Quantcast
Channel: Ethiopian News | ዘ-ሐበሻ | Latest News Provider | News For All
Viewing all 15006 articles
Browse latest View live

በማንነት ፍለጋዉ ጉዞ –የአፋሩን ቅኔ፤ በእኔ ቅኝት

$
0
0

ከ ኆኅተበርሃን ጌጡ /ጀርመን

አጠገቡ ሆኖ ሲያወሩት ጨዋታዉ ለዛለው። ተፈጥሮዉ ሆኖ የ…….. ጠንጋራ ሳይቀር ለይቶ ያዉቃል። በጨዋታ መካከልም ሁለት አይነት ሳቆች አሉት። የዘወትርና  የክት። ወደ ደም ስር ዘልቆ የሚገባ ቀልድና ቁምነገር ከገጠመዉ  ደግሞ ከልቡ ይፍነቀነቃል። ካልጣመዉም በዘወትሩ የለበጣ ሳቅ ያልፈዋል። የሳቁ ዓይነት ሲነግረንም  በረዥሙ ልንቀድ ያሰብነዉን ጉዳይ ባጭሩ  እንቀጨዋለን። ሳቁ ለእኛ ምልከታ ወይም ርችት ነዉ። ለጨዋታዉ ዉበት የሚሰጠዉ ደግሞ አማርኛ የአፍ መፍቻ ቑንቑዉ አለመሆኑ ነዉ። ለምንም ለማንም ሳይል ደፋር ተናጋሪነቱ ደግሞ የብዙዎቻችንን ቀልብ ለመሳብ አስቸሎታል። በእርግጥ ለዚሀ አይነቱ አቑሙ ሰዎች የተለያየ ትርጉም ይሰጡታል። ግራና ቀኝ ተሽክመነዉ  የምንዞረዉ ጆሮ ባእዳቸን ስለሆነ እሱም እራሱ እስካሁን ጉዳዩን ያልሰማዉ ሊሆን ይችላል። የሚባለዉን እኔም ዛሬ ለመጀመሪያ ጊዜ አደባባይ ማዉጣቴ ነዉ። የእሱ ደፋርነት ከሌሎች የተለየ ወንድ ሆኖ አይደለም። ደሙም እንደ የሁላችንም ደም ቀይ ነዉ። ልዩነቱ ከአፋር ክልል ዉጭ በከተማ የሚኑሩ ዘላኖች ስላሉ የዚያ አይነቱ ዘላኔያዊ ባሕርይ ብልጭ እያለበት ነዉ በማለት፤ ሊሞግቱን ይሞክራሉ። ነገርን ነገር እያነሳዉ ተወራጨሁ ወይም ዙሪያ ጥምጥም እየሄድኩ ለአንባቢ አስቸገርኩ መሰል እንጅ፣ ዓላማዬ የሰዉየዉን ባሕርይ ማተት አይደለም። እኔን በግል የሚያስደስተኝና የምመካበት ምንጊዜም የማይበገር ኢትዮዽያዊነት አቁኣሙ እንጅ ግላዊ ባሕርዩ ስላልሆነ፣ ይህን ይህን ለባለቤቱ ለሓዋ ሙሳ ትቼ ወደ ተነሳሁበት ነጥብ ባመራ ከአንባቢም ጋር የምስማማ ይመስለኛል።

አሰባሳቢ ማንነት ባንድ ሃገር ልጅነት፣ የኢትዮጵያ ዕጣ ፋንታ በሚል ርዕስ የተከተበ መጽሓፍ ሰሞኑን ለንባብ መብቃቱን የተለያዩ ድረ ገጾች አብሥረዉናል። ደራሲዉ በሚኖርበት የኖርዌይ መዲና ኦስሎ የሚገኙ ኢትዮጵያዉያንም በደመቀ ሥነ ሥርዓት ኖቬምበር 22 ቀን 2014 መፅሐፉን በይፋ መርቀዉታል፤ ከመፅሃፉ የዉጭ ሽፋን እስከ ጀርባ ድጉሥ፤ ከአርትኦት ሥራ እስከ ሥርአተ ነቁጥ (ነጥብ)፣ ከጎላ ግምገማም አልፈዉ ቀመረ ሰዋስዉ የተከተለ መሆኑንና አለመሆኑንም ጭምር አበራይተዉታል። ደራሲዉንም በጥያቄ አፋጠዉታል። እታዲያ ከዚህ የመፅሃፍ ግምገማ ነክ ምረቃ ሥነ ሥርዓት በዓል፤ ወደ ጀርመን ይዤዉ የተመለስኩት ትዝታ ቢኖር፤ የኖርዌይን ብርድና ስሙን የማላስታዉሰው የዋሽራዉ ተወላጅ፣ የሉሲዉ (ድንቅነሽ) አገር የአፋሩ  ተወላጅ መፅሃፍ የአማርኛ ቑንቑ አጠቃቀም እንደከበደዉ ጥያቄ ማቅረቡና እንደዚህ ዓይነት ችግር ላለባቸዉ ሌሎችም ተመሳሳዮች፤ በኦስሎ ከተማ በቅርቡ  የአማርኛ መማሪያ ጣቢያ እንደሚከፈት የደራሲዉ ባለቤት ስላቅን ያዘለ፤ ፈጣን መልስ መስጠታቸዉና ቃል መግባታቸዉ ተስብሳቢዉን በእጁጉ ማስደመሙ ነዉ። በእርግጥ መፅሃፉና የደራሲዉ የተጸዉኦ ሥም አደባባይ ወጣ እንጅ፤ ሰዉየዉ ለብዙ ኢትዮጵያዉያን አዲስ አይደለም። በአንድ ወቅት የኢትዮጵያ ሕዝብ ልሳን፣ አይንና ጆሮ ሆና ስትታገል የነበረችዋ ጦቢያ መፅሄት ቑሚ አምደኛ በመሆን መጽሃቷን በእግሯ ካቆሙዋትና ተነባቢ እንድትሆን ካበቁአት ጸሐፍት መካከል (እንደነ ጸጋዪ ገብረመድሕን አርአያ፣ ስንሻው ተገኝ…….ወዘተ) በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱት አንደኛዉ ነዉ። ሐሰን ኡመር አብደላ በሚለዉ ተናዳፊ የብዕር ሥሙ። ለአራት አመት ያህል ነጻዉን ፕሬስ ተቀላቅላ በአቅም እጥረት ምክንያት የከሰመችዉ የራዕይ መፅሄትም (ፍራንክፈርት ጀርመን ትታም የነበረችዉ) መሥራች የቦርድ አባልና አምደኛም ነበረ። ካረሳሁት በወቅቱ የመፅሄቷ የሥራ መርሆ ምን መሆን እንዳለበት የተለያዩ ሃሳቦች ቀርበዉ ስንነጋገር፣ <ለሁሉም መድረክ ነን፣ የማንም ልሳን ግን አይደለንም>፣ የሚል እንዲሆን፤ ሁሉንም የቦርድ አባላት በአንድ ድምፅ ያሳመነ ሀሳብ አፍላቂዉ እሱ ነበረ። ይህ ብቻም አይደለም፤ ተዘዉትሮ በጀርመን ድምፅ ራዲዮ የምሥራቅ አፍሪካና የመካከለኛው ምሥራቅ ተንታኝነቱም የሬዲዮ ጣቢያዉ አድማጮች ጆሯቸዉን ቀስረው የሚያዳምጡት ነዉ። ዛሬም የቀድሞ የጦቢያ ደንበኞች በተለያዩ አጋጣሚዎች በአካል ስንገናኝ ያ፣ አፋሩ የጦቢያ መጽሄት የነፍስ አባት ደኅና  ነዉ? ሳንባባል  አናልፍም። ይኽዉ አሁን ደግሞ በእዉነተኛ ሥሙ ሁላችን ስንጠብቀዉ የነበረዉን እምቅ ችሎታዉን ያሳየበትን፣ የወደፊቷን ኢትዮጵያን ዕጣ ፋንታ እንደ መስታወት ወለል አድርጎ  የሚያሳየዉን  መጽሃፍ ይዞ ብቅ ብሏል።

