥት እጅ መያዙ ለኅብረተሰቡ ነው የሚጠቅመው ሲባል ነበር፡፡ በኦሮሚያ ተቃውሞ ገበሬው እያነሳ ያለው ጥያቄ ምንድነው? መንግሥት ያላግባብ መሬታችንን እየነጠቀና እየሸጠ እሱ እየከበረ እኛ ግን እየደኸየን ነው በሚል ነው ተቃውሞውን ያቀረበው፡፡ እኛ ስንከራከር የነበረው የመሬቱ ባለቤት የሕዝቡ እንዲሆን ነው፡፡ ገበሬው በመሬቱ ላይ የመሸጥ፣ የመለወጥ፣ የማከራየት መብት ኖሮት ጥቅም ያግኝ እያልን ነው ስንከራከር የነበረው፡፡ ስለዚህ ስናነሳቸው የነበሩ ችግሮች ሁሉ አሁን ችግር መሆናቸው ጎልቶ እየታየ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በኦሮሚያ የተነሳው ተቃውሞ በተወሰነ መልኩ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ከምታገኘው ልዩ ጥቅም ጋር ተያይዟል፡፡ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ጋር ያላት ግንኙነት በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠበትን መንገድና አተገባበሩን እንዴት ያዩታል?

አቶ ልደቱ፡- በእኛ እምነት ሕገ መንግሥቱ ብዙ ክፍተቶች አሉት፡፡ የሕገ መንግሥት ማሻሻያ ማድረግ ነውር አይደለም፡፡ 25 ዓመት ከተጓዘ በኋላ ይኼ ሕገ መንግሥት ያሉበት ክፍተቶች ምንድን ናቸው? መቀየር ያለባቸው ነገሮች አሉ ወይ? ብሎ መገምገም አለበት፡፡ አሁን ግን ሕገ መንግሥቱ እንደ መለኮታዊ ሰነድ ነው እየታየ ያለው፡፡ የአዲስ አበባና የኦሮሚያ ጉዳይ አንዱ ክፍተት ነው፡፡ በግልጽ ባለመቀመጡ ብዥታ ፈጥሯል፡፡ የጥቅም ግጭትም ፈጥሯል፡፡ ትልቅ የፖለቲካ ጉዳይም እየሆነ ነው፡፡ ለአገርና ለሕዝብ በሚጠቅም መልኩ ግልጽ መደረግ አለበት፡፡ ካስፈለገም እስከ ሕገ መንግሥታዊ ማሻሻያ ድረስ መሄድ ያስፈልጋል፡፡ ወደፊት ሊመጡ የሚችሉ ችግሮች ተጢነው አይደለም ሕገ መንግሥቱ የተረቀቀው፡፡ በወቅቱ ኢሕአዴግ ይዞት የነበረው አስተሳሰብ ነው በቀጥታ ወደ ሕገ መንግሥትነት እንዲቀየር የተደረገው፡፡ የብዙ ፓርቲዎች አስተሳሰብ ምን እንደሆነ ግንዛቤ ውስጥ ገብቶ፣ በቂ የሆነ ውይይት ተደርጎ የተዘጋጀ ሰነድ አይደለም፡፡ ሕገ መንግሥት ግን በባህርይ መሆን ያለበት እንደዚያ ነው፡፡ ይኼን በሒደት ማስተካከል አስፈላጊና ወቅታዊ ነው፡፡ ከመሬት ጥያቄ፣ ከአዲስ አበባና ኦሮሚያ ግንኙነትና የፌዴራል አደረጃጀቱ እስከ መገንጠል ጥያቄ ድረስ ጋር በተያያዘ ያለው አንድምታ በደንብ በድጋሚ መዳሰስ አለበት፡፡ አንዳንዶቹ የሕገ መንግሥት ድንጋጌዎች ኢትዮጵያን እንደ እስራኤልና ፍልስጤም ሁኔታ በሩቅ ሒደት ውስጥ የሚያስገቡ ናቸው፡፡ ወደዚያ አቅጣጫ ከመግባታችን በፊት ቆም ብለን ማሰብና የአጠቃላይ ሕዝቡን ስምምነት ያገኘ ሕገ መንግሥት ማግኘት መቻል አለብን፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ ተገቢውን ትኩረት ማግኘት አለበት፡፡ ነገር ግን አስተማማኝ በሆነ አቅጣጫ ውስጥ እንዲቀመጥ የሚያደርግ መፍትሔ መሰጠት አለበት፡፡

ምንጭ – ሪፖርተር

The post “መለስ ካረፉ በኋላ በእርግጥም ለውጥ አለ” – ልደቱ አያሌው appeared first on Zehabesha Amharic.

የማኅበረ ቅዱሳን ፭ኛው ዙር ልዩ ዐውደ ርእይ ቅድመ ዝግጅት ሒደት እውነታዎችና ቀጣይ ወቅታዊ ጥረቶች

0
0

Source: Hara Tewahido

  • በታቀደው መርሐ ግብር የማካሔድ ጥረቱ ዛሬም ተጠናክሮ ይውላል
  • ዛሬ ከቀኑ 10፡00 በዋናው ማእከል ጽ/ቤት ጋዜጣዊ መግለጫ ይሰጣል
  • የዝግጅቱ ቀጣይነት፣ ጊዜና ቦታ የሚታወቀው በሚሰጠው መግለጫ ነው

patriarchate MK Exb approval and Exb logo
ጳጉሜን 5 ቀን 2007 ዓ.ም. – የማኅበሩ የሥራ አመራር ጉባኤ ጽ/ቤት፣ ማኅበሩ በአራት ዓመት ስትራተጅያዊ ዕቅዱ ያካተተውን የዐውደ ርእይ ልዩ ዝግጅት ለሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማሳሰቡን በመጥቀስ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የድጋፍ ደብዳቤ እንዲጻፍለት ጠየቀ፤

ጳጉሜ 5 ቀን 2007 ዓ.ም. – የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ የዝግጅቱን መካሔድ ፈቅዶ፥ “ከዚኽ በፊት እንደተለመደው ኹሉ አስፈላጊው ትብብር እንዲደረግ” በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም በመጠየቅ ለኤግዚቢሽን ማዕከል እና የገበያ ልማት ድርጅት የድጋፍ ደብዳቤ ጻፈ፤

መስከረም 03 ቀን 2008 ዓ.ም. – የማኅበሩ ጽ/ቤት በዋና ጸሐፊው፣ የኤግዚቢሽን ማዕከሉ ደግሞ በዋና ሥራ አስኪያጁ አማካይነትበስድስት አንቀጾች የተዘረዘረ የአገልግሎት ውል በመፈራረም የጠቅላላ ዋጋውን 35 በመቶ ብር 200 ሺሕ ቅድመ ክፍያ ፈጸመ፤

ጥቅምት ወር 2008 ዓ.ም.፡- የ፭ኛው ዙር ልዩ ዐውደ ርእይ ዝግጅት ዐቢይ ኮሚቴ፣ በማኅበሩ የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ ተቋቋመ፤

  • ከአንድ ሺሕ በላይ የሰው ኃይል በማቀፍ በአምስት ዋና ዋና ክፍሎች (የትዕይንት ዝግጅት፤ የማስታወቂያና ቅስቀሳ፤ የሥነ ሥርዓት፣ የአዳራሽ እና የቴክኒክ አካላት) የተዋቀረው ዐቢይ ኮሚቴ፣ ጊዜያዊ ጽ/ቤቱን በዋናው ማእከል አንደኛ ፎቅ ከፍቶ የድርጊት መርሐ ግብሩን በማጸደቅ ሥራውን ጀመረ፤

ታኅሣሥ ወር 2008 ዓ.ም.፡- ዐቢይ ኮሚቴው የልዩ ዐውደ ርእዩን ዝግጅት ለብዙኃን መገናኛዎች እና እንደ ሐዊረ ሕይወት ባሉ የብዙኃን መድረኮች በሰፊው በማስተዋወቅ የመግቢያ ትኬት ሽያጭ ማካሔድ ጀመረ፤

ጥር 17 ቀን 2008 ዓ.ም.፡- ዐቢይ ኮሚቴው፥ “ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን: አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ!!” የሚለውን የዐውደ ርእዩን መሪ ቃል እና መለዮ(ሎጎ) በዋናው ማእከል ጽ/ቤት አዳራሽ ከ300 በላይ እንግዶችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ይፋ አደረገ፤

01awde r 02

ጥር እና የካቲት፤ 2008 ዓ.ም.፡- ዐቢይ ኮሚቴው፥ የማኅበሩን የሥራ አመራር እና የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ እንዲኹም የዝግጅት ኮሚቴውን አባላት ጨምሮ ፍላጎቱ ያላቸው ተሳታፊዎች ኹሉ በተገኙበት፣ በየሳምንቱ ረቡዕ ባዘጋጀው የግምገማ መድረክ፣ የአራት ትዕይንቶችንና የልዩ ክውን ጥበባት መሰናዶውን ጠቅላላ ይዘትና አቀራረብ በተደጋጋሚ በማስተቸት ዝግጅቱን አጠናቀቀ፤

መጋቢት ወር መባቻ ሳምንታት፡- ዐቢይ ኮሚቴው በአገልግሎት ውሉ መሠረት የአዳራሾች ዝግጅት እና የትዕይንት ክፍሎች ዐቅዱን (floor plan and partition design) ለኤግዚቢሽን ማዕከሉ አስተዳደር በማቅረብ የቴክኒክ ክንውኑን በጋራ ቀጠለ፤ የትዕይንቱን ቁሳቁሶችም ማጓጓዝ ተጀመረ፤

መጋቢት 12 ቀን 2008 ዓ.ም.፡- በተፈጸመው የአገልግሎት ውል የክፍያ ኹኔታ አንቀጽ 4 መሠረት ማኅበሩ ቀሪውን ብር 400 ሺሕ ያኽል የመጨረሻ ክፍያ ለኤግዚቢሽን ማዕከሉ አስተዳደር ፈጸመ፤

መጋቢት 14 ቀን 2008 ዓ.ም.፡- በአገልግሎት ውሉ መሠረት፣ ዐውደ ርእዩ ከመጋቢት 15 – 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ክፍት ኾኖ በሚቆይባቸው ሰባት ቀናት ለሥራ የሚያገለግለውን ጊዜያዊ ቢሮ ቁልፍ ዐቢይ ኮሚቴው ከማዕከሉ አስተዳደር ተረከበ፤

መጋቢት 14 ቀን ረፋድ 3፡50፡- የተረከቡትን ቢሮ ለሥራ ዝግጁ በማድረግ ላይ የነበሩ የዐቢይ ኮሚቴው የአዳራሽ እንዲኹም የቅስቀሳና ማስታወቂያ ክፍሎች ሓላፊዎች ወደ ማዕከሉ የዋና ሥራ አስኪያጅ ቢሮ በጸሐፊዋ አማካይነት በድንገት ተጠሩ፤

  • ሓላፊዎቹን ከኹለት ባልደረቦቻቸው ጋር የተቀበሉት ዋና ሥራ አስኪያጁ፥ “በአካሔድ ላይ ክፍተቶች ስላሉ በአስቸኳይ ተሰብስበን መነጋገር ስላለብን ነው ያስጠራናችኹ፤” በማለት ዐውደ ርእዩን ለማካሔድ ፈቃድ ስለመኖሩ ጠየቁ፤
  • ማኅበሩ ዕውቅና ከሰጠውና ተጠሪ ከኾነለት ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ የፈቃድ ደብዳቤ ማጻፉንና ከማዕከሉ ጋር ከሰባት ወራት በፊት ውል ተፈራርሞ አስፈላጊውን ክፍያ መፈጸሙን የጠቀሱት የዐቢይ ኮሚቴው ሓላፊዎች፣ ቀደም ሲል በማዕከሉ የተስተናገዱት ሦስት ዐውደ ርእዮችም በዚኹ አሠራር መሠረት መካሔዳቸውን በማስታወስ በማኅበሩ በኩል የሰነድ ይኹን የአካሔድ ክፍተት እንደሌለ አስረዱ፤

መጋቢት 14 ቀን ረፋድ 4፡40 – 6፡00፡– የማዕከሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ ተጨማሪ የአስተዳደር ኮሚቴ አባላትን በመያዝ ከማኅበሩ አመራሮች እና አስፈጻሚዎች እንዲኹም ከዐቢይ ኮሚቴው አባላት ጋራ ባካሔዱት አስቸኳይ ስብሰባ፥ “ከአዲስ አበባ አስተዳደር ዐውደ ርእዩን ለማካሔድ የምትችሉበት የፈቃድ ደብዳቤ አምጡ፤” በሚል “የአካሔድ ክፍተት” ያሉትን አስታወቁ፤

  • ማኅበሩ ዐውደ ርእዩን ለማካሔድ ፈቃድ ማቅረብ ያለበት ዕውቅና ከሰጠውና ተጠሪ ከኾነለት አካል መኾኑን ጠቅሰው ማኅበሩም ይህንኑ የድጋፍ ደብዳቤ በወቅቱ ከጠቅላይ ጽ/ቤቱ አግኝቶ ያቀረበ በመኾኑ ከአዲስ አበባ አስተዳደር ማጻፍ አለበት የተባለው ፈቃድ፥ በማዕከሉ አሠራር ያልተለመደ፣ በወቅቱ ያልቀረበ እና ጨርሶም ሕጋዊ አግባብነት እንደሌለውተወካዮቹ አስረዱ፤
  • የሚመለከታቸውን የከተማውን አስተዳደር ሓላፊዎች ለማነጋገር ከቀትር በኋላ በተደረገው ጥረትም፣ ለዐውደ ርእዩ ከአስተዳደሩ እንዲጻፍ ስለተጠየቀው የፈቃድ ደብዳቤ የሚያውቀው ነገር እንደሌለና አሠራሩም በአስተዳደሩ የሕግ ማህቀፍ እንደሌለው ለማረጋገጥ ተቻለ፤
  • ለሰላማዊ ሰልፍ እና ለስብሰባ ፈቃድ በመስጠት ከሚታወቀው የከተማው አስተዳደር አጽፉ፤ በሚል የተጠየቀው የፈቃድ ደብዳቤ አሠራር፣ አራት ዐውደ ርእዮችን በጠቅላይ ቤተ ክህነት ዕውቅና እና ፈቃድ ሲያካሒድ ለቆየው የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕጋዊ አካል ማኅበረ ቅዱሳን፥ ሊቀርብ የማይችል፤ በኤግዚቢሽን ማዕከሉ አሠራር ያልተለመደ መኾኑንና በማኅበሩ በኩልም አንዳችም የአካሔድ ክፍተት እንደሌለ ከማዕከሉ አስተዳደር ጋር መተማመንና መግባባት ላይ ተደረሰ፤

A.A exhibition Center 2008

  • ይኹንና ተሲዓት በኋላ 9፡30 ገደማ፣ የኤግዚቢሽን ማዕከሉ አስተዳደር፣ በቁጥር ኤማ/1085-520-21/08 በዋና ሥራ አስኪያጅ ታምራት አድማሱ “አስቸኳይ” በሚል ለማኅበሩ በጻፈው ደብዳቤ፣ ዛሬ ሊካሔድ የነበረው ዐውደ ርእይ “ከፈቃድ ጋር በተያያዘ ያልተሟላ በመኾኑ” በሚል ዝግጅቱን ለማካሔድ አስቸጋሪ በመኾኑ መሰረዙን አስታወቀ፤
  • በልምድ ያልነበረንና በሕግም የማይታወቅን አሠራር ከጊዜው ውጭ በመጨረሻው ሰዓት የጠየቀውን ትክክለኛ አካል ማንነት በማወቅ፣ የመክፈቻ ጊዜው እክል የገጠመውን ዐውደ ርእይ በመርሐ ግብሩ መሠረት ለማስቀጠል በየፊናው ጥረት ሲያደርግ ያመሸው የማኅበሩ የሥራ አመራርና የሥራ አስፈጻሚ እንዲኹም የዝግጅት ዐቢይ ኮሚቴው ለጋራ ምክክር አስቸኳይ ስብሰባ በመቀመጥ ሌሊቱን አጋምሷል፡፡

መጋቢት 15 ቀን 2008 ዓ.ም.፡- ወራትን ባስቆጠረው መርሐ ድርጊት መሠረት ከብር 2 ሚሊዮን በላይ የቅድመ ዝግጅት ወጪ የተደረገበት ልዩ ዐውደ ርእዩ፥ ዛሬ፣ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት በሚከናወነው የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ለሕዝብ እይታ ክፍት የሚኾንበት ዕለት ነበር፤

  • የማኅበሩ አመራርና ዐቢይ ኮሚቴው ይህንኑ መርሐ ግብር አስቀድሞ በታቀደው መሠረት ለማስቀጠል የሚያደርገውን ጥረት ዛሬም ቀጥሎ የሚውል ሲኾን፤ ውሎውንና የደረሰበትን ውጤት ከቀትር 6፡00 ጀምሮ በማጠቃለልና በመገምገም አንድ ውሳኔ አድርጎ ከቀኑ 10፡00 ላይ በዋናው ማእከል ጽ/ቤት ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ይጠበቃል፡፡
  • ማኅበሩ፣ የልዩ ዐውደ ርእዩን እውንነት፣ ትክክለኛ ጊዜና ቦታም፤ በዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫው ለምእመኑ በይፋ እንደሚያሳውቅ ይጠበቃል፡፡

ለቤተ ክርስቲያን መሠረታዊ አስተህምሮ፣ ለኦርቶዶክሳዊነት ዓለም አቀፋዊነትና ሐዋርያዊ ተልእኮ እንዲኹም ከቤተ ክርስቲያን ነባራዊና ወቅታዊ ተግዳሮቶች አንጻር ከምእመኑ ለሚጠበቀው ድርሻ ልዩ ትኩረት የሰጠው ልዩ ዐውደ ርእዩ፣ ከመቶ ሺሕ በላይ ተመልካቾች እንደሚጎበኙት ግብ የተያዘበት ነው፤ ከ40‚000 በላይ የመግቢያ ትኬቶችን አስቀድመው የገዙ ምእመናንም የመጀመሪያዎቹ ጎብኚዎች ለመኾን በከፍተኛ ጉጉት ይጠባበቁታል፡፡

The post የማኅበረ ቅዱሳን ፭ኛው ዙር ልዩ ዐውደ ርእይ ቅድመ ዝግጅት ሒደት እውነታዎችና ቀጣይ ወቅታዊ ጥረቶች appeared first on Zehabesha Amharic.

‹‹በአገሪቱ ውስጥ ግጭቶች እየታዩ ያሉት በዋናነት የአስተሳሰብ ብዝኃነት በመታፈኑ ነው››

0
0

Lidetu Ayalewአቶ ልደቱ አያሌው፣ የኢትዮጵያዊያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) መሥራች

አቶ ልደቱ አያሌው የኢትዮጵያዊያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) መሥራች ናቸው፡፡ ኢዴፓን ለበርካታ ዓመታት የመሩት አቶ ልደቱ በአወዛጋቢው ምርጫ 97 የኢሕአዴግ ብርቱ ተፎካካሪ በነበረው የአራት ፓርቲዎች ጥምረት ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ በፓርቲያቸው ተወክለው ባሳዩት አመራር ዝናቸው ጫፍ ደርሶ ነበር፡፡ ይሁንና ከምርጫው በኋላ የቅንጅት አመራሮች ሲከፋፈሉ አቶ ልደቱ ላይ የተሰነዘሩት ወቀሳዎች ተቀባይነታቸው ላይ ጥያቄ እንዲነሳባቸው አድርገው ነበር፡፡ አቶ ልደቱ በእሳቸውና በፓርቲያቸው ላይ የቀረበው ወቀሳ አሉባልታ እንጂ ተጨባጭ መረጃና ማስረጃ የሚቀርብበት ሀቅ እንዳልሆነ በሚጽፏቸው መጻሕፍትና መጣጥፎች፣ ለተለያዩ ሚዲያዎች በሚሰጧቸው ቃል ምልልሶች ሲሞግቱ ቆይተዋል፡፡ አቶ ልደቱ እስከ 2003 ዓ.ም. በኢዴፓ ፕሬዚዳንትነታቸው በፖለቲካው መድረክ ጉልህ ሚና መጫወታቸውን ቢቀጥሉም፣ ከዚያ በኋላ ግን በመድረኩ ላይ ብዙም አይታዩም፡፡ የኢዴፓ መሪነቱን ለአቶ ሙሼ ሰሙ ያስረከቡት አቶ ልደቱ በእንግሊዝ ለንደን ዩኒቨርሲቲ በዴቨሎፕመንት ስተዲስ የማስተርስ ዲግሪ አጠናቀዋል፡፡ ከዚያ በፊት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በታሪክ ትምህርት የመጀመሪያ ዲግሪ አግኝተዋል፡፡ ከእንግሊዝ መልስ ‹‹ቲያትረ ፖለቲካ›› በሚል ርዕስ ባለፈው ዓመት መጽሐፍ ማሳተማቸውም ይታወሳል፡፡ ‹‹በሕይወት እስካለሁ ድረስ ራሴን ከፖለቲካ ማግለል ፈጽሞ አይታሰብም!›› የሚሉት አቶ ልደቱ፣ የኢዴፓ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ባይሆኑም የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል በመሆን አሁንም የሚጠበቅባቸውን ተግባር እየተወጡ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ኢሕአዴግ የሠራውን በጎ ተግባር ዕውቅና በመስጠት እንዲሁም ያጠፋውንና ድክመት ያሳየበትን ጉዳይ በግልጽ በመጠቆም የሚተነትኑት አቶ ልደቱ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የገዥው ፓርቲ ዋነኛ አጀንዳ የሆነው የመልካም አስተዳደር ችግሮች ላይ የሚሰማቸውንም አካፍለዋል፡፡ ሰለሞን ጎሹ በወቅታዊ ጉዳዮችና በመልካም አስተዳደር ዙሪያ አቶ ልደቱን አነጋግሯቸዋል፡፡

ሪፖርተር፡- የመልካም አስተዳደር ችግር በስፋትና በጥልቀት የአገሪቱን ህልውና እየተፈታተነ ነው የሚል ግምገማ በራሱ በመንግሥት ቀርቧል፡፡ ብዙ የኅብረተሰብ ክፍሎችም በዚህ ይስማማሉ፡፡ ዋነኛው የልዩነት ምንጭ የችግሩ መነሻ ምንድነው የሚለው ነው፡፡ በእርስዎ ግምገማ የዚህ መጠነ ሰፊ ችግር ዋነኛ ምንጭ ምንድነው?

አቶ ልደቱ፡- አንዱ መግባባት ያቃተን በችግሩ ክብደት ላይ ነው፡፡ ኢሕአዴጎች እንደተባለው ችግሩ የህልውና ጉዳይ ስለሆነ በከፍተኛ ዘመቻ ችግሩን ለመፍታት ቆርጠን ተነስተናል እያሉ ነው፡፡ በተቃዋሚዎች ዘንድና በአንዳንድ የኅብረተሰብ ክፍሎች ይኼ እንደ እውነት አልተወሰደም፡፡ ኢሕአዴግ እንደተለመደው ዘመቻ መልክ ቴአትር አሳይቶ የሚተወው የማስመሰያ እንቅስቃሴ ነው የሚል አስተሳሰብ አለ፡፡ እኔ ኢሕአዴግ ይኼ ችግር የህልውና ጉዳይ ነው፣ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ ነው ብሎ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ የቀልድ ነው ብዬ አላምንም፡፡ የምር ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ኢሕአዴግ የምር እየተንቀሳቀሰ ያለው ይኼ ችግር ሳይፈታ ከቀጠለ የሥርዓቱን ህልውና እንደሚፈታተንና አደጋ ላይ እንደሚጥለው ስለገባው ይመስለኛል፡፡ ሥርዓቱ ላይ ያለው አንዱም ችግር ይኼ ነው፡፡ ችግሮች ሳይጠነክሩ፣ ሳይሰፉና ሥር ሳይሰዱ ለሕዝብና ለአገር ጥቅም ሲባል በተገቢው ወቅትና ሁኔታ መፈታት ሲገባቸው፣ አንዳንድ ጊዜ ዘመቻዎቹ ጠንከር ብለው የሚመጡት በራሱ ህልውና ላይ ችግሩ ሲመጣ ነው፡፡ ይኼ ችግር የሥርዓቱን ህልውና ብቻ አይደለም የሚፈታተነው፡፡ አጠቃላይ የአገር ጥቅምና ደኅንነትን የሚፈታተን ጉዳይ ነው፡፡ ኢሕአዴግ ማየት የነበረበት ከአገር ጥቅም እንጂ ከራሱ ጥቅምና ደኅንነት አንፃር መሆን አልነበረበትም፡፡ ዞሮ ዞሮ በዚህ ጉዳይ ላይ ኢሕአዴግ እየቀለደ አይደለም፡፡ እርግጥ በኢሕአዴግ በኩል መልካም አስተዳደር ምንድነው በሚለው ጉዳይ ላይ ልዩነት አለ፡፡ ከተለያዩ መድረኮች እንደተረዳነው በኢሕአዴግ አስተሳሰብ መልካም አስተዳደር የቢሮክራሲ ውጣ ውረድ ነው፡፡ ኅብረተሰቡ ወደ መንግሥት ቢሮዎች አገልግሎት ፈልጎ ሲሄድ የሚገጥመው ውጣ ውረድና የመጉላላት ችግር ተደርጎ ነው የሚታየው፡፡ በእርግጥም ይኼ አንዱ የመልካም አስተዳደር ችግር መገለጫ ነው፡፡

ነገር ግን መልካም አስተዳደር የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት ጥያቄም ነው፡፡ በአጠቃላይ የመንግሥትንና የሕዝብን ግንኙነት የሚመለከት ጉዳይ ነው፡፡ በምርጫ አማካይነት ከሕዝብ ጋር የገባውን ውል መንግሥት በአግባቡ እየተወጣ ነው ወይስ አይደለም የሚለው ጥያቄ ነው የመልካም አስተዳደር ጥያቄ፡፡ ገዥው ፓርቲ ግን የመልካም አስተዳደር ጥያቄን በዋናነት ከኢኮኖሚ ጉዳይ ጋር አስተሳስሮ ያያል፡፡ በዚህ መልኩ የሚደረግ ዘመቻ ችግሩን ከምንጩ ያደርቃል ብዬ አላምንም፡፡ ሁለተኛ በዚህ ጠባብ ማዕቀፍም ውስጥ ቢሆን የችግሩ መሠረታዊ ምንጭ ምንድነው የሚለው ላይ በግልጽ ውይይት ሲደረግበት አይታይም፡፡ እርግጥ ችግሩ ምን ያህል ከባድ እንደሆነና በሁሉም የአገሪቱ አካባቢ ያለ መሆኑ ላይ የፖለቲካ አመራሩ ስምምነት ላይ የደረሰ ይመስላል፡፡ ለምንድነው ይኼ ሥርዓት በዚህ መጠንና ሁኔታ የመልካም አስተዳደር ችግር ውስጥ የተዘፈቀው ብሎ መሠረታዊ የሆነውን ምክንያት ማወቅና ችግሩን ከምንጩ የማድረቅ አቅጣጫ ግን አይታይም፡፡ እኔ ከዚህ በፊት በጋዜጣችሁ ላይ ይኼ ዘመቻ የሚከሽፍ መሆኑ ከወዲሁ የታወቀ ነው ብዬ ለመደምደም ያስገደደኝ ይኼ ምክንያት ነው፡፡ ለእኔ ምንጩ የፖለቲካ ሙስና ነው፡፡ የኢኮኖሚ ሙስናው የፖለቲካ ሙስናውን ተከትሎ የመጣ ነው፡፡ ሥርዓቱ ለፖለቲካ ሥልጣን የበላይነት ብሎ ከፍተኛ የሆነ የፖለቲካ ሙስና የሚፈጽም በመሆኑ የኢኮኖሚ ሙስናው ይኼን ተከትሎ የመጣ ነው፡፡ በቢሮክራሲው ውስጥ የሚቀጠሩት ሰዎች በሙያ ብቃታቸው፣ በትምህርት ደረጃቸውና በሥነ ምግባራቸው አይደለም በዋናነት የሚመለመሉት፡፡ በዋናነት የሚቀጠሩት ለሥርዓቱ ባላቸው ታማኝነት ነው፡፡ ይኼ የፖለቲካ ውሳኔ ነው፡፡ የፖለቲካ ሙስናም ነው፡፡ ከሚኒስትር ጀምሮ እስከ ጥበቃና ፅዳት ሠራተኛ ድረስ ሰዎች የሚቀጠሩት በፖለቲካ ታማኝነታቸው ነው፡፡ የአገሪቱን ቢሮክራሲ የሚያመርቱት ዩኒቨርሲቲዎች ሲመረቁ ሳይሆን ገና ሲገቡ ነው ተማሪዎቹ የኢሕአዴግን የመታወቂያ ካርድ በእጃቸው የሚይዙት፡፡ ምክንያቱም በሥራ የመቀጠር ዋስትናቸው እሱ ነው፡፡ በዚህ መልኩ በፖለቲካ ሙስና የተሰባሰበ ቢሮክራሲ የኢኮኖሚ ሙስና ቢፈጽምና የመልካም አስተዳደር ችግር ውስጥ ቢዘፈቅ የሚደንቅ አይደለም፡፡

አንድ ሥርዓት የፖለቲካ የሥልጣን የበላይነቱን ለማስጠበቅ ብሎ ምርጫን የሚያጭበረብር ከሆነ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን የሚያፍን ከሆነ፣ የሕዝብን ሰብዓዊ መብት የሚያፍን ከሆነ፣ የፕሬስ መብትን የሚያፍን ከሆነ፣ ይህን የሚያደርገው በካድሬዎቹ አማካይነት ነው፡፡ አባላቱ እንዲህ ዓይነት የፖለቲካ ሙስና ሲፈጽሙ የማይቀጣ መንግሥት የኢኮኖሚ ሙስና ሲፈጸም ሊደንቀው አይገባም፡፡ በተለይ በዝቅተኛ እርከን ላይ ያሉ ካድሬዎች ናቸው በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ዳታ የሚያዘጋጁት፡፡ የሚቀርበው ዳታ አለቆችን የሚያስደስት እንጂ እውነታውን የሚያንፀባርቅ አይደለም፡፡ የበላይ አመራሮች የሚቀርብላቸውን ዳታ እንዳለ በግርድፉ ከመቀበል ይልቅ ዳታ ኦዲት ማድረግ ተገቢ እንደሆነ ለዓመታት ተከራክሬያለሁ፡፡ ይህ እንደ ጠቃሚ ሐሳብ አሁንም ድረስ አይወሰድም፡፡ እኔ ከ20 ዓመታት በላይ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ተሳትፎ ቢኖረኝም ይህ ካድሬ ይህን የፖለቲካ ሙስና ፈጽሟል ተብሎ ዕርምጃ ሲወሰድበት አላየሁም፡፡ አባላቱን ለመቅጣት አለመፈለግ ብቻ ሳይሆን አንዳንድ ጊዜ እነዚህ የፖለቲካ ሙስናዎች በመንግሥት ትዕዛዝ የሚፈጸሙ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ በቢሮክራሲው ውስጥ የተሰባሰበውን ካድሬ ካየህ የሕዝብ አገልግሎትን አጀንዳ አድርጎ የተሰበሰበ ኃይል አይደለም፡፡ በተለይ ከምርጫ 97 በኋላ በኢሕአዴግ ዙሪያ የተሰበሰበው ኃይል ጥቅም ፈላጊ ኃይል ነው፡፡ ስለዚህ የፖለቲካ ሙስናን ስትዋጋ የኢኮኖሚ ሙስናን ማድረቅ አትችልም፡፡ ስለዚህ ይህን ችግር ለመቅረፍ መሠረታዊና ሥር ነቀል የሆነ የፖለቲካ አስተሳሰብ ለውጥ ያስፈልጋል፡፡

ሪፖርተር፡- የኢትዮጵያ የፌዴራል ሥርዓት ማንነት ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ይህ ለብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በፍትሐዊነት የአገሪቱን ሀብትና ሥልጣን ማከፋፈልን ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡ ነገር ግን ይኼ አቅምን መሠረት ካደረገ ቢሮክራሲ ጋር አብሮ ይኼዳል?