ኮብላዩ ሚኒስትር ኤርምያስ ለገሰ ስለባለቤት አልባዋ ከተማ አዲስ አበባ በወዶ ገብ የኢሕአዴግ ካድሬነቱ ለአሥራ ሁለት አመታት ያለፈበትን ጉዞ፣ ሥርአቱ ምን ያህል የተግማማ እንደሆነና ከቀዳማዊት እመቤት ጀምሮ እስከ አዉራ ካድሬዎቹ በከተማ ቦታ ዝርፊያና በሙስና የነቀዙ መሆናችዉን የጆሮ ሳይሆን የአይን ምሥክርነቱን ሰጥቶበታል። <አሰባሳቢ ማንነት ባንድ ሃገር ልጅነት> የተሰኘዉ ይህ መጽሃፍ ደግሞ ስለባለቤት አልባዋ፣ የእነሱ? ወይንስ የእኛ የሁላችን የዜጎቿ? መሆኗ ገና በዉል ስላልታወቀችዉ ኢትዮጵያ ስለምትባለዋ ሀገራችን ነዉ። እስኪ እራሳችሁን ጠይቁ፣ በአሁኑ ጊዜ ማነዉ የኢትዮጵያ ባለቤትዋ? እነሱና እኛ ተባብለን ሳንቧደን እኛ ኢትዮጵያዉያን የምንላት የሁላችን የሆነች፤ እኛም ዜጎቿ የእሷ የሆንላት፤ የጋራ ሀገር እንዴት መፍጠር እንደሚቻል በአመክንዮ አስረግጦ፣ የአብሮነት ቀመርን አስፈላጊነት ከነመፍትሄዉ ቁልጭ አድርጎ አስቀምጧል። ከማንነቶች መራኮት ይልቅ ወደ ኢትዮጵያዊነት አሰባሳቢ ማንነት፤ ፍለጋ የመኹተን አስፈላጊነትን በአጽንኦት ለማሳዬት ደክሞበታል። አዎ፤ ሁላችን የምንነጋገረዉ፤ ኢትዮጵያ ስለምትባለው ሃገር ከሆነ፣ ኢትዮጵያዊነት ግን ግለሰቡ በምርጫዉና በገዛ ፈቃዱ የሚላበሰዉ ወገንተኝነት በመሆኑ፣ ይህን አሰባሳቢነት ኢትዮጵያዊነት በእያንዳንዱ ተወለድሽኝ ዜጋ ሥነ አዕምሮ እንዴት ማስረጽ እንደሚቻል፣ አትቷል። የመጽሃፉ ምሥጢርና ሰምና ወርቅም በዚህ ዙሪያ የሚያጠነጥን ሆኖ እናገኝዋለን። የመጽሃፉ መዘዉረ ሃሳብ በዚህ ዙሪያ ያቀንቅን እንጅ፣ ደራሲዉ ወደዚህ የማሳረጊያ ነጥቡ ለመድረስ ብዙ የማንነት ፍለጋ ጉዞ እንዳደረገ፣ ያገላበጣቸዉ ዋቢ መረጃዎቹ ያስረዳሉ። ዋቢዎቹም ሀገርኛና የዉጭ ቑንቑዎችን አካተዋል። ከመጽሃፉ ይዘት ጋር ቁርኝት ያላቸዉ የኅብረተሰቡን ገሃድ አለም አቀንቃኞች የሚገልጹባቸዉ የዘፈን ስንኞችም ልብ መሳጭነት ባለዉ መንገድ ሰፍረዋል። የመጽሃፉ ዘይቤያዊ አገላለጽና የአጻጻፍ ሥልት ሲፈተሽ፤ በመንዝኛም፤ በጎንደርኛም፤ በሸበል በረንታም ቅላጼ ባለዉ አማርኛ ሳይሆን፤ እራሱን ዩሱፍ ዩሱፍን በሚሸት የራሱ ዩሱፋዊ ዘይቤና ቃና ባለዉ መንገድ ተክሸኖ የቀረበ ነዉ። የመልዕክቱን ይዘት ለተረዳዉ ደግሞ አፋሩ ለኢትዮጵያዉያን የተቀኘዉ ይበል የሚሰኝ ቅኔ የተቀኘበት መጽሃፍ ነዉ። ብዙአዪሁ የሚባል ዘፋኝ ቅርብ ጊዜ ባወጣዉ አልበሙ፣ አንዷን ኮረዳ ይህ ቀረሽ በማይባል ዉበት መላበሷን ሲግልፅ፣ ፈጣሪ ተራቆብሻል፤ ጥበቡን ማሳያ አርጎሻል። እንዳለዉ፣ የኢትዮጵያዉያንን የአብሮነት የመኖር ጥበብን አስፈላጊነት ጆሮ ያለዉ ከሰማ፣ልብ ያለዉ ካስተዋለ ለአሰባሳቢ ማንነታችን እንደ ፍቱን መሳሪያነት ልንጠቀምበት የሚገባ ሰነዳችን ነዉ።

ከማንነቶች መራኮት ይልቅ ወደ አሰባሳቢ ማንነት ፍለጋ ጉዟችንን እንድናሳምር፣ ጸሐፊዉ የማሳረጊያ ቡራኬ ከመስጠቱ በፊት፤ ለመጽሃፉ አላማ ግብ መምቻ የሚዉሉና በቀጥታ ለመፅሃፉ መደረስም አዉራ አመክንዮነት ያላቸዉን መድበለ ሃሳቦች በአሥራ ሦስት ሞእራፎች (መሪ ርዕሶች) እና በሰማንያ አራት ንኡሳን ክፍሎች (መዘርዝረ ሐተታ) በመፈረጅ፤ ለእያንዳንዱ ተጟዳኝ ርዕስ ጥልቅ ትንተና ሰጥቶባቸዋል። ስለማንነት፤ ማንነትን ስለመለዬት ሂደት፤ በምን፣ በምን፣ እንደምንኮራ፤ ከምን፣ ከምንስ፣ እንደምንሰጋ፤ያለን የመንግሥትነት ታሪክ? ወይንስ ረዥም የሥልጣኔ ታሪክ? በማለት ከራሱና ካለፈ ታሪካችን ጋር ይሟገትና ከዚሁ ርዕስ ጋር ተቆራኝቶ፤ ያለን የረዥም ጊዜ የሥልጣኔ ታሪክ ነዉ ወደሚል መደምደሚያ የምናመራም ከሆነ፤ ሌሎቹ ለምን ጥለዉን ሄዱ? ለምን እኛ ጭራ ሆነን ቀረን? ብለን እራሳችንን በቁጭት እንድንጠይቅ ያደርግና፤ በቁስላችን ላይ እንጨት ሰድዶ ሆዳችንን ያባብሰዋል። የመንግሥት ጣልቃ ገብነትንና የሃይማኖት ተቑማትን ነጻነት ስለመለዬት አስፍላጊነት፤ በታሪካችን ስለተከናወነዉ የግዛተ አፄን የማስፋፋትና የማዕከላዊ መንግሥትን መደላደል ዘመቻ፤ ይህ የጥንት ዘመቻም በአሁኑ አብሮነታችን ላይ ያሳረፈዉ አሉታዊና አወንታዊ ገጽታዉ ምን እንደሆነ፤ ይህን ርዕስም ያጎዳኝና፤ የኦሮሞ ብሔረተኛነት፣ የማንነት ፖለቲካና ተፈታታኝ ተግዳሮቶቹን አስመልክቶ ድንቅ ትንተና አድርጎባቸዋል። እንኝህንና መሰል ተዛማጅ ርዕሰ ጉዳዮችን በየምዕራፉ ካብጠለጠላቸዉ በኁላ ነዉ፤ አብዛሔነትን አስተዳድሮ ለዜግነታዊ መንግሥት መሠረት መጣል፤  ወደሚለዉ አዉደ ሐሳብ የተሸጋገረዉ። ከፊታችን ተደቅኖ ከሚታዬዉ ከዉስብስቡ ግዙፍ ሀገራዊ የፖለቲካ ችግር አንፃር፤ ይህ ነዉ፣ እያንዳንዳችንንም ኢትዮጵያዉያን ዜጎች የሚመለከተዉና ወቅታዊዉም የመፅሃፉ ምሥጢርና የአፋሩ ቅኔ።

እስኪ መጽሐፉ ካዘላቸዉ  ቁምነገሮች ጥቂቱን ቀንጨብ አድርጌ ላቃምሳችሁ። “<….ሁላችን የተሳፈርንባትን፣ እየተወዛወዘች ለመስመጥ የቀረበችዉን ጀልባ ላይ፣ እሳት ማቀጣጠሉንም ሆነ ሽንቁር መሸንቆሩን አቁመን፣ ሃገራችን ባሁኗ ሰአት የምትገኝበትን አሳሳቢ ሁኔታ ተገንዝበን፣ ወደ ልበ ልቦናችን ተመልሰን በሃገራዊ የሃላፊነት ስሜት እያንዳንዱ ድርሻዉን ለመሸከም ዝግጁነቱን ማረጋጥ ይኖርበታል። …..የተቁኣማት፣ የሕግ ልዕልና ሲቪል፤ ዜግነታዊዉ መንግሥት ምሥረታም ሆነ ማደላደል ረዥም  ጉዞ ቢሆንም ቅሉ የሀገሬ ልጆች፣ የተለያዩ የብሔረስብና የእምነት አባላት፣ የተለያዩ የመደብና የሙያ ማሕበራት፣ ሴቶችና ወንዶች እጅ ለእጅ ተያይዘዉ የዜግነታዊ መንግሥት ዳገቷ ላይ ሲደርሱ ይታዩኛል። አጣልቶ የሚያፋቅር ትዳር ይስጣችሁ ተብሎ ሲመረቅ ሰምተናል፣ ያጣላንም ይበልጥ እንድንፋቀር ከሆነም አጣልቶናልና ያፋቅረን!! አንዱ በሌላኛዉ ወንድሙ ባደረሰዉ በደል ምክንያት የቑጠረዉን የቅሬታ ስሜትና የታሪክ ቁርሾ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሽሮ፣ የሚያፋቃር በተደላደሉ መሠረቶች የቆመ ብሔራዊ አንድነትም ይስጠን! የሁሉንም የሕብረተሰባችን ተካይ ነቃይ ብዛሔሰብዕ ባንድነት በሚያቅፍ አቃፊ ደጋፊዉና አጣሪው አሰባሳቢና ሃገራዊ ማንነት በሆነዉ፣ ዜግነታዊ መንግሥትና ተቑማቱ ሥር ሁላችን ያስጠልለን!! ያሰባስበን!! በዚችዉ ሃገር፣ ባንድ ሃገር ልጅነት በእኩልነት ያኑረን! ያኗኑረን!! አ..ሜ..ን! ይለናል በሐገራዊ ቡራኬዉ።