አቶ ልደቱ፡- መሠረታዊው ነገር በአንድ የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ በቋንቋና በዘር ማንነታቸው ካደራጀህ ሌሎች ለሥራ፣ ለአስተዳደርና ለኢኮኖሚ ዕድገት አስፈላጊ የሆኑት ነገሮች ሁሉ ወደ ጎን ይገፋሉ፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ አሁን ያለው የመልካም አስተዳደር ችግር ከዚሁ የሚመነጭ ነው፡፡ ሰዎች ወደ አንድ የመንግሥት መሥሪያ ቤት አገልግሎት ፈልገው ሲሄዱ ምን ዓይነት ተቋም አለ? ምን ዓይነት ሕግ አለ? ብለው አይደለም የሚሄዱት፡፡ ማን አለ? ብለው ነው የሚሄዱት፡፡ የራሴ የሚሉትን ሰው ነው ፈልገው የሚሄዱት፡፡ ይኼ በአብዛኛው የሚመዘነው በዘር ማንነትና በፖለቲካ አመለካከት መቀራረብ ነው፡፡ ይኼ ዜጎች በእኩል ዓይን የማይታዩበትን ሁኔታ ፈጥሯል፡፡ እኛና እነሱ የሚል አስተሳሰብ በየመንግሥት ተዋረድ ባሉ መዋቅሮች ውስጥ ተፈጥሯል፡፡ በዚህ ምክንያት በተለይ በገጠር ወደ መንግሥት መዋቅር የሚመጣው ትምህርትና እርሻ ጠል የሆነው የኅብረተሰብ ክፍል ነው፡፡ በከተማም አብዛኛው ወደ መንግሥት መዋቅር ገብቶ ሲሠራ የምናየው ሰው መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች ውስጥ ተቀጥሮ መሥራት የማይችል፣ ወይም በግሉ ካፒታል ኖሮት መነገድ የማይችል፣ ወይም በግሉ ክፍለ ኢኮኖሚ መሥራት የማይችል ሰው ነው፡፡ እዚያ ውስጥ የሚገባው ለኑሮዬ የሚበቃ ጥቅምና ደመወዝ አገኛለሁ ብሎ ሳይሆን የሕግና የአሠራር ክፍተቶችን ተጠቅሜ ከኅብረተሰቡ ጉቦና የተለየ ጥቅም ተቀብሎ ኑሮዬን እደጉማለሁ ብሎ ነው፡፡ ሥርዓቱ የራሱን የፖለቲካ የበላይነት ለማስጠበቅ ታማኝ የሆነ፣ ጥያቄ የማይጠይቅና ታዛዥ የሆነ ቢሮክራሲ ነው መሰብሰብ የሚፈልገው፡፡ መንግሥት ይህን ችግር ለመዋጋት የሚያደርገው ጥረት ሁሉ በራሱ መዋቅር ተሸናፊ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ራሱን በራሱ ነው የሚታገለው፡፡

ሪፖርተር፡- አንዳንድ የፌዴራሊዝም ምሁራን ግን ማንነትን መሠረት ያደረገ የፌዴራል ሥርዓት አቅምን መሠረት ያደረገ ቢሮክራሲ ለማዋቀር ችግር እንደማይፈጥር ይከራከራሉ፡፡ የብሔር ተዋፅኦው እንዳለ ሆኖ በእዚያው ብሔር አባላት መካከል አቅምን መሠረት ያደረገ ምልመላ ማድረግ ይቻላል ሲሉም ይጠቁማሉ፡፡ እርስዎ በዚህ ይስማማሉ?

አቶ ልደቱ፡- ይኼ አስተሳሰብ ችግር ውስጥ የሚገባው በክልሎች ደረጃ ነው፡፡ ለምሳሌ በአማራ ክልል በየቢሮክራሲው ተቀምጦ የመልካም አስተዳደር ችግር እየፈጠረ ያለው ከሌላ ብሔር የመጣው ሳይሆን ራሱ አማራው ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በፌዴራል መንግሥት ደረጃስ?

አቶ ልደቱ፡- ችግሩ ሕዝቡን በማማረር ላይ ያለው በፌዴራል ደረጃ ነው? ከሕዝቡ የዕለት ተዕለት ኑሮ ጋር የተገናኘው ችግር እየተፈጸመ ያለው በክልሎች ደረጃና ከሕዝቡ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ባለው ቢሮክራሲ ነው፡፡ እላይ ያሉት ችግራቸው ተገቢ የሆነ የአሠራር ሥልት ዘርግተው ይህ የመልካም አስተዳደር ችግር መጀመሪያውኑ እንዳይስፋፋ አላደረጉም፡፡ መስፋፋት ሲጀምር ደግሞ በአጭሩ እንዲቀጭ ዕርምጃ አልወሰዱም፡፡ የአመራር ሚናቸውን በአግባቡ ባለመጫወታቸው ጉዳዩ አገራዊ ችግር እንዲሆን አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡ አለበለዚያ በራስህ ተወላጅ ስለተመራህ ብቻ ችግሩ አይቀረፍም፡፡ ለእኔ የብሔረሰቦችን መብት እያከበሩ ግን ደግሞ የአስተዳደር ሥራን በአቅም መሠረት እንዲያዝ ማድረግ የሚጋጭ ነገር አይደለም፡፡ ችግሩ የፖለቲካ ድርጅቶቹ ወደ ቢሮክራሲው እንዲመጣ የሚመለምሉት ሰው በብሔር ብቻ አይደለም በፖለቲካ ወገንተኝነትም ነው፡፡ በኦሮሚያ የኦሕዴድ፣ የኦነግ ወይም የኦፌኮ ደጋፊ የሆነ ሰው አለ፡፡ ሦስቱም ኦሮሞዎች ናቸው፡፡ ወደ ቢሮክራሲው አንድ ሰው የሚመጣው በኦሮሞነቱ ብቻ አይደለም፡፡ በኦሕዴድ ደጋፊነቱ ነው የሚያመጡት፡፡ ነገር ግን ተገቢ የሆነ ሕግና ሥርዓት አስቀምጠህ ኃላፊነቱን በአግባቡ እስከተወጣ ድረስ የኦፌኮን አባል ቢሮክራሲው ውስጥ እንዲሠራ ብታደርገው ችግር የለውም፡፡ ፌዴራሊዝም ተግባር ላይ የሚውለው መብትን ለማክበር ብቻ አይደለም፡፡ የኢኮኖሚ ልማትን ለማሳደግና አስተዳደራዊ ፍትሕንም ለማምጣት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፌዴራሊዝም ጥቅም ላይ የዋለው በዋነኛነት አለ ተብሎ የታመነውን የብሔር ጭቆና የመፍቻ መሣሪያ ሆኖ ነው፡፡ ፌዴራሊዝም የመጣው ከዚህ ጥያቄ በፊት ነው፡፡ ስለዚህ በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ፌዴራሊዝም ሊፈታቸው የሚችላቸውን ሌሎች ጥያቄዎች ማስተናገድ አልተቻለም፡፡ ለምሳሌ የአስተዳደር አመችነትና የኢኮኖሚ ልማት ጉዳይ ከፍተኛ የሆነ ትኩረት ማግኘት ነበረባቸው፡፡ የብሔር ጥያቄም ስለመመለሱ አጠያያቂ ነው፡፡ ለምሳሌ በኦሮሚያ ከፍተኛ የሆነ የመብት ጥያቅ ይነሳል፡፡ በክልሉ ግን የፌዴራል አደረጃጀት ተግባራዊ ሆኗል፡፡ ክልሉን የሚያስተዳድሩት የኦሮሞ ብሔር አባላት ናቸው፡፡ ችግሩን ግን ፈቱት ወይ? አልፈቱትም፡፡

ሪፖርተር፡- ከአመራር ዘይቤ አንፃር ኢትዮጵያ ከአቶ መለስ ሕልፈተ ሕይወት በኋላ መሠረታዊ ለውጥ አሳይታለች ብለው ያስባሉ?

አቶ ልደቱ፡- አቶ መለስ ካረፉ በኋላ በእርግጥም ለውጥ አለ፡፡ ምን ዓይነት ለውጥ ነው ያለው የሚለው እንደየአስተሳሰባችን ሊለያይ ይችላል፡፡ በእኔ በኩል ከአቶ መለስ ሞት በኋላ ከፍተኛ የሆነ የአመራር ክፍተት አያለሁ፡፡ አጠቃላይ የኃይል ማዕከሉ የት እንደሆነ የጠፋበት ሁኔታ ነው የተፈጠረው፡፡ ይኼ ስሜት የሚሰማው ከኢሕአዴግ ውጪ ለሆነው ሰዎች ብቻ አይመስለኝም፡፡ ኢሕአዴግም ውስጥ ራሱ ይኼ ግልጽ ያልሆነላቸው ሰዎች ያሉ ይመስለኛል፡፡ አቶ መለስ እያሉ በተለይም ከሕወሓት መከፋፈል በኋላ የፖለቲካ ሥልጣኑ ተጠቃሎ ሊባል በሚችል መጠን በእሳቸው እጅ ነበር፡፡ ከእሳቸው መሞት በኋላ በግለሰብ ደረጃ ያንን ሚና የተካ ሰው የለም፡፡ በቡድን ደረጃ ያ የኃይል ሚዛን ማን ላይ ነው ያለው የሚለው ግልጽ ሳይሆን የቀጠለ ነው፡፡ አሁን ኢሕአዴግ ሥልጣኑን እያጠናከረ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ያ ሒደት አልቆ ሥልጣን በአንድ ግለሰብ ወይም ቡድን በግልጽ ተይዞ አይታይም፡፡ ስለዚህ አንዳንድ ጊዜ መመርያዎች፣ ትዕዛዞችና ውሳኔዎች ከየት አቅጣጫ እንደሚመጡ ለማወቅ አስቸጋሪ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በይፋ መንግሥት አራምዳለሁ የሚለው አቋም ሌላ ነው፣ መሬት ላይ በተግባር ሲተረጎም የሚታየው ደግሞ ሌላ ነው፡፡ በድርጅቱ ውስጥ ግጭቶች ተፈጥረው በሒደት አንድ ግለሰብ ወይም ቡድን አሸናፊ ሆኖ መውጣት አለበት፡፡ እንደዚያ ዓይነት ሒደት አሁን ኢሕአዴግ ውስጥ የተፈጠረ አልመሰለኝም፡፡ የሚፈጠርበት አዝማሚያ ግን ያለ ይመስለኛል፡፡ ሌላው ለውጥ በተለይ በቅርቡ በአገሪቱ በተፈጠሩ ችግሮች እየጎላ የመጣው ጉዳይ በኢሕአዴግ ዘንድ አንድን ውሳኔ በደንብ ሳያጤኑ ወስኖ፣ ነገር ግን የሕዝብ ተቀባይነት ሲያጣ ወዲያው የመቀልበስ አሠራር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ የውሳኔው ትክክለኛነት ላይ ማተኮር ሳይሆን ሕዝቡ ለውሳኔው ያለው አመለካከት ላይ የማተኮር አዝማሚያ ይታያል፡፡ ለዚህ እንደ አብነት በኦሮሚያ ማስተር ፕላንና በቅርቡ ደግሞ ከታክሲ ሾፌሮች ጋር በተያያዘ የተወሰኑትን ውሳኔዎች መጥቀስ ይቻላል፡፡ ውሳኔ ወስኖ ተግባራዊ የማድረግ አቅም እያጣ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በቅርቡ በፓርላማ ባደረጉት ቆይታ የማንነት ጥያቄዎች ኢትዮጵያ ውስጥ ተመልሰው አልቀዋል ብለዋል፡፡ ይኼ እንደ መሠረታዊ ለውጥ ሊወሰድ አይችልም?

አቶ ልደቱ፡- የጠቅላይ ሚኒስትሩን የፓርላማ ንግግር ተከታትየዋለሁ፡፡ እውነቱን ለመናገር ስሰማው ደንግጫለሁ፡፡ በእውነት ታስቦበት የተነገረ ንግግር ነው ወይስ በድንገት በስሜት የተነገረ ንግግር ነው የሚለውን እስካሁን መለየት አልቻልኩም፡፡ ታስቦበት የተነገረ ንግግር ከሆነ በጣም አከራካሪ ይመስለኛል፡፡ እኔ እስከሚገባኝ ድረስ ሕገ መንግሥቱ ከዚህ በኋላ የብሔር ብሔረሰቦች ችግር ተፈቷል አላለም፡፡ የሚፈታበትን አካሄድ አስቀምጧል፡፡ ሁለተኛ የማንነት ጥያቄ አንድ ወቅት ላይ ተነስቶ አንድ ወቅት ላይ ሙሉ በሙሉ ተፈቷል የሚባል አይደለም፡፡ በመቼውም ሁኔታና ጊዜ ሊከሰት ይችላል፡፡ ሕገ መንግሥቱ ያን የመፍቻ መሣሪያ ነው የሚሆነው፡፡ የማንነት ጥያቄ በውሳኔ ከዚህ በኋላ ተዘግቷል ሊባል አይችልም፡፡ አንዱ መጀመሪያም ሕገ መንግሥቱ ሲረቀቅና የፌዴራል ሥርዓቱ ሲዋቀር ግምት ውስጥ መግባት የነበረበት ይኼ ነው፡፡ የማንነት ጥያቄ አንድ ጊዜ ከቋንቋና ከብሔረሰብ ማንነት ጋር ከተያያዘ ማቆሚያ የሌለው እንደሆነ ግምት ውስጥ መግባት ነበረበት፡፡ ስለዚህ ይኼ ውሳኔ ራሱን ሕገ መንግሥቱን የሚቃረን ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም አስበውበት ተናገሩ ብዬ አላምንም፡፡ አስበውበት የተናገሩ ከሆነና ከጀርባም የድርጅታቸው ውሳኔ ከሆነ ይኼ ትልቅ ለውጥና ሽግግር ነው፡፡ በፓርላማ እንደ ቀልድ ተነግሮ ብቻ መታለፍም የለበትም፡፡ ይኼ ለውጥ ለአገር ይጠቅማል ወይስ አይጠቅምም የሚለው ለውይይት ቀርቦ ሁላችንም ሐሳብ መስጠት ያለብን ይመስለኛል፡፡ ይኼ ኢሕአዴግን እንደገና የመፍጠር ጥያቄ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በቅርቡ ከዘመን መጽሔት ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የኢትዮጵያ ቢሮክራሲ መንግሥት ሊቋቋመው ያልቻለና መንግሥትን የማይፈራ ነው ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል ቢሮክራሲው ታማኝና ታዛዥ ነው እያሉ ነው፡፡ ይኼ እርስ በርሱ አይጋጭም?