ግን በተደላደሉ መሠረቶች ላይ የቆመ ብሔራዊ አንድነት እንዴት እንፍጠር? እንዴትስ ነዉ መምጣት የሚችለዉ? ነዉ ጥያቄዉ። ምን ዓይነት አንድነት ነዉ የነበረን? አብሮ ያኖረንን አንድነት አሁን ለምን ጠላነዉ? ችለናቸዉ እንጅ አብረን የኖርነዉ ተቻችለን ስላልነበር፣ እስኪ እንሞክረዉ ደግሞ ተለያይተን የሚል እንጉርጉሮዉን እያሰማ፣ ነፍጥ አንስቶ ዱር ቤቴ ያለ ክፍል አለ። ለዘመናት በደረሰብኝ በደል ከበሽታዬም ገና ስላልተፈወስኩ፣ አንድም ከእግሬ ጫማ ሥር ወድቀዉ፣ እንደገናም ላይለምዳቸዉ ቃል ገብተዉ፣ ይቅርታ ይጠይቁኝ፣ ይህ ካልሆነ፣ ከእነርሱ ጋር አብሮ የመኖሩ ጉዳይ አይታሰቤ ነዉ በማለት የበቀል ፖለቲካ ሲያካሂድ እየተስተዋለ ነዉ። እዚህ ላይ መረሳት የሌለበት ነጥብ ግን ከፊደሉ ጋር መርዙን አብሮ የተጎነጨዉ የኤሊቱ ጥያቄ ነዉ የብሔርትኝነት ጥያቄዉን ያጎላዉ? ወይንስ የአብዛኛዉ የአሮሞ ሕዝብ ጥያቄ ሆኖ አብሮነትን ተፈታትኗል? በዚህ ረገድ የተደረገ ጥናትስ አለ ወይ? በእርግጥም የሕዝብ ጥያቄ ሆኖ እስከቀረበ ድረስ ግን ያንድ ሀገር ዜጎች መሆናችንን የሚያበሥር፤ የዜግነት ሕገ መንግሥታዊ መብትን በተግባር ያጎናፀፈ መልስ ማግኘት የግድ ይኖርበታል። የጥያቄዉ ግንባር ቀደም አስተጋቢዎችም፤ ጣራ የነካ የቂም በቀል ፖለቲካቸዉን ወደ ጎን በመተዉ፣ በኢትዮጵያ ሥም ይቅር ለእግኣብሔር የምንባባልበትን መንገድ ቢቀይሱ በዕዉንም የፖለቲካ ጠበብት መሆናቸዉን አስመሰከሩ ማለት ነዉ። ያ ሳይሆን ቀርቶ ግን የመጠፋፋትን መንገድ ከመረጥን ተጎጅዎቹ ሁላችንም ነን። ያለፈ ቂምና በደልን ከአዕምሯችን ፍቀን ስለነገዉ ብቻ እንሰብ!!  የፅድቅ መንገዱም ይህ ነዉና። ይህን ማድረግ ካልቻልን ግን አቀንቃኙ፤ ቂማችን ተራራ፣ መንገዳችን ግራ፤ አልተገናኘንም ከፈጣሪ ጋራ። እንዳለዉ፣ እንዴት ነዉ ከፈጣሪም፣ ከኢትዮጵያም ጋር የምንገናኘዉና አብረንስ የምንኖረው ነዉ ጥያቄዉ?

በሌላዉ ጫፍ ደግሞ የተፈፀመ የታሪክ ስህተት ኖረም አልኖረም፣ በተለባበሰ የአረም እርሻ ላይ ቆሞ፤ የጭፍን አንድነት መዝሙር እያስተጋባ፤ ዛሬም እንደ ትናንቱ የአንድነት ወይም ሞት ቀረርቶና ፉከራዉን የሚያድለቀልቅ ፅንፈኛ አቑም አራማጅ አለ። ጭራሽ ጥያቄዉን መስማትና እንዲነሳም የማይፈልግ። የእምቧይ ካብ አንድነት ሳይሆን ምንም ዓይነት ፖለቲካዊ ማዕበል የማያናዉፀዉ፤ በኢትዮጵያዊነት ማገርና ምሰሶ ተለብዶ የቆመ፤ ብሔራዊ አንድነት የግድ ያስፈልገናል።  ይህም ሲባል፤ ምንም ይሁን ምን ያለፈ ታሪካችን ኅፀፅ አልነበረበትም ብለን አንሟገትም። ለመቀበል ገታራ አቁኣም ተያዘ እንጅ፣ አንገታችንን ቀና አድርገን እንድንሄድ የሚያደርገን አኩሪ ታሪካችንንም፤ አንገት የሚያስደፋ የወል የሰቆቃ ግፋችንንም በጋራ ተቀብለነዉ ወደ አዲስ የመኖር ምዕራፍ እንሸጋገር ነዉ የምንለዉ። በእንደነዚህ ዓይነት መሠረተ ሀሳቦች መስማማት የማንችል ከሆነ፣ ምን ዓይነት አንድነት ብንመሠርት እነኝህን ጫፍና ጫፍ የተለጠጡ ገታራ ፅንፎች ወደ ኢትዮጵያዊነት አሰባሳቢ ማንነት ማዕቀፍ ሥር ማጠቃለል የምንችለዉ? ስለቂም በቀል ጉዳይ ካነሳሁ በቅርቡ የሰማሁትንና ለማመን የሚያስቸግረዉን ተምሳሌት ከቶዉኑ ለአንባቢ ሳልጠቅስ ማለፍ ግድ ይለኛል። ተወዛዋዡ ወጣት አብዮት (ካሣነሽ) ደመቀ በእሳት ቴሌቪዥን ጣቢያ በታማኝ በየነ የጥበብ ቃና ሾዉ ቀርቦ ባደረገዉ ጭዉዉት፤ በ 1993 ዓ.ም አዲስ አበባ ከተማ ሲረበሽ ብቸኛ ልጃቸዉን ፍለጋ ከቤት ወጥተዉ፣ ከፖሊሶች በተተኮሰ ጥይት እየተዝለፈለፉ በደቂቃ ዉስጥ ልጃቸዉንም ያገኙትና ለራሳቸዉ ሳይሆን ለእሱ የኖሩት እናቱ ካሣነሽ፣ በእጁ እንደደገፋቸዉ እጁ ላይ እንዳሉ ሕይወታቸዉ ታልፋለች። ከቤታቸዉ ላይመለሱ ለአንዴና ለመጨረሻ እንደወጡ ቀሩ። በመላ ሕይወቱ የማይረሳዉ ገጠመኙ ቢሆንም፤ ገዳዮቹን ለመበቀል ግን እንደማያስብ፣ የሚከተለዉ ሃይማኖቱም የቂም በቀል መንገድ በር መክፈትን እንደማይፈቅድለት ሲገልፅ፤ በቴሌቪዥኑ መስኮት  የማዬዉን ሰዉ ማመን፤ የገዛ ጆሮዬንም መጠራጠር ጀመርኩ። እስኪ ማን ይሙት በዓፄ ምኒልክ ሠራዊት በተተኮሰ ጥይት በቅድመ ዘር ቆጠራ ደርሶበት የቅድም፣ የቅድም አያቱ እጁ ላይ ሕይወቱ ያለፉበት ዜጋ በመካከላችን ካለ፣ የዚህን ወጣት ታሪክ ሲሰማ የቂም በቀልን ሥርዓተ ቀብር ፈፅሞ ከራሱም፣ ከሌላዉም ጋር ታርቆ፤ አዲስ የመኖር ምዕራፍ አይጀምር ይሆን ትላላችሁ? እስኪ ልቦና ይስጠን!!