አቶ ልደቱ፡- አይጋጭም፡፡ ሥርዓቱ ቢሮክራሲውን ሲያሰባስብ የራሴ የሚለው ጥቅም እንዲያገኝ ፈልጎ አይደለም፡፡ መንግሥት የራሴ የሚለው የፖለቲካ ጥቅም ስላለው ነው፡፡ እኔን የሚመስል፣ የእኔን አስተሳሰብ የሚደግፍና ለእኔ ታማኝ የሆነ ቢሮክራሲ አሰባስቤ የፖለቲካ የበላይነቴን አስጠብቄ እቀጥላለሁ ብሎ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ዓይነት ሠራዊት ሲፈጥር ነገ ከነገ ወዲያ የራሱን ጥያቄ ይዞ ሊመጣ እንደሚችል ማሰብ ነበረበት፡፡ የኢኮኖሚ ጥቅም መፈለግ የሚጀምረው ኋላ ላይ ነው፡፡ አሁን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሙስናው ተመጋጋቢ ሆነዋል፡፡ ተቃራኒ በመሆናቸው ጦርነት ውስጥ ናቸው፡፡ አንድ ሰው ሙስና ውስጥ የሚገባው ደሃ ስለሆነ አይደለም፡፡ ይበልጥ ሙስና ውስጥ የሚገባው ሙስናውን ማጣጣም ከጀመረ በኋላ ነው፡፡ ከሥር ከመሠረቱ የመልካም አስተዳደር ችግርን ነቅሎ የሚጥል ዘመቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡ ችግሩ መዋቅራዊ መሆኑን አምኖ መቀበል ይጠይቃል፡፡ በለብ ለብ ዘመቻ አሸናፊ የሚሆነው ቢሮክራሲው ነው፡፡ ከዚህ ቀደም መቀጣጫ እንዲሆኑ የተወሰኑ ሰዎች ሲታሰሩ አይተናል፡፡ ችግሩ ግን አልተፈታም፡፡ የቢሮክራሲው ኃይል አሁን ገዝፏል፡፡ ቢሮክራሲውና ሙስና አሁን አንድ ሆነዋል፡፡ ሙስናን ብታቆም ቢሮክራሲው በደመወዝ ብቻ ሊተዳደር አይችልም፡፡ ጥሎት ስለሚወጣ መንግሥት ተንገራግጮ ይቆማል፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ችግር ለመፍታት አንደኛ ሁሉን አቀፍ የሆነ መፍትሔ መፈለግ አለብህ፡፡ ዋናው የፖለቲካ መፍትሔ ነው፡፡ ቀጥሎ ደግሞ ይኼ ቢሮክራሲ ራሱን፣ ቤተሰቦቹን፣ ልጆቹን የሚያስተምርበትና የሚመግብበት ደመወዝና ጥቅማ ጥቅም እንዲያገኝ ማድረግ አለብህ፡፡ የሥርዓቱ አብዛኛው አካል ተበክሏል፡፡ ይኼን አካል ቆርጦ መጣል ቀላል ውሳኔ አይደለም፡፡ ግን ደግሞ አማራጭ የለም፡፡ ይኼንን የተገነዘቡ የኢሕአዴግ አመራሮች ያሉ ይመስለኛል፡፡ ነገር ግን ከችግሩ ጋር ደግሞ እጅና ጓንት የሆኑና የተያያዙ አካላት አሉ፡፡ አንዳንዳቹ እኮ የኢሕአዴግ ድርጅቶች በትክክል በሙስና የተዘፈቀ ሰው ሁሉ ይጠየቅ ቢባል ድርጅቶቹ እንደ ድርጅት ሊፈርሱ ይችላሉ፡፡ የሚያስከትለው የፖለቲካ ጣጣ ሊኖር ይችላል፡፡ ግን ደግሞ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ግን ይጠይቃል፡፡

ሪፖርተር፡- በኢሕአዴግ ዲስኩር ውስጥ ፓርቲው ራሱን የሚያስተዋውቀው ለሕዝብ ጥቅም የሚኖሩና ለዚህ ዓላማ መስዋዕት ለመሆን ዝግጁ በሆኑ አባላት እንደተሞላና ጥቂት ከዓላማው ውጪ የሚሠሩ አባላትን የማክሰም ብቃት እንዳለው ነው፡፡ በሌላ በኩል ሙስናን ለመዋጋት ከአስተዳደራዊና ከሕጋዊ ዕርምጃዎች ይልቅ ፖለቲካዊ መፍትሔዎች በቅድሚያ መወሰድ እንዳለበት የመንግሥት የፖሊሲ ሰነዶች ይጠቁማሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች አብረው የሚሄዱ ናቸው?

አቶ ልደቱ፡- ሁለቱም የመፍትሔው አካል ናቸው፡፡ ተቀናጅተው ተግባራዊ መሆን አለባቸው፡፡ ኢሕአዴግ የሚታገለው አንደኛውን ነጥሎ ለመፈጸም ነው፡፡ ነገር ግን በኢሕአዴግ ዙሪያ የተሰባሰበው በትክክል የአገር ፍቅር ያለውና ለሕዝብ አገልግሎት ጊዜውን፣ ጉልበቱንና ዕውቀቱን መስዋዕት ለማድረግ የተሰባሰበ ኃይል ነው ወይ? በዚህ መንፈስ ወደ ኢሕአዴግ የተቀላቀሉ ሰዎች የሉም ልል አልችልም፡፡ በተለይ በትጥቅ ትግሉ ወቅት ይኼን ዓይነት አመለካከት ይዘው የገቡ ሰዎች አሉ ብዬ አምናለሁ፡፡ ግን አሁን ይኼ ሥርዓት በሥልጣን ላይ ከ20 በላይ ዓመታት ከቆየ በኋላ በዙሪያው ያሰባሰባቸው ኃይሎች እነማን ናቸው የሚለውን ካየን ግን በትክክል ለሕዝብ አገልግሎት የቆሙ አይደሉም፡፡ ያለ ምንም ማጋነን ከ95 በመቶ በላይ የሆነው ኅብረተሰብ ለዚያ ብሎ የተሰባሰበ አይደለም፡፡ ከአምስት ወይም ከስድስት ዓመታት በፊት ኢትዮጵያ ውስጥ የነበረው የሙስና መጠን በጣም ዝቅተኛ ነበር፡፡ አሁን ለማመን በሚከብድ መጠን ጨምሯል፡፡

ሪፖርተር፡- ከቀድሞ መንግሥታት በተቃራኒ ኢሕአዴግ የዘረጋሁት የአስተዳደር መዋቅር 1 ለ 5ን ጨምሮ በእያንዳንዱ ቤት የሚደርስ ነው በማለት በኩራት ይገልጻል፡፡ ከዚህ አንፃር ይህን ለአገሪቱ ህልውና የሚያሰጋ ችግር እስካሁን እንዴት ሳይገነዘበው ቀረ?

አቶ ልደቱ፡- ችግሩን ከተገነዘበው ቆይቷል፡፡ በመሠረቱ ኢሕአዴግ ሥልጣን ከያዘ ጀምሮ የመዋቅር ማሻሻያ ያልተሞከረበት ጊዜ የለም፡፡ ከፍተኛ የሆነ የመልካም አስተዳደር ችግር አለ የተባለው ዛሬ አይደለም፡፡ በሌላው አገር አንድ ችግር ተፈጠረ ብሎ ከሥልጣን የሚለቅ ሚኒስትር የተለመደ ነው፡፡ መንግሥት በአግባቡ ሥራዬን አልተወጣሁም ብሎ ሲያስብ የመተማመኛ ድምፅ ይጠይቃል፣ ሕዝበ ውሳኔ ያደርጋል፡፡ ይኼ የሚያሳየው ችግሩ ከፍተኛ ከሆነ የፖለቲካ ህልውናህን ሊፈታተን እንደሚችል ነው፡፡ ኢሕአዴግ ግን የራሱን የፖለቲካ የበላይነት አስጠብቆ ነው ችግሮችን መፍታት የሚፈልገው፡፡ የፖለቲካ ህልውናውን የሚነካኩ ከሆነ ሊነካቸው አይፈልግም፡፡

ሪፖርተር፡- ኢሕአዴግ የመልካም አስተዳደር ችግርን ለመቅረፍ የተለያዩ ዕርምጃዎችን እንደሚወስድ ሲገልጽ ቆይቷል፡፡ ለዚህ የዴሞክራሲ ተቋማት የሚባሉት እንደ ፓርላማ፣ ፀረ ሙስና ኮሚሽን፣ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን፣ እንባ ጠባቂ ተቋምና ሚዲያ የራሳቸው ሚና እንደሚኖራቸው ተገልጿል፡፡ እስካሁን የተወሰዱትን ዕርምጃዎችና የተቋማቱን ሚና እንዴት ያዩታል?

አቶ ልደቱ፡- ይኼን ችግር በብቃት ለመዋጋት ነፃ የሆኑ ተቋማት ያስፈልጉ ነበር፡፡ ነገር ግን እነዚህ ተቋማት የተፈጠሩት የፖለቲካ ወገንተኝነት ባላቸው ወገኖች ነው፡፡ ነፃ ሆነው ሥርዓቱ አቅጣጫ ሲስት የሚገዳደሩና የሚጠይቁ ሰዎች አይደሉም በተቋማቱ የተሰባሰቡት፡፡ የፖለቲካ ታማኝነት መመዘኛ ሆኖ የሥርዓቱ ደጋፊና ታማኝ የሆኑ ሰዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ተቋማቱ አሁን ነፃነት አላቸው ማለት አይቻልም፡፡ በሥርዓቱ ውስጥ ያለውን ችግር ታግሎ ለመፍታት የሚያግዝ ጉልበት አላቸው ማለት አይቻልም፡፡ መንግሥትን ከጥቃት የሚከላከሉ ናቸው፡፡ የእኔ ጠላት ናቸው የሚላቸውን አካላት እንዲያጠቁለት የተቋቋሙ ናቸው፡፡ ስለዚህ ጥርስ የሌለው አንበሳ ሆነዋል፡፡ ፀረ ሙስና ኮሚሽን ከተቋቋመ በኋላ ሙስና እየጨመረ ነው የመጣው፡፡ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ከተቋቋመ በኋላ የኅብረተሰቡ የሰብዓዊ መብት ችግር የበለጠ እየተባባሰ ነው የመጣው፡፡

ሪፖርተር፡- ባለፈው ግንቦት ወር በተካሄደው ጠቅላላ ምርጫ መቶ በመቶ ያሸነፈው ገዥው ፓርቲ፣ በጥቂት ወራት ልዩነት ውስጥ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ተቃውሞ ሲነሳበት እንዴት አዩት?

አቶ ልደቱ፡- ኢሕአዴግ መቶ ፐርሰንት እንዳሸነፈ በምርጫ ቦርድ ሲነገረው መደሰት ሳይሆን መደንገጥ ነው የነበረበት፡፡ ምክንያቱም የተለያየ የፖለቲካ አስተሳሰብና የፖለቲካ ቅራኔ ባለበት አገር አንድ ፓርቲ በብቸኝነት ከቀበሌ እስከ ፓርላማ ያለውን መዋቅር መቶ በመቶ አሸንፎ የሚይዝበት ሁኔታ የለም፡፡ መቶ በመቶ አሸንፏል ከተባለ በኋላ እንደዚህ ዓይነት በጣም ከፍተኛ የሆነ የኅብረተሰብ ብሶቶችና ግጭቶች መፈጠራቸው የምርጫው ውጤቱ በፍፁም ነባራዊ ሁኔታውን የማይገልጽ መሆኑን ነው የሚያሳየው፡፡ ኢሕአዴግ ቆም ብሎ ማሰብ ያለበት አሁን ነው፡፡ መቶ ፐርሰንት የምርጫ ውጤት የሚያሳየው በኢትዮጵያ ውስጥ የሐሳብ ብዝኃነት ቦታ ማጣቱን ነው፡፡ ብዝኃነት የሚገለጸው በቋንቋ፣ በሃይማኖትና በብሔረሰብ ማንነት ብቻ አይደለም፡፡ እንዲያውም በዋናነት ብዝኃነት የሚገለጸው በአስተሳሰብ ነው፡፡ በኢትዮጵያ እየነገረና እየተሳበበ ያለው፣ በተግባር እየዋለ ያለው የአንድ ፓርቲ ብቸኛ አስተሳሰብ ነው፡፡ ሌሎች አስተሳሰቦች ተደፍቀዋል፡፡ ኅብረተሰቡ ብሶቱን፣ ተቃውሞውንና ቅሬታውን የሚገልጽበት መድረክ አጥቷል፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በተፈጠረበት አገር አሁን የምናያቸው ዓይነት አላስፈላጊ የሆኑ ግጭቶች መከሰታቸው ተፈጥሯዊ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ደረጃና በማንፈልገው መጠን በአገሪቱ ውስጥ ግጭቶች እየታዩ ያሉት በዋናነት የአስተሳሰብ ብዝኃነት በመታፈኑ ነው፡፡ መንግሥት ሁለት ወዶ ሊሆን አይችልም፡፡ በአንድ በኩል ሰላማዊ መድረኩን ሙሉ በሙሉ ዘግቶ፣ በሌላ በኩል ደግሞ አመፅን መዝጋት አይቻልም፡፡ የአመፅን መንገድ መዝጋት የሚቻለው ሰላማዊ መድረኩን በመክፈት ነው፡፡ አሁን ባለንበት ተጨባጭ ሁኔታ ቁልፉ ጥያቄ የአስተሳሰብ ብዝኃነት አለመከበር ነው፡፡ በቅርቡ ትልቅ ችግር ውስጥ የገቡት እንደነ ግብፅ፣ ሊቢያና ሶሪያ ያሉ አገሮች ራሳቸውን ለረጅም ዓመታት ከለውጥ አርቀው ነበር፡፡ የአስተሳሰብ ብዝኃነትን ማስተናገድ አቅቷቸው ነው መጨረሻ ላይ ወደማይፈለግ ግጭትና ብጥብጥ የገቡት፡፡ ይኼ ችግር የማይፈታ ከሆነ የኢትዮጵያም ዕጣ ፈንታ ወደዚያ ነው የሚያመራው፡፡

ሪፖርተር፡- በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች የተቃውሞ እንቅስቃሴ መጀመሪያ ሲነሳ መንግሥት የውጭ ፀረ ሰላምና ፀረ ልማት ኃይሎች እጅ ነው ብሎ ነበር፡፡ አሁን ግን ችግሩ በዋነኛነት በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያሉ ሰዎች እንደሆነና እነዚህ ኃይሎች የማቀጣጠል ሚና መጫወታቸውን የሚገልጽ ነው፡፡ በእርስዎ ግምገማ የውስጣዊና የውጫዊ ምክንያቶች ድርሻ እንዴት ይገለጻል?

አቶ ልደቱ፡- በዋናነት ችግሩ የተፈጠረው ውስጥ ባለው ሁኔታ ነው፡፡ ሕዝቡ ውስጥ ባለ ተጨባጭ ብሶት ነው፡፡ ነገር ግን የዚህን ጉዳይ መገለጫዎች ስናይ ብቻውን የቆመ ነው ማለት አይቻልም፡፡ እነዚህን ብሶቶች ከጀርባ ሆነው ለራሳቸው የፖለቲካ አጀንዳ የሚጠቀሙባቸው የውጭ ኃይሎች የሉም ማለት አይቻልም፡፡ ግን እነዚህ ኃይሎች ይህን ዕድል ያገኙት የውስጡን ችግር በአግባቡ፣ በተገቢው ጊዜና ሁኔታ ለመፍታት ስላልተቻለ ነው፡፡ መነሻው ግን የአገር ውስጡ ችግር ነው፡፡ የውጭ ኃይሉ የተመቸ ሁኔታ አግኝቶ ይህችን አገር ወደ መጥፎ አቅጣጫ እንዳያስገባት መፍትሔው ማውገዝና ፕሮፖጋንዳ አይደለም፡፡ መፍትሔው ውስጥ ላለው ኅብረተሰብ ብሶት መነሻ የሆነውን ችግር ከምንጩ ማድረቅ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- ኢሕአዴግ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የጥቂቶችን ጥቅም ለማስከበር የቆሙና የሕዝብ ፍላጎትን መሠረት አድርገው የማይሠሩ ናቸው ሲል ሁሌም ይተቻል፡፡ በቅርቡ በተከሰተው የተቃውሞ እንቅስቃሴም አንዳንድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የውጭ ኃይሎችን አጀንዳ ለማስፈጸም ተንቀሳቅሰዋል ሲል ከሷል፡፡ ችግር ላይ ያለችውን ኢትዮጵያን ለመታደግ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ምን ሚና ሊጫወቱ ይገባል?

አቶ ልደቱ፡- የፖለቲካ ፓርቲዎች የማይተካ ሚና አላቸው፡፡ መንግሥት ዝም ብሎ በአገሪቱ ውስጥ ያሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጅምላ አጀንዳ የለሽ አድርጎ ከማየት፣ ፀረ ሕዝብና ፀረ ልማት አድርጎ ከማየት የተለየ አመለካከት ያላቸው የፖለቲካ ኃይሎች አሉ ብሎ መውሰድ የተሻለ ነው፡፡ እነዚህ ኃይሎች ደግሞ አነሰም አደገም የሚወክሉት ኅብረተሰብ መሬት ላይ አለ ማለት የተሻለ ነው፡፡ ይህን ኃይል የሚያስተናግድ ሥርዓት መገንባት ግድ ነው፡፡ ኢሕአዴግ አማራጭ እኔ ብቻ ነኝ ብሎ የትም ሊሄድ አይችልም፡፡ የተለያዩ የኅብረተሰቡን ፍላጎት የሚወክሉ የፖለቲካ ድርጅቶች ያስፈልጋሉ፡፡ እነዚህ ኃይሎች የሚወከሉበት መድረክ ያስፈልጋል፡፡ በፖሊሲ ውሳኔና በሕግ ማውጣት ጉዳይ ላይ ትርጉም ያለው ተሳትፎ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ በሌላ በኩል ተቃዋሚዎች እስካሁን የሄዱበትን አስተሳሰብ መፈተሽ አለባቸው፡፡ አካሄዳቸውን ማስተካከል አለባቸው፡፡ በሰሞኑ ግርግር እንኳን ስናይ ግርግሩ ወዴት ያደርሰናል? የግርግሩ መነሻ ምንድነው? ተጠያቂው ማነው? ብለው ሳይገመግሙ የተፈጠረውን ችግር ሁሉ ለማባባስና በዚህ ግርግር የመንግሥት ለውጥ እንዲመጣ ሲጠብቁ አይተናል፡፡ ይኼ ስህተት ነው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሰከን ብለው አጀንዳቸውን ከሕዝብና ከአገር ጥቅም ጋር አያይዘው መንቀሳቀስ አለባቸው፡፡ እንቅስቃሴያቸውም ሰላማዊና ሕጋዊ መሆን አለበት፡፡ መንግሥትንም በምክንያት መተቸት አለባቸው፡፡ አስተሳሰባቸው ከመንግሥት ለውጥ ጋር ሁልጊዜ መንጠልጠል የለበትም፡፡ ተጨባጭ የሆነ የፖሊሲ አማራጭ ይዘው ቀርበው መንግሥት የመሆን ዕድል እንኳን ባያገኙ፣ በመንግሥት ላይ ትርጉም ያለው ተፅዕኖ አሳድረው የፖሊሲ ለውጥ ማሻሻያ እንዲመጣ ማድረግ አለባቸው፡፡ የዚህ ዓይነት ባህል ካላቸው ብቻ ነው በሒደት በኅብረተሰቡ ውስጥ ተቀባይነት እያገኙና እምነት እያገኙ ወደ መንግሥትነት ደረጃ የሚበቁት፡፡

ሪፖርተር፡- ፓርቲዎ ኢዴፓ አላምደዋለሁ የሚለውን የሊበራል አስተሳሰብ ለጥቂቶች ጥቅም የቆመና ኢትዮጵያዊ መሠረት የሌለው አድርጎ ገዥው ፓርቲ ያቀርበዋል፡፡ ይህን አቀራረብ እናንተ እንዴት ነው የምታዩት?

አቶ ልደቱ፡- የግራ ፖለቲካ አስተሳሰብ ኢትዮጵያ ውስጥ ማቆጥቆጥ ከጀመረበት ካለፉት 50 ዓመታት ወዲህ የሊበራል አስተሳሰብ ቦታ እያጣ ነው የመጣው፡፡ በጣም ፅንፈኛ የሆነ ወይ ከእኔ ነህ ወይ ከእነሱ ነህ የሚል የፖለቲካ ባህል ነው የሰፈነው፡፡ ነገሮችን ከተለያየ አቅጣጫ አይቶ ሚዛናዊ አስተሳሰብ መያዝ ነውር እየሆነ የመጣበት ባህል ነው የተስፋፋው፡፡ ገዥው ፓርቲ የግራ ፖለቲካ ውጤት ነው፡፡ የሊበራል አስተሳሰብ በዓለም ገዥ የሆነ አስተሳሰብ ነው፡፡ ዛሬ የምንቀናባቸውና ዕርዳታ እንዲሰጡን የምንለምናቸው የሊበራል አስተሳሰብ የሚያራምዱ ናቸው፡፡ የሊበራል አስተሳሰብ በኢትዮጵያ ውስጥ ሕዝባዊ መሠረት እንዳለው ወይም እንደሌለው ሊረጋገጥ የሚችለው ነፃና ፍትሐዊ ምርጫ ስታካሂድ ብቻ ነው፡፡ የሊበራል አስተሳሰብ የሚያራምድን አካል እንደ ሕዝብ ጠላት ፈርጀህ፣ መድረክ አሳጥተኸው፣ አምቀኸው፣ ሐሳቡን ለኅብረተሰቡ እንዳይሸጥ አድርገህ አይጠቅምም ማለት ዋጋ የለውም፡፡ ሁለተኛ አሁን ባለው የኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ የሊበራል አስተሳሰብ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ይሆናል ብለን አናምንም፡፡ የሊበራል አስተሳሰብ በሩቅ ግብ እንደርስበታለን ብለን የምናምንበት ነው፡፡ በሒደት የሚመጣ ነው፡፡ ነገር ግን እዚያ ለመድረስ ከአሁኑ ነገሮች መጀመር አለባቸው፡፡ ገዥው ፓርቲ ኢዴፓ የሚያነሳውን ሐሳብ ሁሌም ሲያጥላላ ነው የኖረው፡፡ ነገር ግን ይኼ ስህተት እንደሆነ የሚያሳዩ ከወቅታዊ የአገራችን ሁኔታ ጋር የተያያዙ ሦስት ምሳሌዎችን ላንሳልህ፡፡ ከኢኮኖሚ አንፃር ደግመን ደጋግመን ስንናገር የነበረው መሠረታዊ የሆነ መዋቅራዊ ሽግግር በኢኮኖሚያችን ካልተፈጠረና በአስቸኳይ ከእርሻ ጥገኝነት ራሳችንን ካላወጣን ያለው ኢኮኖሚ ዝናብ ቀጥ ቢል ችግር ውስጥ እንደሚገባ ነበር፡፡ ዘንድሮ የታየው ይኼ አገር አሁንም በምግብ እህል እንኳን ራሱን እንዳልቻለ ነው፡፡ ሁለተኛ ፌዴራሊዝም የአገሪቱን የብሔር ብሔረሰቦች ጥያቄ ፈቷል፣ ከዚህ በኋላ አንድነታችን የበለጠ ጠንክሯል ተብሎ ሲነገር ነበር፡፡ እኛ ስንል የነበረው ይኼ የፌዴራሊዝም አደረጃጀት በዋናነት ትኩረት ያደረገው ልዩነት ላይ ስለሆነ በሒደት የኅብረተሰቡን አንድነት እያላላው እንደሚመጣ ነበር፡፡ ግጭት እያዳበረ፣ ጤናማ ያልሆነ ፉክክርን ያዳብራል ነው ስንል የነበረው፡፡ አሁን መንግሥት እያስተናገደ ያለው ምንድነው? በብዙ የአገሪቱ አካባቢዎች በታሪክ አይተነው የማናውቀው ግጭት ነው የተከሰተው፡፡ ሦስተኛ ከመሬት ጥያቄ ጋር በተያያዘ መሬት በመንግሥት እጅ መያዙ ለኅብረተሰቡ ነው የሚጠቅመው ሲባል ነበር፡፡ በኦሮሚያ ተቃውሞ ገበሬው እያነሳ ያለው ጥያቄ ምንድነው? መንግሥት ያላግባብ መሬታችንን እየነጠቀና እየሸጠ እሱ እየከበረ እኛ ግን እየደኸየን ነው በሚል ነው ተቃውሞውን ያቀረበው፡፡ እኛ ስንከራከር የነበረው የመሬቱ ባለቤት የሕዝቡ እንዲሆን ነው፡፡ ገበሬው በመሬቱ ላይ የመሸጥ፣ የመለወጥ፣ የማከራየት መብት ኖሮት ጥቅም ያግኝ እያልን ነው ስንከራከር የነበረው፡፡ ስለዚህ ስናነሳቸው የነበሩ ችግሮች ሁሉ አሁን ችግር መሆናቸው ጎልቶ እየታየ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በኦሮሚያ የተነሳው ተቃውሞ በተወሰነ መልኩ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ከምታገኘው ልዩ ጥቅም ጋር ተያይዟል፡፡ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ጋር ያላት ግንኙነት በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠበትን መንገድና አተገባበሩን እንዴት ያዩታል?

አቶ ልደቱ፡- በእኛ እምነት ሕገ መንግሥቱ ብዙ ክፍተቶች አሉት፡፡ የሕገ መንግሥት ማሻሻያ ማድረግ ነውር አይደለም፡፡ 25 ዓመት ከተጓዘ በኋላ ይኼ ሕገ መንግሥት ያሉበት ክፍተቶች ምንድን ናቸው? መቀየር ያለባቸው ነገሮች አሉ ወይ? ብሎ መገምገም አለበት፡፡ አሁን ግን ሕገ መንግሥቱ እንደ መለኮታዊ ሰነድ ነው እየታየ ያለው፡፡ የአዲስ አበባና የኦሮሚያ ጉዳይ አንዱ ክፍተት ነው፡፡ በግልጽ ባለመቀመጡ ብዥታ ፈጥሯል፡፡ የጥቅም ግጭትም ፈጥሯል፡፡ ትልቅ የፖለቲካ ጉዳይም እየሆነ ነው፡፡ ለአገርና ለሕዝብ በሚጠቅም መልኩ ግልጽ መደረግ አለበት፡፡ ካስፈለገም እስከ ሕገ መንግሥታዊ ማሻሻያ ድረስ መሄድ ያስፈልጋል፡፡ ወደፊት ሊመጡ የሚችሉ ችግሮች ተጢነው አይደለም ሕገ መንግሥቱ የተረቀቀው፡፡ በወቅቱ ኢሕአዴግ ይዞት የነበረው አስተሳሰብ ነው በቀጥታ ወደ ሕገ መንግሥትነት እንዲቀየር የተደረገው፡፡ የብዙ ፓርቲዎች አስተሳሰብ ምን እንደሆነ ግንዛቤ ውስጥ ገብቶ፣ በቂ የሆነ ውይይት ተደርጎ የተዘጋጀ ሰነድ አይደለም፡፡ ሕገ መንግሥት ግን በባህርይ መሆን ያለበት እንደዚያ ነው፡፡ ይኼን በሒደት ማስተካከል አስፈላጊና ወቅታዊ ነው፡፡ ከመሬት ጥያቄ፣ ከአዲስ አበባና ኦሮሚያ ግንኙነትና የፌዴራል አደረጃጀቱ እስከ መገንጠል ጥያቄ ድረስ ጋር በተያያዘ ያለው አንድምታ በደንብ በድጋሚ መዳሰስ አለበት፡፡ አንዳንዶቹ የሕገ መንግሥት ድንጋጌዎች ኢትዮጵያን እንደ እስራኤልና ፍልስጤም ሁኔታ በሩቅ ሒደት ውስጥ የሚያስገቡ ናቸው፡፡ ወደዚያ አቅጣጫ ከመግባታችን በፊት ቆም ብለን ማሰብና የአጠቃላይ ሕዝቡን ስምምነት ያገኘ ሕገ መንግሥት ማግኘት መቻል አለብን፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ ተገቢውን ትኩረት ማግኘት አለበት፡፡ ነገር ግን አስተማማኝ በሆነ አቅጣጫ ውስጥ እንዲቀመጥ የሚያደርግ መፍትሔ መሰጠት አለበት፡፡

ምንጭ – ሪፖርተር

The post ‹‹በአገሪቱ ውስጥ ግጭቶች እየታዩ ያሉት በዋናነት የአስተሳሰብ ብዝኃነት በመታፈኑ ነው›› appeared first on Zehabesha Amharic.

በኡማህጅርና በታች በርማጭሆ በደቡብ ተከዜ ወንዝ አካባቢ ውጊያ ተደረገ |በወልቃይት ገበሬዎች እና የውስጥ አርበኞች የሕወሓት ሰራዊትን መከቱ

0
0

clash

ከልዑል ዓለሜ

ወልቃይት ጠገዴና ጠለምት….. ከትግራይ አስገዶ_ ጼምበላ እንዲሁም ከታህታይ አዲያቦ በመጡ ልዩ ሐይል እና ታጣቂዎች ቢወረሩም ቆራጡ የአማራ ኢትዮጵያዊ ገበሬና የዉስጥ አርበኞች አልበገር ባይነታቸዉን እያስመሰከሩ ይገኛሉ፡፡

በአካባቢዉ የሚኖሩ ልዩ ሐይልና ታጣቂዎችን ከማስጠንቀቅ አንጻር በቤተሰብ በኩል ከእኩይ ተግባራቸዉ እንዲቆጠቡ ተጠይቀዉ አሻፈርን ባሉ 3 ግለሰቦች ላይ እርምጃ መወሰዱን ያሳወቁት የዉስጥ አርበኞች አያይዘዉ በዳንሻ፣ በሳንጃ፣ በሶርቃ፣ በወልቃይት ጠገዴ እና በጠለምት እንዲሁም በሁመራ ዙሪያ 29 ከትግራይ ክልል የመጡ ወራሪዎች ላይ ተመሳሳይ እርምጃ መውሰዳቸው ተሰምቷል::

በተያያዘ ዜና በትናንትናዉ እለት በወያኔና በነጻነት ሐይሎች መካከል በኡማህጅርና በታች በርማጭሆ በደቡብ ተከዜ ወንዝ አካባቢ ከባድ ዉጊያ መደረጉን ታማኝ ምንጮች ጠቅሰዋል።

ለዘ-ሐበሻ የሚደርሱ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት በዚህ አካባቢ የአማራ ወጣቶች ንቅናቄና የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይል በተለያዩ ጊዜያት በሥርዓቱ ሰዎች ላይ እርምጃ ሲወስዱ ቆይተዋል::

ይህ በ እንዲህ እንዳለ የአማራ ዲሞክራሲያዊ ኃይል ንቅናቄ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ መሆኑ ተሰምቷል:: ከኤርትራ ሙሉ በሙሉ ጠቅልሎ ወጥቷል የሚባለው ይኸው ንቅናቄ በጎንደር በኩል በተለያዩ ጊዜያት የሽምቅ ውጊያዎችን እንደሚያደርግ በተደጋጋሚ እየተዘገበ ነው:: ንቅናቄው ሰሞኑን በወልቃይት ጠገዴ ጸለምት ዙሪያ ያወጣው መግለጫ እንደሚከተለው ተስተናግዷል::

ከአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይል ንቅናቄ /አዴሃን/ የተሰጠ አገራዊ ጥሪ
መጋቢት 14 ቀን 2008 ዓ• ም
ለአማራው ቆሜያለሁ፣ አማራውን ከጥቃት፣ ከውርደትና ከጉስቁልና እታደጋለሁ ብሎ በአማራ ህዝብ ትክሻ ላይ የተፈናጠጠው ብአዴን ማንነቱ የሚፈትንበት ታሪካዊ ጊዜ ተፈጥሯል። ወልቃይት፣ ጠገዴ፣ ዳንሻ ላይ የተነሳው የማንነት ጥያቄ በህወኃት ልዩ ኃይልና በፌደራል ፓሊስና በመደበኛ ሰራዊት ሲደበደብ ዝምታ የመረጠው ብአዴን ከወያኔ ባልተናነሰ ሁኔታ የአማራ ህዝብ ቀንደኛ ጠላት መሆኑን እያሳዬ ነው። እነ አባይ ወልዱ ለህዝባቸው ቀንና ሌሊት አማራን ሲያሳድዱ፣ ሲጨፈጭፉና ሲያፈናቅሉ እነ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ጣና ዳር ዘና ብለው በአማራ ህዝብ ስቃይ የደስታን ኑሮ ከዚህ በኋላ የሚኖሩ መስሏቸው ከሆነ ተሸውደዋል።
አሁን የአማራ ህዝብ ትግል ከራስ ይጀምራል። ማንኛውንም የወያኔ ጆሮ ጠቢ፣ አቃጣሪ፣ አለቅላቂና አሽቃባጭ አማራን መመንጠር እንጀምራለን። ቤታችን ሳናፀዳ ሌላውን ለማፅዳት መሞከር ብዙ ኪሳራ ስላለው ሆዳቸው ሞልቶ በህዝባችን ሞት በሚያጋሱ የብአዴን ካድሬዎች ላይ ሰይፋችን ይመዘዛል። ብአዴን የአማራ ተወካይ ወይም የትግራይ ተወካይ መሆኑን በግልፅ ያሳይ። ከዚህ በኋላ በአማራ ሞትና ስቃይ እንጀራ እየበሉ ለመኖር የተሰለፉ የብአዴን ካድሬዎች ወዮላቸው። ለወገን ሳይሰሩ በወገን ላብ መኖር ፈፅሞ አይቻልም። ብአዴን ከህወኃት ጋር ያለው ጋብቻ ይፍረስ ወይም ጓዛቸውን ጠቅልለው መቀሌ ይግቡ። የአማራ መሬት ሲነጠቅ፣ ህዝቡ ሲፈናቀል፣ ሲሰደድና ሲገደል እያዬ የተኛ መሪ ስለ አማራ ለማውራት የስነ ምግባርም ሆነ የሞራል ብቃት የለውም። አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ማንነታቸው የሚለካበት ወሳኝ የታሪክ ዘመን ጋር ተፋጠዋል። ምርጫቸውም ሁለት ብቻ ነው። ስልጣን፣ ክብር፣ ዝና፣ ደስታ ይቅርብኝ ብለው እንደ ሙሴ ከህዝባቸው ጋር መከራን ለመቀበል መምረጥ ወይም ስልጣን፣ ብርና ክብር ይበልጥብኛል ብለው ከወያኔ ጋር በማበር ህዝባቸውን መጨፍጨፍ።
የአማራ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ/ አዴሃን/ የብአዴንን አስቸኳይ ውሳኔ ይፈልጋል። በአምስት ቀናት ውስጥ ብአዴን በወልቃይት፣ ዳንሻና ሌሎችም የአማራ መሬቶች ላይ በህዝባችን ላይ እየደረሰ ያለውን የወያኔ ፋሽስታዊ ጭፍጨፋ በማውገዝ ከህዝብ ጎን በመቆም ወያኔን በቃ በማለት የአቋም መግለጫ ካላወጣ አዴሃን የአማራን ህዝብ እየደረሰበት ካለው የዘር ማጥፋት ወንጀል ለመታደግ አሁን እያደረገ ካለው ትግል በላይ አድማሱን አስፍቶ የዘረኞችን ሰንሰለት በመበጣጠስ አኩሪ ታሪክ ሊሰራ ተዘጋጅቷል። ይህን ለማድረግ ደግሞ ወኔውም፣ አቅሙም አለን።
በመሆኑም አዴሃን የአማራን ህዝብ ከጭፍጨፋ ለመታደግ መላው የአማራ ህዝብና ሌሎችም የአገራችን ህዝቦች በስርዓቱ ላይ በጋራ እንዲነሱ አገራዊ ጥሪውን ያቀርባል። ከዚህ በላይ ትዕግስት፣ ከዚህ በላይ መከራ፣ ከዚህ በላይ ስደትና ሞት አያስፈልግም። ወያኔን በቃ ብለህ ህዝባችን ተነስ። አማራው በያለህበት በመደራጀት በወያኔ ሎሌዎች ላይ እርምጃ መውሰድ ጀምር። አዴሃን ትናንትም፣ ዛሬም ወደፊትም ለህዝባችን አስፈላጊውን ሁሉ መስዋዕትነት በመክፈል ላይ ይገኛል። ህዝባችን በያለበት አዴሃንን በመቀላቀል የነፃነት ትግሉን ታቀጣጥል።
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!!!
ድል ለአማራ ህዝብ!!!
ድል ለመላው የአገራችን ህዝቦች!!!

The post በኡማህጅርና በታች በርማጭሆ በደቡብ ተከዜ ወንዝ አካባቢ ውጊያ ተደረገ | በወልቃይት ገበሬዎች እና የውስጥ አርበኞች የሕወሓት ሰራዊትን መከቱ appeared first on Zehabesha Amharic.

“የመንግሥቱ ኃ/ማርያም የትምህርትና ዕውቀት ውስንነት እንዳለ ሆኖ፤ የተፈጥሮ ብሩህ አዕምሮውን ግን ለመካድ አይቻልም።” –ፕ/ር ገብሩ ታረቀ

0
0

mengistu hailemariam

“የመንግሥቱ ኃ/ማርያም የትምህርትና ዕውቀት ውስንነት እንዳለ ሆኖ፤ የተፈጥሮ ብሩህ አዕምሮውን ግን ለመካድ አይቻልም።” – ፕ/ር ገብሩ ታረቀ

ፕሮፌሰር ገብሩ ታረቀ፤ ስለ የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዚደንት መንግሥቱ ኃ/ማርያም የአገዛዝ ዘመን ጅምርና ፍጻሜ ይናገራሉ። ፕሮፌሰር ገብሩ “The Ethiopian Revolution: War in the Horn of Africa” እና “Ethiopia: Power and Protest: Peasant Revolts in the Twentieth Century” መጻሕፍት ደራሲ ናቸው።

The post “የመንግሥቱ ኃ/ማርያም የትምህርትና ዕውቀት ውስንነት እንዳለ ሆኖ፤ የተፈጥሮ ብሩህ አዕምሮውን ግን ለመካድ አይቻልም።” – ፕ/ር ገብሩ ታረቀ appeared first on Zehabesha Amharic.

“መንግሥቱ ኃ/ማርያም የአገራቸው ናፍቆትና ፍቅር አሁንም በልባቸው የነደደ ነው፤ አለ።” –ገነት አየለ

0
0

ጋዜጠኛና ደራሲ ገነት አየለ፤ ስለ የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዚደንት መንግሥቱ ኃ/ማርያም የስደት ሕይወት ይናገራሉ። ጋዜጠኛ ገነት አየለ “የሌተናንት ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ትዝታዎች” መጽሐፍ ደራሲ ናቸው።

The post “መንግሥቱ ኃ/ማርያም የአገራቸው ናፍቆትና ፍቅር አሁንም በልባቸው የነደደ ነው፤ አለ።” – ገነት አየለ appeared first on Zehabesha Amharic.

የዲሞክራቲክ ኮንጐን ፖለቲካዊ ትርምስን ለመፍታት ለፖለቲካ ትግል ቆርጠው ከአሜሪካ ወደ አገራቸው ለመዝመት የተነሱት ኢንቨስተር ውጥን ሲቃኝ |በድምጽ

0
0

የዲሞክራቲክ ኮንጐን ፖለቲካዊ ትርምስን ለመፍታት ለፖለቲካ ትግል ቆርጠው ከአሜሪካ ወደ አገራቸው ለመዝመት የተነሱት ኢንቨስተር ውጥን ሲቃኝ | በድምጽ

የዲሞክራቲክ ኮንጐን ፖለቲካዊ ትርምስን ለመፍታት ለፖለቲካ ትግል ቆርጠው ከአሜሪካ ወደ አገራቸው ለመዝመት የተነሱት ኢንቨስተር  ውጥን ሲቃኝ | በድምጽ

The post የዲሞክራቲክ ኮንጐን ፖለቲካዊ ትርምስን ለመፍታት ለፖለቲካ ትግል ቆርጠው ከአሜሪካ ወደ አገራቸው ለመዝመት የተነሱት ኢንቨስተር ውጥን ሲቃኝ | በድምጽ appeared first on Zehabesha Amharic.


 ዝክረ ዲበኩሉ (1) –መስፍን ማሞ ተሰማ (ከሲድኒ)

0
0

ሰንበተ ጉዳ ነበር ቀኑ። ከመኖሪያዬ አካባቢ እርቄ በአንድ የባህር ዳርቻ በመንሸራሸር ላይ ነበርኩ። ያው እንደተለመደው ብቻዬን።

ሰማያዊው ሰማይ ከአፅናፍ አፅናፍ ተንጣሏል። አልፎ አልፎ በሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ የተሳሉ እሚመስሉ ምትሃታዊና ምስጢራዊ ምስሎች በነጭ ደመና መልክ ተቀርፀው ይታያሉ።

ለምሳሌ አንደኛውን የደመና ቅርፅ በአንድ ወገን ሲያዩት ለመዝለል የተዘጋጀ የተቆጣ አንበሳ ይመስላል። አይንን ከደን አድርገው ከፍተው ሲመለከቱት ደግሞ የአንበሳው ጋሜ የቴዎድሮስን ሹርባ መስሎ፤ መልኩም ተቀይሮ  መይሳውን ሆኖ ቁጭ! በትዝብት አይን ቁልቁል እየተመለከተ። ታዲያ፤

“እዚህ ፈረንጅ ሀገር ምን ትሰራለህ?” ብለው ጠየቁኝ፤ ድንገት ሳላስበው።

“ተሰድጄ ነው” አልኳቸው፤ ድንጋጤ መላ አካላቴን እየወረረኝ።

“የምን ስደት ነው፤ ሽሽት በለኝ እንጂ። ኢትዮጵያን ሽሽት። ችግሯን ሽሽት። ሰቆቃዋን ሽሽት። ዋይታዋን ሽሽት። ጥሪዋን ሽሽት። ድህነቷን ሽሽት። እንጂ ስደት አይደለም። ስደት ማለት በእኛ ሀገር በእኛ ቋንቋ እኛ ስናውቀው፤ ከጭልጋ ቡልጋ፤ ከቢቸና ደንቢያ፤ ከፎገራ ላስታ፤ ከወለጋ መቱ፤ ከጨርጨር ለገሃር፤ ከቃሮራ ገዋኔ፤ ከቦረና የጁ፤ ከሽሬ ደብረ ብርሃን፤ ከሲዳሞ ሊማሊሞ፤ . . . እንጂ፤ ከአዱ ገነት ፈረንጅ ሀገር አይደለም። ያልታደለች እናት። የወላድ መካን። ፈሪ ትውልድ። ታሪክ ከሃዲ ትውልድ። ታሪክ አዋራጅ ትውልድ። አፅም ወቃሽ ትውልድ። በአርበኞቹ ተሳላቂ ትውልድ። . . . እና ተሰድጄ ነው አልከኝ? ስደት ነው፤ ሽሽት?” ጠየቁኝ መይሳው በሚያስገመግም ድምፅ።

ዝም። ድርግም። ማን ለአፄ ቴዎድሮስ መልስ ይሰጣል? ቀና ብዬ መመልከት ፈራሁ። ሀፍረት አሸማቀቀኝ። ኩርማን አከልኩ። አንገቴን አዙሬ አይኔን ከቴዎድሮስ አነሳሁና ወዲያ ማዶ ወዳለው ደመና ወረወርኩ።

ራሳቸው ናቸው። አፄ ዮሐንስ። ፈረሳቸው ላይ እንደተቀመጡ፤ ግራ እጃቸውን የጎራዴያቸው አፎት ላይ አሳርፈው በትዝብት ይመለከቱኛል።

ወይ ዘንድሮ?! ዝም አሁንም። ማን አፄ ዮሐንስን በሙሉ አይኑ ይመለከታል? አይኔን ሰበርኩ። ይበልጥ አፈርኩ። ይበልጥ ኩርማን አከልኩ። ሱዳን ታወሰችኝ። መሀዲ ታወሰኝ። በአፄ ዮሐንስ ታላቅ ጦር  የራደው የተርበደበደው ከሊፋ ከእምዱራማን ቤተመንግሥት እንደ ወላድ ምጥ ይዞት ሲያማምጥ ከመተማ ተወርውረው ደረሱብኝ እያለ ሲታመስ ሲተራመስ ታየኝ። አይ ጊዜ!  ደግሞም ዛሬ፤ በዚህ ዘመን፤ በእኔ ዘመን – የደም መሬት በድርድር . . . ለአል በሽር? አኬክዳማ! . . . ምነው እምዬ ማርያም የጨው ሀውልት አድርገሽኝ በዚህ ፀሀይ ሟሙቼ ከዚህ ባህር በገባሁ?

“መተማ ላይ የወደቅሁት ለአንተ እኮ ነው። ከእኔም በፊት መቅደላ ላይ ወንድሜ ቴዎድሮስ የወደቀው ለአንተው ነው። ተከብረህ እና ታፍረህ በሀገርህ እንድትኖር። በኢትዮጵያዊነትህ እንድትኮራ። በአባቶችህ መስዋዕትነት እንድትኮራ። በታሪክህ እንዳታፍር። ታሪክ ኖሮህ፤ ዳር ድንበር ኖሮህ ማንነትህ እንዲከበር። እንጂማ የጦረኝነት ሱስ ይዞን አልነበረም። ከሰሜን ደቡብ፤ ከምስራቅ ምዕራብ፤ ከሀገር ወራሪ፤ ከአንድነት አጥፊ ጋር የተሳየፍነው። ደግሞም ከሀገር በቀል የጎጥ ፊታውራሪ ጋር ስንተናነቅ የኖርነው። ጥለን የሞትነው፤ ለአንተ ነበር። ክልል ሳይሆን ሀገር እንዲኖርህ። መንደራዊ ሳይሆን ሀገራዊ መለያ፤ ዜግነታዊ መከበሪያ እንዲኖርህ። ያስረከብንህን ነፃነት እንድትጠብቅ። በሠንደቅ ዓላማህ እንድትዋብ። የኢትዮጵያ መመኪያም እንድትሆን። ከእንግሊዙ፤ ከቱርኩ፤ ከግብፁ፤ ከመሀዲስቱ፤ ከጣሊያኑ. . . ጋር የተናነቅነው ጥለን የወደቅነው፤ በአጥንታችን ካስማ በደማችን ሊሾ  ኢትዮጵያን ያቆምነው  ለአንተ ነው።  ቴዎድሮስ በመቅደላ እኔ በመተማ። ከኛም በፊት የእኛ አያት ምንጅላቶች። ከመተማም በሗላ ቢሆን አድዋ ላይ . . .” አሉና አፄ ዮሐንስ ቀኝ እጃቸውን ወደ ሰሜን አወናጨፉ። የእጃቸውን አቅጣጫ ተከትዬ ስመለከት አፄ ምኒሊክ የጦር ለምዳቸውን እንደለበሱ፤ ፈረሳቸው ላይ ጉብ ብለው፤ አይኖቻቸው አንዳች ምትሃታዊ ድባብ ለብሰው ተመለከትኩ። ከሗላቸው አያሌ ጦረኞች ይታዩኛል። ከጎናቸው ጎልቶ የታየኝን ግን ማመን አቃተኛ። አፍጥጬ ስመለከተው ፈገግ አለልኝ። የአራዳው ግዮርጊስ ራሱ ነው፤ ጦሩን እንደያዘ።