ሦስተኛዉና በጣም አደገኛዉ የትርምስ አካሄድ ደግሞ፣ ተጠቃሾቹን ሁለት ፅንፈኛ አቁም አራማጆችን የማን አባቱ ገደል ገባ እያለና በችግራቸዉ ክብሪት እየጫረ፣ ችግሩንም የፈታ እያስመስለና በችግሩም እያፌዘ፣ ዓላማዉም እራሱን ከሥልጣን ላይ አደላድሎ ማቆዬት ብቻ ይሆናል። ምክንያቱ ደግሞ በተደላደሉ መሠረቶች ላይ የቆመ ብሔራዊ አንድነት መመሥረት ከመጀመሪያዉም አጀንዳዉ አይደለምና። ወጋ ወጉ ተይዟል፣ ችግር አንቆ ይዟል እንደሚባለዉ ዓይነት ሆነ እንጅ፤ ባለጊዜዉ ቡድን በችግሩ መፍቻ የማኀበራዊ ሳይንስ መድኃኒትነት ተጠቅሞ ሳይሆን፣ ለራሱ በሚያመቸዉ መንገድ ብቻ የብሔረሰቦችን ችግር ፈትቻለሁ ባይ ነዉ። የነበረንን የአሐዳዊ የመንግሥትነት አወቃቀር አፍርሶ በሐዉርታዊ (ብሔር-በሐዉርት) ፌዴራል መንግሥት መሥርቼ፣ ሁሉም እራሱን በራሱ እንዲያስተዳድር አድርጌያለሁ ይለናል። ይህ ብቻም አይደለም። ብሔረሰቦቻችን ልዩነታችን ዉበታችን እያሉ እየዘመሩ፣ በየዓመቱም የብሔረሰቦችና የሰንደቅ ዓላማ ቀን እያከበሩ እንዲፈነጥዙ በማድረግ አግኝተዉት የማያዉቁትን ድል እንዲጎናፀፉ በማብቃት ተወዳዳሪ የማይገኝልኝ ለብሔረስቦች እኩልነት የቆምኩ ብቸኛ መንግሥት እኔ ነኝ ባይ ነዉ፤ የእኔ መስታወት በሆነዉ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን መስኮት ስመለከታቸዉና የግል ጥሩንባዬ በሆነዉ የኢትዮጵያ ሬዲዮ ጣቢያ ወደ ላይ፣ ወደ ላይ እየዘለዘሉ ልዩ ልዩ ኅብረ ቀለማት ባላቸዉ አልባሳት አሸብርቀዉና ደምቀዉ ስመለከታቸዉ፣ የቆምኩለት ዓላማ ምን ያህል ግቡን እንደመታ እርካታን ይሰጠኛል ባይ ነዉ፤ የሕዝብ ብሶት ወለደኝ የሚለዉ ጀግናዉ  ኢሕዲአግ። የአሃዳዊ መንግሥት  አለመኖር በመርኀ ደረጃ አያጣላንም። ፌዴራሉ የፌዝና የቧልት ፌዴራል መሆኑ ነዉ፣ የማያስማማን።

ከቀድሞዉ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ጀምሮ አሁንም ገና ዕልባት ያላገኘዉና አብሮ የመኖርና ያለመኖር ተግዳሮታችንም ይኽዉ የብሔር-ብሔረሰብ ፈታኝ ጥያቄ መሆኑ ለሁሉም ገሃድ ዕዉነት ነዉ። በደራሲዉ መፅሃፍ እንደተገጸዉ፣ አንድ አናሳ ቡድን በራሱ ስብስብ ሥም  የተቆጣጠረዉን ሥልጣንና የሃብት ምንጭ እንዳያጣ፤ ነባሩን ችግር ይበልጥ እንዲወሳሰብ አደረገዉ እንጅ፣ መፍትሄ አልሻተለትም። መፍትሄዉን አጥቶት አይደለም። ለችግሩ በትክክል መፍትሄ ከተገኘለት አናሳዉ ቡድን ቦታ የለዉም። ሥልጣን ከሌለ ደግሞ፣ በሃያ አራት ሰዓት የናጠጠ ሐብታም የሚያደርግ የሀገር ዘረፋ ሎተሪ የለም። ተመልሶ ወደ ጫካ የማይታሰብ ነዉ። የቃታ እጆች ለስልሰዋል። ጫንቃዎች አብጠዋል። ቦርጮች ወጥተዋል። በከተማዎች ብዙዉን ጊዘ የስኩኣር መጥፋት የሚያጋጥመዉ ገበሬዉ ስኩኣር መቃም ስለለመደ ነዉ፣ እየተባለ እንደሚፌዝበት፣ ተጋዳላዮቹ ዛሬ የቢራ ደንበኞች መሆናቸዉን ግን መካድ አስቸጋሪ ነዉ። ባጭሩ ብዙ ዳገት ሳንወጣና ሳንወርድ ፍላጎቶች ከመበርከት አልፈዉ  ቅጥ አጥተዋል ነዉ። ሥሜቶች ገደብ አልፈዋል። ኀሊና ተጋርዷል። ለሕዝቦች የተገባዉ የጫካዉ ቃል ኪዳን አዲስ አበባ ሲገቡ ፈርሷል። ለዲሞክራሲ ማበብ የተዘመረዉ መዝሙር የቁራ ጩኸት ሆኖ ቀርቷል። በብሶት አዋለደን ለሚሉት ሕዝብ መኖር ተረስቶ ለእራስና ለቤተስብ መኖር ተመርጧል።

ስለዚህ መፍትሔዉ፣ ሥልጣን ከእጅ እንዳያፈተልክ፣ ሕዝቡ አንድ ሆኖ ጣቶቹን ወደ እኛ እንዳይቀስር፣ እርስ በርሱ ማናከስ፤ ሀገራዊ ፋይዳ ያላቸዉ ዕሴቶችን ድኩማን በማድረግ፣ ብሔራዊ ሥሜቱን ማኮሰስ፣ ከመንደርና ከቀዬዉ አርቆ እንዳያስብ ማድረግ፣ አስተሳስብ አድማሱን በዘር ልጟም መሸበብ፣ እርስ በርሱ ሲባላም፣ እኛ የማታለል ሥራችንን ተቀባይነት ያለዉ በሚያስመስል መንገድ ማካሄድ፡ ለዚህ ደግሞ እኛን ገና ሳያስነጥሰን ይማራችሁ የሚሉ ካድሬዎችን በሲቪል ሰርቪስ ኮሌጂያችን የአብዮታዊ ዲሞክራሲን ድጟ እንዲያስመሰክሩ  በማድረግ ለሥርዓቱ ዘብ በመቆም ሥልጣን ከእጅ አፈትልኮ እንዳይወጣ የሞት የሸረት ትግል ማካሄድ ለአንዳፍታም ቸል የማይባል ዓላማችን መሆን ይኖርበታል ይላሉ ኢሕዲጋዉያን። አካፋዉን አካፋ፤ ዶማዉን ዶማ ብለን ከተነጋገርን ግን እነሱ በሃገር ሃብት የኑሮን ጣዕም እያጣጣሙ ሲኖሩ፣ ድምፅ አልባዉና እነሱን አኗኗሪው ሕዝብ ግን (ከተሜዉም ገጠሬዉም) በድምፆቹ፣ በልሳኖቹ፣ ጆሮዎቹ በሆኑት የኪነጥበብ ሰዎች እንዴት ነዉ ብሶቱን የሚያሰማው ብለን እስኪ እራሳችንን እንጠይቅ? አለ ነገር፣ አለ ነገር፣ ዘንዶሮ አለ ነገር፤ አለ ነገር፣ ከርሞም አለ ነገር፤ መቼም ታመን፣ ታመን አንገት ደፍተን አንቀር። ይላል፤ ይህ የገጠሬዉ እንጉርጉሮም ሆነ፣ የከተሜዉ እሮሮ ዉስጠ ወይራም፤ ሠም ለበስ ቅኔም አይደለም። ምን ያህል ሕይወት እንደመረረዉና ወቅት ጠብቆ የሚፈነዳ ቦምብም በጉያዉ አቅፎ እንደሚኖር ጠቑሚ የሆነ ፅድቅ ቅኔ እንጅ።

ይቺ ቂም የቑጠረች አባባል ጊዜዋ ሲደርስ እንደ የካቲት 66ቱ፣ እንደ ግንቦቱ 83ቱ፣ ሌላ ብሶት የሚወልደዉ፣ ገና ሥሙ የማይታወቅ ሊመጣ ይችልና ተሰዳጁ አሰዳጅ፣ አሳሪዉ ታሳሪ፣ ፈራጁ ተፈራጅ፣ አዛዥ ናዛዡ ባላሥልጣን ከሰዉነት ወርዶ ምስኪን ዜጋ ሆኖ ሲንገዋለል የሚታይበትን ቀን ከማቃረብ፤ አስቀድሞ ቢታወቅበት ግን ሀገርንም እራስንም ማዳን አይቻልም ትላላችሁ? ያለጥርጥር ይቻላል ነዉ መልሱ። ግን ከፀሐዩ ንጉሣችንም፣ ከአብዮታዊዉ መሪያችንም ትምሕርት ማግኘት አልተፈለገም። የመፅሃፉን ርዕስና ደራሲ ለጊዜዉ በዘነጋሁት ግን ደግሞ ካነበብኩት የማስታዉሰዉ፤ ፕሬዚደንት ኮሎኔል መንግሥቱ ባንድ ወቅት የጦር አበጋዞቻቸዉን ይሰበስቡና ስለስሜኑ የሀገራችን ሁኔታ ዉይይት ያደርጋሉ። ከጦር አዝማቾቻዉ መካከል አንደኛዉ (ጄኔራል ታሪኩ ያይኔ ይመስሉኛል) ይነሱና ጟድ ፕሬዚዴንት፤ ችግራችን ሻቢያ ወይንም ጀብሃ አይደለም፣ የትግራዩ ነፃ አዉጪ ከተመታ እነኛን ይተዋቸዉ ብቻቸዉን የትም አይደርሱም፣ ዋናዎቹ ፍልፈሎች እነኘህ ናቸዉ ይሉና ሃሳባቸዉን ያቀርባሉ። ዘወር በል አንተ የምታዉቀዉ ጉዳይ የለህም ይባሉና ቀልባቸዉ ይገፈፋል። ብዙም ሳይቆይ ሁላችን በዓይናችን በብሌኑ ያየነዉን ዕዉነት በመናገራቸዉ ብቻ፤ ቀልባቸዉ ብቻም ሳይሆን፣ ዘግይቶም ማዕረጋቸዉም ጭምር ይገፈፍና የአብዮቱ ሠይፍ አርፎባቸዉ ይችን ዓለም ተሰናብተዋል።  እዉነት እንነጋገር ከተባለ፣ መቀሌን እስከተቆጣጠሩ ድረስ መንግሥት የእነሱን ሥም አንስቶና ዕዉቅና ስጥቶ ለመነጋገርና ብሔራዊ ዕርቅም ለማዉረድ ፍላጎቱም አልነበረም። ከዚህ ነጥብ ጋር የሚሄድ፣ እስኪ አንድ ስንኝ ከመዝሙረ ዳዊት ላቃምሳችሁ። ዕብን ዘመነንዋ ነደቅት ወይዕቲ ኮነት ዉስተ ርዕሰ ማእዘንት (የተናቀች ድንጋይ እርሷ የማዕዘን ጭንቅላት-ራስ ትሆናለች እንደ ማለት) ሆነና የተናቀችዋ የደደቢት ፅንስ ለዚህ በቅታ፤ የደርግን መንግሥት በዚህ መንገድ ተሰናብተን አሁን እምንገኝበት ደረጃ ደርሰናል። አሁን ጥያቄዉ በደርግ መቃብር ላይ ሥልጣኑ ያበበዉ ኢሕአዲግ ለሕዝብ የገባዉን ቃል ፈፅሟል ወይ? የሚፈለገዉ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትስ በሀገራችን ሰፍኗል ወይ? ያለጠብ መንጃ አስገዳጅነት በሕዝብ ይሁንታ የተመረጠ መንግሥትስ አለን ወይ? እነዚህ ሁሉ የሚገዙብት፤ በሕዝብ ይሁንታ የረቀቀና የፀደቀ ሕገ መንግሥት አለን ወይ? በእነዚህ መሠረታዊ ጥያቄዎች አለመመለስ ልቡ ለሸፈተ ሕዝብና ፋኖ ተሠማራ ላለ ቡድን፣ የማስተናገጃ መልሱ አሁንም እንደ ትናንቱ እኛ በመጣንበት ኑና ሞክሩን ነዉ ሽለላው? ወይንስ……..? እስከ መቼስ ነዉ ወንድም ወንድሙን እየገደለ ጀግና የምንባባልበትን አሳፋሪ ብቻም ሳይሆን አንገት አስደፊ የሆነዉን፣ የታሪክ ምዕራፍ ለአንዴዬና ለመጨረሻ ጊዜ የምንዘጋዉ?