“ተናገር እንጂ። በስደት ስም ማነው ሽሽትን ያወረሰህ? በታሪክ ስም ማን ነው የእንቧይካብ ታሪክ የካበልህ? ማን ነው ወኔህን የሰለበህ? ማን ነው በኢትዮጵያዊነትህ እንድትሸማቀቅ ያደረገህ? ኢትዮጵያዊነትህን በመንደር፤ በጎጥ፤ በዘርማንዘር መታወቂያ ያስለወጠህ ማን ነው? ማን ነው ኢትዮጵያዊነቴ ተቀጥላ እንጂ ውልደቴ መታወቂያዬ ክብሬም አይደልም እንድትል ያደረገህ? የሀገርህን ዳር ድንበር በጠበቅን፤ ለኢትዮጵያ ሉዐላዊነትና ክብር በሞትን፤ ወራሪዎቿን በባንዲራዋ ድል ባደረግን፤ በባዶ እግራችን ቆላ ወርደን፤ ደጋ ወጥተን፤ ተራራ ቧጥጠን፤ ደን ሰንጥቀን. . . የኢትዮጵያን አንድነት፤ የህዝቧን ህብረት በጠበቅን . . . ዛሬ ሹምባሽና የታሪክ ከሃዲ “ነፍጠኛ ሲለን” “ቅኝ ገዥ” ገለመሌ እያለ ስም ሲሰጠን፤ በኢትዮጵያ ላይ ሲሳለቅ፤ በአንድነቷ ሲዘባበት፤ አርበኞቿን ሲያንጓጥጥ፤ ታሪኳን ሲዘረጥጥ . . . እምቢኝ ለነፃነቴ፤ እምቢኝ ለመብቴ፤ እምቢኝ ለኢትዮጵያዊነቴ፤ እንቢኝ ለታሪካዊው ታሪኬ ብለህ ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትህ . . . በሀገርህ አድባር፤ በሀገር አውጋር በሀገርህ መኻል እንደመፋለም እንደመሞት. . . . ሽሽትን ስደት ብሎ ያስተማረህ ማን ነው? ጠየቁኝ የምኒልክ ክንድ የኢትዮጵያ ግርማ፤ የኢትዮጵያ ሞገስ፤ የጀግና አርማ ራስ ጎበና ዳጬ በዚያ ቁመታም፤ በዚያ ግርማ ሞገስን ከኩራት ጋር በተላበሰው ፈረሳቸው ላይ ሆነው ከምኒሊክ ጎን እየቆሙ።

ጉድ ፈላ ዘንድሮ! ዝም። ድርግም። ማን ለጎበና መልስ ይሰጣል? ጨነቀኝ። ምነው እንደለመድኩት አልጋዬ ውስጥ ስገላበጥ በዋልኩ ኖሮ? አሁን ለጎበና ምን ብዬ ነው መልስ የምሰጣቸው? በእኔ ዘመን በእኔ ትውልድ በሆነው ቱማታ ሁሉ ተሸማቀቅሁ። በራሴ አፈርኩ። ኩርማን ሥራዬ አሳፈረኝ። ኩርማን “ራዕዬ” ቅዠቱ ታየኝ። ተግባሬም ሆነ የነገር አታሞዬም ኩርማንነታቸው ገዝፎ ታየኝ። ኩርማን መሆኔ ታወቀኝ። . . . ጎበናን ቀና ብዬ ማየት አሸማቀቀኝ። እምዬ ምኒሊክንስ የማይበት ምን አይን አለኝ? እንግዲህስ ለምኒልክ ልሳኔን የምከፍትበት ምንስ የሞራል ብቃት አለኝ? በእኔ ትውልድ በዘመኔ በቀድሞው ትውልድ (ግርማዊነታቸውንና መንግሥታቸውን ጨምሮ) ገድል እና ሥራ ላይ እንደ ዛር አናታቸው ላይ ከመስፈር፤ በነገር ከመንዘርዘር፤ ነገር ከማባዘት፤ ነገር ከመጎንጎን፤ በነገር ከመራቀቀር፤ ነገር ከመሰንጠቅ. . . በቀር በትውልዴ ለትውልድ የሚያልፍ  ምን ፈየድኩ? ምን ገነባሁ? የተገነባውን ግን ሳፈርስ. . . ሳስፈርስ. . .ጥላቻን ከቂም በቀል ጋር ስኮተኩት፤ ሳስኮተኩት፤ የጎጥ ባንዲራ ሳቀልም. . .የጎጥ ባንዲራ ስሸከም፤ የጥበት የጥላቻ፤ የቂም በቀል አራማጅና ተምሳሌ ሐውልት ሳቆም. . . ሐውልት ሳስቆም ግን ኖሬያለሁ። በሀይማኖት ቢሉ በፖለቲካ፤ በማህበራዊ ቢሉ በግል የገባሁበት ሀገራዊ ኪሳራ እንደውቅያኖሱ ተንጣልሎ ታየኝ። እግዚኦ!!. . .ምነው ቅዱስ ሩፋኤል ዛሬ እግሬን በሰባበረው ኖሮ? . . . አሁን ለጎበና ምን ብዬ ነው መልስ የምሰጣቸው? ተሰድጄ ነው ሸሽቼ? ለኢትዮጵያ ስል ነው ለራሴ? እያልኩ ሳሰላስል፤ ከባህሩ አንደኛ ወገን የጡሩንባ ድምፅ ሰማሁ።

ሰውነቴን ሰቀጠጠኝ። የጦርነት መለከት የተነፋልኝ መሰለኝ። የጥሪ ድምፅ የቀረበልኝ መሰለኝ። ዞር ብዬ ተመለከትኩ። የባህሩን ወደብ በመልቀቅ ላይ የነበረች እጅግ ግዙፍ መርከብ ነበረች ጡሩንባዋን ያስተጋባችው። የእኔን ቁመት የሚያካክል ፅሁፍ ጎኗ ላይ ይነበበኛል። “ጣይቱ ቡጡል የባህር ሃይል ብርጌድ – ኢትዮጵያ ” ይላል። የመርከቧ ስም መሆኑ ነው።  “ጉድ ፈላ ዛሬ!” አልኩ ለራሴ። አይኔን ማመን እያቃተኝ። እየተርበተበትኩ ቀና ብዬ ተመለከትኩ። አፄ ቴዎድሮስ በቦታው የሉም። ደመናውም የለም። አፄ ዮሐንስን ወደ አየሁበት ብዞር እሳቸውም እዛ የሉም። ደመናውም የለም። አፄ ምኒሊክን ወደ አየሁበት ወደ ሰሜን ባቀና እሳቸውም እዛ የሉም፤ ራስ ጎበናም የሉም። እዚያ ላይ አይቼው የነበረው ሁሉ ተቀያይሮ፤ ደመናው ደግሞ በእጥፍ ገዝፎ ተመለከትኩ። ዶፍ ሊወርድ ይሆን እንዴ? ምፅዐት ሊመጣ? . . . ..”ሊነጋ ሲል ይጨልማል” አይደል እሚሉት  እኒያ ጥንታውያኑ . . . ጠቢባኑ።

ድንገት ደግሞ ሶስቱም ፈረሶቻቸው ላይ እንደተቀመጡ፤ እጅ ለእጅ ተያይዘው፤ የጀግንነት ግርማ ሞገስን ተላብሰው፤ ከወዲያ ማዶ ሆነው ተመለከታኳቸው። አፄ ቴዎድሮስ፤ አፄ ዮሐንስ፤ አፄ ምኒሊክ፤ እነ ጎበና ደጀን ቆመው። ። ከበላያቸው ቀስተ ደመና ይታየኛል። ቀለሞቹ አረንጓዴ፤ ቢጫ፤ ቀይ ናቸው። ቀስተ ደመና ነው ወይስ የኢትዮጵያ ባንዲራ? ደግሞ ይውለበለባል እንዴ? ከሶስቱ ጀርባ ደግሞ በቅድመ ታሪክ የማውቃቸው ነገስታት፤ እነ ላሊበላ፤ እነ ፋሲለደስ እና ሌሎችም ከነአጀባቸው በደጀንነት ቆመቀው ታዩኝ። አራዳው ግዮርጊስ ግን ፈረሱ ላይ አልነበረም። ክንፎቹን ዘርግቶ ከበላያቸው ያንዣብባል። በተዘረጋው ቀኝ እጁ በያዘው ጦር ላይም የሚውለበለብ ቀስተ ደመናዊ ባንዲራ ይታየኛል። እሱም የያዘው የኢትዮጵያን ባንዲራ ነው እንዴ? የሚያመለክተውም ወደ ምስራቅ? ጉድ’ኮ ነው! አንዳች ምስጢራዊ መልእክት አይኖቹ ውስጥ ያነበብኩ መሰለኝ። ምን ይሆን ሊነግረኝ የፈለገው? ወዴት ይሆን ይህ ሁሉ መሰናዶ?

ለሁለተኛ ጊዜ የመርከቧ ጡሩንባ አስተጋባ። ሰላማዊውን ውቅያኖስ እያተራመሰች አፍንጫዋን ወደ ምስራቅ አቀናች። በዛ ግዙፍ ሰውነቷ ባህሩን እየሰነጠቀች አንዳች ግርማ ሞገስን እና በራስ መተማመንን ስሜት ለተመልካቾቿ ሁሉ እየረጨች ተፈተለከች።

ቀና አልኩኝ። ያ ክምር ደመና ደረቱን ገልብጦ እየተጀነነ፤ እየተንጎማለለ ጉዞ ጀምሯል። የት ሄዱ? ምነው አይታዩኝም? አንዳቸውም የሉም። አፄ ቴዎድሮስ፤ አፄ ዮሐንስ፤ አፄ ምኒሊክ፤ ራስ ጎበና፤ እነ ላሊበላ፤  የአራዳው ግዮርጊስ. . . ሁሉም የሉም። ተያይዘው የት ገቡ? ደመናው እየተጓዘ ነው። መርከቧን እየተከተለ። ደመናው የጀግኖቹ የጦር መንኮራኩር መስሎ ታየኝ። ይሆን እንዴ? . . .

አይኔን ወደ መርከቧ አቀናሁ። እየራቀች፤ እየራቀች እያነሰች፤ የምስራቅን አቅጣጫ ይዛ ስትጓዝ ታየችኝ። ደመናውስ? ደመናውም ከበላይዋ በኩራት ይቀዝፋል። ሄዱ፤ ነጎዱ፤ አድማስ ጥግ ደረሱ። ይሄኔ አንበሳው የኢትዮጵያ ኩራት፤ የኢትዮጵያ ጀግና ጎበና ዳጬ ወደ እኔ ዞረው የተመለከቱ መሰለኝ። ነጭ ጥርሳቸውን ብልጭ አድርገው ከትዝብት ፈገግታ ጋር ለቅፅበት አተኩረው ያዩኝ መሰለኝ። ስለምን ይሆን እንዲያ የተመለከቱኝ? አዝነውብኝ? አፍረውብኝ? ወይስ አዝነውልኝ? . . . ደንዝዤ ቀረሁ።  መርከቧም ደመናውም ከአድማስ ወዲያ ተሻገሩ። ከአይኔ ጠፉ . . . እኔም እራሴን ይዤ በራሴ ሀሳብ ጠፋሁ።

መቼ እንደሆን ባላውቅም ወደ ራሴ ስመለስ ባህር ዳር መቀመጤን ጊዜውም ደንገዝገዝ ማለት መጀመሩን አስተዋልኩ። ጉድ ነው! የሆነውን ሁሉ አስታወስኩ። ምን ነበር ያየሁት? . . . ወይስ አላየሁም? ድንቅ’ኮ ነው ባካችሁ! አሁን ያየሁትን ለሰው ባወራ ማን ያምነኛል? ይህንን ለአራዳ ልጆች ብነግራቸውስ ምን ይላሉ?። መቼስ ፈረንጅ አምላኩ ይህንን ሲሰማ አንደኛህን ለይቶልሃል ነው የሚለኝ። ካልሆነም አንድ ሐሙስ ቀርቶሃል። ግን እርግጠኛ ነኝ አስተማሪ አለሙ ያምነኛል።  እትዬ አቻሜም ያምኑኛል። ዋቅጅራም ያምነኛል። ኒቂሴም ታምነኛለች። ሸምሱም ያምነኛል።

ከተቀመጥኩበት ተነስቼ በዝግታ ወደ ባቡር ጣቢያ የሚወስደውን መንገድ ያዝኩ። ህሊናዬ በጥያቄ ተወጥሯል። ስደት ነው ሽሽት? . . . ስደት ነው ሽሽት? የትኛው ነው የእኔ?. . .

———– ተ ፈ ፀ መ ————–

በያለንበት ቸር ይግጠመን!

{ይህ ፅሁፍ አስቀድሞ በየካቲት 1994 ዓ/ም (ፌብሩዋሪ 2002) በሲድኒዋ “ድንቅነሽ” መፅሔት ላይ ተነበበ። በዚህ አቅርቦት ጥቂት ቃላት ተነቅሰዋል/ተጨምረዋል እንጂ}

መጋቢት 2008 ዓ/ም (ማርች 2016)

ሲድኒ አውስትራሊያ

አስተያየት ቢኖርዎ፤ mmtessema@gmail.com

comment_stage_5

The post  ዝክረ ዲበኩሉ (1) – መስፍን ማሞ ተሰማ (ከሲድኒ) appeared first on Zehabesha Amharic.

ሰበር ዜና! የመለስ ፋውንዴሽን ተዘጋ! –ነፃነት ዘለቀ

0
0

arton390ይህን የመለስን ፋውንዴሽን መዘጋት በሚመለከት “ዜና ላድርገው ወይንስ መጣጥፍ?” ብዬ ብዙ ተጨነቅሁ፡፡ ዜናም ላድርገው መጣጥፍ መቼም እስካሁን የቀደመኝ እንደማይኖር ተስፋ አለኝ፡፡ ወደሰበር ዜናው ላምራ፡፡

የሕዝብ ዋይታ የፈጠረው ዕንባና ያፈሰሰው የንጹሓን ደም ፈጣሪ ዘንድ ጮኸው ባመጡት የጸሎት መልስ ለገሠ ዜናዊ – በፖለቲካዊ የብዕር ስሙ መለስ ዜናዊ – የሚባለው ሽፍታ  የዛሬ አራት ዓመታት ገደማ ከሥሩ ተግነድሶ አይሞቱ አሟሟት መሞቱ የሚታወስ መሆኑን የገለጸልን ይህን ሰበር ዜና ያደረሰን ግለሰብ በመቀጠልም በዚህ ዱርዬ ሀገር አጥፊ ስም ተቋቁሞ የነበረውና ካዛንቺስ አካባቢ የሚገኘው ፋውንዴሽን ላልተወሰነ ጊዜ መዘጋቱን ጠቁሟል፡፡

አቶ ነፃነት ዘለቀ የሚባሉ – ባጋጣሚ ሆኖ የዜናውም ዘጋቢ እርሳቸው ናቸው – የአዲስ አበባ ኗሪ ዛሬ መጋቢት 16 ቀን 2008 ዓ.ም – በዕለተ ኪዳነ ምሕረት – ከቤታቸው ወደ ሥራቸው ለመሄድ ዝምቡን እንኳን እሺ የሚልለት ሰው ሳይኖር ኦናውን ተገትሮ በሚውለው በዚያ ፋውንዴሽን አጠገብ ሲያልፉ የተመለከቱት ነገር ከባድ ምልኪያዊ ገጽታ እንዳለው የደረሱበት መሆኑንም አልሸሸጉም፡፡