ለመሆኑ የአሰባሳቢ ማንነት፣ ባንድ ሀገር ልጅነት-የኢትዮጵያ ፋንታ ደራሲ ምን የሚለን አለ? ልዩነታችን ዉበታችን ነዉ ለማለት የምንደፍረዉ ወይም የደራሲዉን አገላለፅ ልዋስና …ከአብዛኄነታችን ጋር መኗኗር ችለናል ማለት የምንደፍረዉ፤ ስለመንግሥት አስተዳደር፤ የሥርዓቱ ባሕርይና ምንነት ዙሪያና ሳቢያ የተለያዩ ዕይታ አመለካከቶች መኖራቸዉንና ጉራማይሌነታቸዉን በተግባር ተቀብለን ማስተናገድ መቻላቸዉን ማረጋገጥ ስንችል ብቻ ነዉ። ለሁሉም በሚከናወኑ ተግባራት ዙሪያ ቀዳሚዉ ብሔራዊ መግባባት ነዉ። ከሁሉም በፊት አንዱ ከሌላዉ ጋር የሚኖረዉ መስተጋብር፣ ግንኙነት፤ ተዛምዶ ነዉና ወሳኙ መቀሰም ያለበት ትምህርት ቢኖር፣ የዚህን ዓላማ ተግባር አስፈላጊነትንና ቀዳሚነትን መገንዘቡ ላይ ነዉ ቅድሚያ የምንሰጠዉም።…. ከብሔረተኛ መፈክርነት ባሻገርና በመለስ፣ ኢትዮጵያዊነት እንደ አንድ ሐገራዊ የኢድዮሎጂ ትክክለኛዉ ይዘቱ መፈታት አለበት ነዉ በሌላ መልኩ። ማለትም ከሌሎች ከእሱ ጋር ከሚፎካከሩ ኢድዮሎጂዎች አሸንፎ ወይንም የእሱን ተፃራሪዎች በአመክንዮ አምክኖ፣ አሰባሳቢ የበላይነቱን ማረጋገጥ ካልቻለ፣ ኢትዮጵያዊነት እንደ ኢድዮሎጂ የትሕተ ሀገራዊ ማንንትን ካባ ከደረቡ ቅርንጫፍ ማንነትቾች ጋር ግብግቡን ሳያሸንፍ ይቀርና ይሽመደምዳል። ይህ ግን አይታሰቤ ነዉ።…. በሀገሪቷ የዲሞክራሲ ልደት ወይም የመበታተን ዋዜማ ላይ ቆመን፣ ማንም ይግዛ ማን ገዢዉ አካል የዜጎቹ መብት ሳይገሰሥ፣ በተፍጥሮ የተጎናፀፉት ሰብዓዊ መብታችዉ ሳይገፈፍ፣ ሕገ መንግሥታቸዉን በራሳቸዉ ወኪሎች አርቅቀዉና አፀድቀዉ፤ ባጭሩ ሌሎችን የማኗኗር ሕይወት የሚገፉባት ሳትሆን፤ እነርሱ እራሳቸዉም የሕይወትን ጣዕም የሚቀምሱባት ሀገር ኢትዮጵያዊነት አሰባሳቢ ማንነት አሸንፎ እንዲወጣ፤ እንዚህን ሁሉ ተግባራት በዋስትናነት የሚመክቱ ተቑማትን በማረጋገጥ፣በተደላደሉ መሠረቶች ላይ የቆመ ብሔራዊ አንድነትን መፍጠር ይኖርብናል ነዉ የመልዕክቱ አስኹል። ደራሲዉ በመጨረሻም የመፅሃፉን ዋንኛ የመዳረሻ ግብ ሲያጠቃልለዉ፣ ለዜግነታዊ መንግሥት መሠረት የመጣል ክንዉን የሩቅ ተግባር እንጅ፣ ባንድ ጀንበር የሚከናወን የይድረስ፣ የይድረስ ተግባር አለመሆኑን አፅንኦት ይሰጠዋል። …. አሰባሳቢ የሆነ ሀገራዊ ማንነት ለመቅረፅ የምናደርገዉ ረዥም ጉዞም በሀገራችን  ከምንመኘው ዲሞክራሲያዊ ለውጥ ጋር ተዳብሎ የሚታይ ብቻ ሳይሆን፤ በዋንኛነት ነጥሮ መዉጣት ያለበት ብሔራዊ አጀንዳችን መሆኑንም ያሠምርበታል። ይህንን ሀገራዊ ራዕይም ወደ ተግባር ለመመንዘር፤

በሥልጣን ላይ ያለዉን መንግሥት ማስገደድ፣ ካልሆነም ማስወገድ፣

የብዙዎች ስምምነት የታከለበት ብሔራዊ መግባባት ላይ መድረስ፤

የሸግግር ጊዜ ተግባራትን በመግባባት መንደፍ፤

እነኝህ ቅድመ ሁኔታዎችም ለምንፈልገዉ የለዉጥ እንቅስቃሴ ወሳኞች በመሆናቸዉ፤ ስለሌላዉ ማዉራቱን አቆመን እርስ በራሳችን ስለወደፊቱ መነጋገር ማስፈለጉን አስረግጧል፤ ዜጋዉ እርስ በርሱ ሳይተማመን ኢትዮጵያዊነት አይሰበክም ይላል። ከዚሁ ጋር አያይዞም፣ በአካል ስንነጋገር፣ የብዙ ዓመት ጟደኛቸዉ በመፅሃፉ ጀርባ ባስመዘገቡት መወድስ፣ < የልቡን እንደ ልቡ፣ ለነገ ሳይል የሚናገረዉ ጟደኛዬ> የሚለዉን የዶክተር ደረጀ ዓለማዬሁን አባባል ጋሼ የሱፍ ሲያጫዉተኝ  ከዚህ ይልቅ <ለነገ ብሎ የልቡን እንደ ልቡ የሚናገረዉ ቢባል እኔን በሚገባ ይገልፀኛል። ይህንንም የምለዉ ዝምብዬ ከምድር በመነሳት ሳይሆን፣ የወደፊቱ የአብሮነታችን ጉዳይ፣ ወይም የነገዉ ዕጣ ፋንታችን ስለሚያሳስበኝ ነዉ ይላል። በቅርቡም ዋሸንግተን ላይ በተካሄደ ሕዝባዊ ስብሰባ የአማርኛው ቃና የሚጥመዉ የጊዜያችን ጥቁሩ ሰዉ የአኝዋኩ  ኢትዮጵያዊ ኦባንግ ሜቶ ስለነገዉ ካሰብን፣ ለመተማመን እንነጋገር በማለት እንደደገመዉ፣ ድሉን እንድናቃርብና ኢትዮጵያዊነት አሰባሳቢ ማንነት እንዲያብብ፣ እንዲፈካና  በአሸናፊነትም ተመንጥቆ እንዲወጣ ማድረግ አለብን ባይ ነዉ ጋሼ ዩሱፍ። እኔ በማንነት ፍለጋዉ ጉዟችን የአፋሩን ቅኔ፣ ቅኝት በተገለጸዉ መልክ  ተረድቼዋለሁ። እናንተስ? ለማንኛዉም ገና መፅሃፉን አግኘታችሁ ላላነበባችሁ መልካም ንባብ።

Comment

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 


9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ፀኃፊ አቶ ግርማ በቀለ በማህበራዊ ድረ ገጽ በሰጡት አስተያየት መልስ ሰጡ

$
0
0

የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ፀኃፊ አቶ ግርማ በቀለ በማህበራዊ ድረ ገጽ በሰጡት አስተያየት ትብብሩ ያለ ቅድመ ሁኔታ ወደ ምርጫ እንደሚገባ በማህበራዊና በሌሎች ሚዲያዎች ተላልፏል፡፡ ጉዳዩን አስመልክቶ ጥያቄ ያቀረብንላቸው አቶ ግርማ እንደሚከተለው መልስ ሰጥተውበታል፡፡

10402715_628438880615107_772756782297672198_n‹‹እኛ ቅድመ ሁኔታ ያስቀመጥነው ምርጫ ላይ ሳይሆን የምርጫ ሂደቱ ላይ ነው›› አቶ ግርማ በቀለ የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ፀኃፊ