ዝርዝሩን በተመለከተ እንዲህ በማለት ገልጸዋል – አቶ ነፃነት፡፡ “ዌል፣ እኔ ኖርማሊ ጧት ጧት ወደ ሥራ የምሄደው በዚህ የመለስ ፋውንዴሽን በሚሉት መንገድ አስታክኬ ነው – ብዙም የምታከክ ደግሞ እንዳይመስልህታዲያ፤ እናንት ጋዜጠኞች አንድን ነገር ኤግዛጀሬት እንደምታደርጉና ነገሮችን እንደምታዛቡ አውቃለሁ፡፡ እርግጥ ነው አክቹዋሊ እዚያ አካባቢ ስደርስ ወደፋውንዴሽኑ ማየትን አልወድም፡፡ ሰውዬው በቁሙ ያስጠላኝና የእናቴ ገዳይ ያህል እቆጥረው ስለነበረ በዚያ የማልፈው ደሜ እየተንተከተከ ነው – ዩዥዋሊ፡፡ ዛሬ ግን ለየት ያለ ነገር ታዘብኩና የመኪናየን ፍጥነት በረድ አድርጌ በመስኮት በኩል ስመለከት ከዐድዋ ድልድይ አቅጣጫ የመጣ የሚመስል አንድ ላንድክሩዘር በመናኸሪያ ሆቴል አቅጣጫ በኩል ከሚገኘው የፋውንዴሽኑ ዋና መግቢያ የበሩ ኮለን ጋር በመጋጨት በሩን ዘግቶ ቆሞ አየሁ – በትዕዛዝ በሩን ለመዝጋት የቆረጠ ይመስላል፡፡ ወደግቢው የሚወስደውን መንገድ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ዘግቶታል፡፡ ከሰው በቀር ወደግቢ መኪና አያስገባም – ለነገሩ ከዚያች ውሻ ሴት በስተቀር ሌላ ሰው ማን ሊገባ እንደሚችል አላውቅም – (ውሻ ማለቴን በዜናህ እንዳታቀርበው ታዲያ ፤ እናንተ እኮ አትታመኑም – አደራህን ኤዲት አድርገህ አውጣው ኦኬ?) ብዙ ሰዎችም ዙሪያውን ቆመው ጉድ ጉድ ይላሉ – “ድ” እንደማይጠብቅ አንባቢዎችህን ንገራቸው – አለበለዚያ ምን ድግስ ኖሮ ነው ‹ጉድ ጉድ› (አሁን ‹ድ› ይጠብቃል) የሚሉት እንዳይሉህ፡፡ እንደምገምተው ብዙዎቹ ሳይደሰቱ አልቀሩም፤ ግን በላይ ያዘኑ መስለው ሊፓቸውን ይመጣሉ – ‹እምጵ› እያሉ፡፡ ግጭቱ ከባድ ቢመስልም የተጎዳ ሰው ግን እንደሌለ አንገቴን በመስኮት አስግጌ የጠየቅሁት አንድ ሰው ነግሮኛል፡፡” በማለት ፋውንዴሽኑ ቢያንስ ያ ላንድክሩዘር እሰኪነሳ ድረስ ተዘግቶ እንደሚቆይ አስረድተዋል፡፡

“በዚህ በፋውንዴሽኑ መዘጋት ምን ተሰማዎት?” ተብለው የተጠየቁት አቶ ነፃነት ሲመልሱ “ኦፍ ኮርስ ምንም አልተሰማኝም ልልህ አልችልም፡፡ ግጭቱ ባይደርስ ደስ ይለኛል፡፡ በተለይ ከመጠነኛ የንብረት ዲስትራክሽን ውጭ የሰው ላይፍ ላይ ምንም ሃፕን ያደረገ ነገር ባለመኖሩ ደስ ብሎኛል፡፡ በት ኦን ዚአዘር ሃንድ ላንድ ክሩዘርን የመሰለ ሚጢጢየ ካር ኦር መኪና ኢፍ ዩ ላይክ ሳይሆን የሆነ ዩ ኖው የፋውንዴሽኑን ግቢ ብቻ የሚያህል ሜቴዎሮይድ ቢወድቅበትና ድራሽ አምላኩ ቢጠፋም የምጠላ ፐርሰን አይደለሁም – ኤግዛክትሊይ ኤ ካይንድ ኦፍ ዛት፡፡ ቱ ዩር ሰርፕራይዝ ይሄ ላንድክሩዘር በሩን እንዲህ ልክክ አድርጎ በግጭት ምክንያት መዝጋቱ ኢት ኢዝ ሪሊ ኦሚነስ – ማለቴ ምልኪያዊ ነው፡፡ ይህ ያልተጠበቀ ክስተት ግቢው በቅርቡ እንደሚዘጋና ለሌላ ፍሬያማ ተግባር እንደሚውል ይጠቁማል፡፡ ሶሪ እቸኩላለሁ፡፡ ሌላ ነገር ባትጠይቀኝ ደስ ይለኛል” በማለት ወደ ሥራቸው ለመሄድ ማቆብቆባቸውን በሰውነት እንቅስቃሴያቸው ቢጠቁሙም የያዛቸው ጋዜጠኛ ቀላል ባለመሆኑ “ጥሩ ነው፣ በንግግርዎ ጣልቃ እንግሊዝኛን የሚጠቀሙት ለምንድነው?” ሲል ጠይቋቸዋል፡፡ መልሳቸውም “ሂድና ኢቲቪን ጠይቅ፣ ሂድና ወያኔን ጠይቅ፣ ሂድና በየስብሰባውና በየዐውደ ጥናቱ በእንግሊዝኛና ዐማርኛ ጉራማይሌ በቅጹ ሳያውቅበት እያወለጋገደ የሚንተባተበውን ምሁርና ካድሬ ጠይቅ፣ ሂድና ስሙን ሲጠየቅ ባላስፈላጊ ሁኔታ ሳይቀር ‹አክቹሊ ስሜ ገረመው ነው› የሚል ዓይነት ጉራማይሌ ሠርክ የሚነገርባቸውን ኤፌሞች ጠይቅ፣ ሂድና የተማርኩ ነኝ የሚለውን ዜጋ በሙሉ ጠይቅ፣ ‹የሠራተኞች መጓጓዣ› ማለት አቅቷቸው አይደለም እንዴ ዐማርኛን በመጸየፍ ‹ፐብሊክ ሰርቪስ› የሚል የዐማርኛ ጽሑፍ ሰማያዊ አውቶቡሶች ላይ ለጥፈው የሚያስቁን? እኔስ ታዲያ ከማን አንሳለሁ? ሁ ማይነስ ሁ አንተ!?” በማለት በንዴት መልሰዋል፡፡ አሁን የቸኮልኩት እኔ ጋዜጠኛው ሆንኩ – እርሳቸው እንደሆኑ ሥራቸውንም ረስተው ከኔ ጋር ሲያወሩ ቢውሉ ደስተኛ ይመስላሉ፡፡

በተዋዛ አቀራረብ ላደረስንላችሁ ጮማ ሰበር ዜና ምሥጋና እንደሚገባን በሾርኒ በመጠቆም በሌላ – ከተገኘ – ሰበር ዜና እስክንገናኝ ደህና ዋሉ በማለት የምሰናበታችሁ –

ከመለስ ፋውንዴሽን ቅጽር ግቢ ውጪ የተጠናቀረውን ዜና ያቀረብኩላችሁ ነፃነት ዘለቀ ነኝ ከአዲስ አበባ

ማሳሰቢያ፡- ይህንን ዜና በምስል ማስደገፍ ያልተቻለው በዚያ አካባቢ ፎቶግራፍ ማንሣት ከጤና አኳያ ጎጂ ሆኖ በመገኘቱ መሆኑን ከይቅርታ ጋር ማሳሰብ እንወዳለን፡፡ ጎመን በጤና፡፡ ለሥራ ያልደረሱ፣ ለምግብ ያላነሱ ልጆችን ቀፍቅፎ ከጅብና ከዓሣማ ጋር አላስፈላጊ ልፊያ ውስጥ መግባት ብልኅነት አይደለም፡፡

The post ሰበር ዜና! የመለስ ፋውንዴሽን ተዘጋ! – ነፃነት ዘለቀ appeared first on Zehabesha Amharic.

ፍትህ ሚኒስቴር ሊፈርስ ነው አሉ….. (አቤ ቶኪቻው)

0
0

abe-tokichaw-satenaw

ፍትህ ሚኒስቴር ሊፈርስ ነው አሉ….. ‘’የባልሽ ቂጣ እንክትክቱ ይውጣ….’’ ብዬዋለሁ። እስከዛሬም ስሙ ከብዶት አለመውደቁ ምን ያህል ይሉኝታ ቢስ መሆኑን የሚያሳይ ነው። ሌላው ፌደራል ፖሊስ በጠቅላይ ሚኒስትሩ እዝ ስር ሊሆን ነው። (ወይ ጠቅላይ ሚኒስትር… !) እርሳቸውም አንድ ቀን ይሄ ስም ከብዷቸው ክልትው እንዳይሉ ስጋት አለኝ… የሆነው ሆኖ ፌደራል ፖሊስ ድሮ በማን ስር ነበር… ብላችሁ የሪፖርተርን ዜና አንድ አረፍተ ነገር ስታነቡ ‘…ቀድሞ በፌደራል እና አርብቶ አደር ጉዳዮች ሚኒስቴር ስር የነበረው የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን…’ ይላችኋል። አርብቶ አደር ነው አባሮ አደር… ?

እስቲ አሁን ፌደራል ፖሊስ እና አርብቶ አደርን ባንድ ላይ ተጠርንፈው ያስተዳድራቸው የነበረው ሰውዬ…. ምን አይነት ሙያ ነበረው ማለት ነው… የግብርና ባለሙያ ነበር ወይስ የወንጀል መከላከል ባለሞያ? አሃ ለካስ ዋናው የኢህአዴግን ፖሊሲ ማስፈጸሙ ላይ ነው እንጂ አማርኛ መምህርን ፊዚክስ እንዲያስተምር መመደብ ይቻላል… (በሳቅ መሞት አለ ደርቤ!)

በጥቅሉ ግን ፍትህ ሚኒስቴር ፈርሶ ድጋሚ ተቦክቶ ቢሰራ፤ ወይም ለሌላ ባለስልጣን ስራው ቢሰጥ እንዲሁ ፌደራል ፖሊስ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢመሩት ወይም ፕሪዘዳንቱ ይምሩት ቢባል፤ አጠቃላይ ኢህአዴግ ፈርሳ ካልተሰራች በቀር ሰውም አትሆንም ለሰውም አትሆንም! (ፈርሳ ትሰራ የሚለውንም እኔ ቡቡ ስለሆንኩ ነው እንጂ እንደነገሯማ ፈርሷ የሰው ልጆች የማይደርሱበት ቦታ መጣል ነው ያለባት….) የምር አማረሩን እኮ!!! እስቲ ማን ቀራቸው ሁሉንም መደዳውን አስለቀሱን እኮ!!! ይዘገያል እንጂ ሁሌ እንዳስለቀሱ መኖር የሚሳካለት አስለቃሽ ጭስ ብቻ ነው!

The post ፍትህ ሚኒስቴር ሊፈርስ ነው አሉ….. (አቤ ቶኪቻው) appeared first on Zehabesha Amharic.

በመቐለ ከተማ የባለ ባጃጆች አድማ 3ተኛ ቀኑን መያዙ ተዘገበ

0
0

mekele

አምዶም ገብረሥላሴ ከመቀሌ
የመቐለ ከተማ ህዝብ ከፍተኛ የትራንስፖርት ችግር ኣጋጥሞታል።

ዛሬ ጥዋት ኤፍ ኤም መቐለ (FM Mekelle ) የሰራው ዜና

* “ባለ ባጃጅ ማህበራት የይቅርታ ደብዳቤ ኣስገቡ” ኣለ ወዲ ሓየሎም የመቐለ መንገድ ትራንስፖርት ሓላፊ።

* “ባጃጅ የድሃ ኣገልጋይ ናቸው ተሎ ወደ ስራ ቢገቡልን” ኣንድ ነብሰጡር ሴት

* “መንግስት ከ ባለ ባጃጅ እልኽ ሊጋባ ኣይገባም ተሎ ወደ ስራ ይመልስልን” ኣንድ ኣባት ኑዋሪ።

የዜናው ርእስ “የመቐለ ኑዋሪዎች በትራንስፖርት መቸገራቸው ገለፁ። ” ይላል።

የሓላፊዎግ መልስ
“ተዋቸው ዕቁብ መክፈያ ሲያጡ በሶስተኛ ቀናቸው ሳይወዱ በግድ ሮጦው ወደ ጉያችን ይመለሳሉ”
ወዲ ሓየሎም የመንገድ ትራንስፖርት ሓላፊ

* “ኣስርቦ መግዛት” የሚል ፖሊሲ ይኸው “ዕቁብ መክፈያ ሲያጡ ይመለሳሉ” እያሉ በድህነቱ እየተሳለቁበት ነው።

ይኸው ህዝቡ በትራንስፖርት ችግር ሰዎች ህሙማን በየመንገዱ እየወደቁ ነው።

በምስሉ የምታይዋት እናት ኣራስ ስትሆን ወደ ህክምና መጓጓዣ ኣጥታ በትግራይ ቲቪ( Tig_TV) በቅጥያ ሱሙ ቶግ ቲቪ መንገድ ዳር ወድቃለች።

መንግስት መመርያው በኣፋጣኝ ኣስወግዶ ባጃጆች ወደ ስራ ሊመልሳቸው ይገባል።

ሓላፊዎቹ በቪ 8 መኪና እየተጓዙ ህዝቡ ባጃጅ ሊነፍጉት ኣይገባም።

‪#‎Bajaj_Protest‬

ነፃነታችን በእጃችን ነው።

it is so.

The post በመቐለ ከተማ የባለ ባጃጆች አድማ 3ተኛ ቀኑን መያዙ ተዘገበ appeared first on Zehabesha Amharic.

“በኢትዮጵያ ሁሉንም ወገኖች ያሳተፈ አገሪቱን ወደፊት የሚያስቀጥል የሽግግር መንግስት መቋቋም አለበት””አቶ ማሙሸት አማረ ሕጋዊው የመኢአድ ፕሬዝዳንት ከአ/አ

0
0
  • ተኩስ የተባለውም ሕዝብ ከተባበረ አልተኩስም የሚልበት ቀን ይመጣል
  • ሁሉንም ያሳተፈ የአገሪቷን የሚታደጋት በአገር ቤት በአስቸኳይ ሽግግር መንግስት መቋቋም አለበት
  • የሀይማኖት ፣የተማሪውም፣የሕዝቡም ሁሉም ትግል ዞሮ ዞሮ ለሕዝብ ነው የሁሉም ትግል ወደ አንድ አቅጣጫ መምጣት አለበት
  • የስርዓቱን አፈና ማስቆም የሚቻለው ሁሉም በጋራ መቆም ሲችል ነው
  • አገሪቱን ከገባችበት አጣብቂኝ ለማውጣት መነጋገር መግባባት ብሔራዊ እርቅ የሚያስፈልግበት ወሳኝ ወቅት ነው
  • ሁሉም ተቃዋሚዎች ባለፈው ጉዳይ መጨቃጨቅ ወደኋላ ሳይሆን አሁን የአገሪቱ ሕልውና አደጋ ላይ በመውደቁ በጋራ መምከር አለባቸው
  • መንግስት ራሱ መቶ በመቶ ተመረጥኩ ያለው ባዶ ሆኖ እንደቀረ አውቋል በጠመንጃ ብቻ የሕዝብን ጥያቄ ማዳፈን አይቻልም

  • “በኢትዮጵያ ሁሉንም ወገኖች ያሳተፈ አገሪቱን ወደፊት የሚያስቀጥል የሽግግር መንግስት መቋቋም አለበት”” አቶ ማሙሸት አማረ ሕጋዊው የመኢአድ ፕሬዝዳንት ከአ/አ

    The post “በኢትዮጵያ ሁሉንም ወገኖች ያሳተፈ አገሪቱን ወደፊት የሚያስቀጥል የሽግግር መንግስት መቋቋም አለበት”” አቶ ማሙሸት አማረ ሕጋዊው የመኢአድ ፕሬዝዳንት ከአ/አ appeared first on Zehabesha Amharic.

    Viewing all 15006 articles
    Browse latest View live