አንድ የሌላ ፓርቲ ደጋፊ ማህበራዊ ድረ ገጽ ላይ ምርጫው ውስጥ ስለመግባትና አለመግባት ላይ ባነሳው ክርክር የግል አስተያየቴን ሰጥቼ ነበር፡፡ ይህ የግል አስተያየትም ትብብሩም ሆነ አባል ፓርቲዎች በምርጫው ሂደት ላይ ምንም አይነት ጥያቄ ሳያነሱ ወደ ምርጫው እንደሚገቡ ተደርጎ በማህበራዊ ሚዲያዎች ተሰራጭቷል፡፡

አንድ ፓርቲ በምርጫ ቦርድ ተመዝግቦ በሰላማዊ መንገድ እንቀሳቀሳለሁ ሲል የምርጫ ፓርቲ ነው ማለት ነው፡፡ በመሆኑም የምርጫ ፓርቲ ሆኖ እንደ ስልት በምርጫ ላይ ቅድመ ሁኔታ ሊያቀርብ አይችልም፡፡ ቅድመ ሁኔታ ሊያቀርብ የሚችለው በምርጫው ሂደት ላይ ነው፡፡ በሌላ በኩል አንድ በሰላማዊ መንገድ እንቀሳቀሳለሁ የሚል ፓርቲ ስልጣን ሊይዝ የሚችለው በምርጫ ነውና ምርጫ እገባለሁ ብሎ ሊያውጅ አይችልም፡፡ የምርጫው ሂደት ላይ ጥያቄ ሲያነሳ ደግሞ ከምርጫው ራሱን አገለለ ማለት አይደለም፡፡ እኛ በምርጫው ሂደት ላይ ጥያቄ በማንሳታችን ከአሁኑ ራሳችን ከምርጫ ያገለልን የሚመስላቸው አካላት አሉ፡፡ ግን እኛ ራሳችን አላገለልንም፡፡ ከአሁኑ ምርጫ እንሳተፋለን ብሎ ማወጅም አላስፈለገንም፡፡ ከዚህ ይልቅ ‹‹ነጻነት ለፍትሓዊ ምርጫ›› በሚል ምርጫው ፍትሓዊ እንዲሆን እየታገልን ነው፡፡

ስለሆነም ምርጫው ሂደት ላይ ጥያቄዎችን አንስተን ምርጫው ፍትሓዊ እንዲሆን እየታገልን ነው፡፡ ስለሆነም በምርጫው ሂደት ላይ አለን ማለት ነው፡፡ ነገር ግን በሂደቱ ላይ አለን ማለት ጥያቄዎቹ ሳይመለሱ ምርጫውን እንሳተፋለን ማለት አይደለም፡፡ በምርጫው ሂደት ሲሳተፍ ቆይቶ ሂደቶቹ ፍትሓዊ ባለመሆናቸው፣ የተነሱት ጥያቄዎች ባለመመለሳቸውና በሂደቱ ላይ የተቀመጡት ቅድመ ሁኔታዎች ባለመሟላታቸው ምርጫው አንድ ቀን ሲቀረው ራሱን ከምርጫው ያገለለ ፓርቲ አውቃለሁ፡፡

ከአሁኑ ምርጫው ላይ ጥያቄ በማንሳታችን ከምርጫው ራሳችን አግልለናል ማለት አይደለም፡፡ እኛም ቅድመ ሁኔታ ያስቀመጥነው ምርጫ ላይ ሳይሆን የምርጫ ሂደቱ ላይ ነው፡፡ ሂደቱ ፍትሓዊ ካልሆነ አጃቢ መሆን አንፈልግም፡፡ ለዛም ነው ሂደቱን ለማስተካከል ‹‹ነጻነት ለፍትሓዊ ምርጫ›› በሚል እየታገልን ያለነው፡፡ በትግላችን መሰረት ሂደቱን እናስተካክለዋለን ብለን እናስባለን፡፡

ደማቅ ህዝብዊ ስብሰባ በኖርዌ በርገን ከተማ ቅዳሜ Dec 13.2014 ዓ.ም ተካሄደ

$
0
0

ለዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት በኖርዌ በርገን ቅርንጫፍ አዘጋጂነት የተካሄደው ይህ ህዝባዊ ስብሰባ ከመላው የኖርዌ ከተሞች እና በአቅራቢያዊ ከሚገኙ አጎራባች ሀገሮች የመጡ ኢትዮጵያዊያኖች ተሳታፊ ሆነውበታል:

23

ስብሰባው የተጀመረው ኢትዮጵያ ውሰጥ ባለው አስከፊ ስርዓት በቀጥታ የመንግስት ትእዛዝ በስውርም ይሁን በግለጽ ህይወታቸውን ላጡ ፣ቤተሰባቸው ለተበተነባቸው፣ትዳራቸው ለፈረሰ፣ ጧሪ ቀባሪ አጥተው የስቃይ ህይወት ለሚገፉ፣ በጎረቤት ሀገሮች እስር ቤቶች ውስጥ ለሚሰቃዩ፣ በስደት በበረሃውና በባህር ውሰጥ ህይወታቸው አልፎ ያለቀባሪ ለቀሩት ወገኖቻችን የአንድ ደቂቃ የህሊና ፀሎት በማድረግ ነበር።

በመቀጠል ስብሰባውን በንግግር የከፈቱት ለዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት በኖርዌ በርገን ቅርንጫፍ ዋና ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አንተነህ አማረ ሲሆኑ፡ እሳቸውም እንግዶቹንና ተሰብሳቢዎቹን እንኳዋን ደህና መጣችሁ ካሉ በኋላ በሀገራችንና በህዝባችን ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍና በደል በመዘርዘር ህብረተሰባችን ከዚህ ውስብስብ ችግር እንዲወጣ ሁላችንም የየድርሻችንን መወጣት ይጠበቅብናል በማለት እዚህ በአዳራሽ ውስጥ የተሰባሰብነው ተመካክረን መፍተሄ ለማምጣት እስከሆነ ድረስ ሁላችሁም በንቃት እንድትሳተፉ እየጋበዝኩ መልካም የውይይት መድረክ እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ በማለት ንግግራቸውን አጠናቀዋል።

231

በመቀጠል ንግግር ያደረጉት ለዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት በኖርዌ  ዋና ሊቀመንበር የሆኑት አቶ ይኋንስ አለሙ ሲሆኑ ፡እሳቸውም ይህ የዛሬው ስብሰባ ለኔ በሁለት አብየት ምክነያቶች በጣም  የተለየ ነው ካሉ በኋላ ይህውም  አሉ 1ኛ/ ይህ ስብሰባ ቅርንጫፍ ጽ∕ቤቱ እንደ አዲስ ከተዋቀረ በኋላ በመሆኑ እና 2ኛ. በራስ አነሳሽነት ያለምንም  ድጋፍ በቅርንጫፍ  ጽ∕ቤቱ ብቻ መከናወኑ በማለት አድናቆታቸውን ገልፀዋል። በመቀጠልም የሰማያዊ እና የዘጠኙ ፓርቲዎቸ ህብረት በቅርቡ በመስቀል አደባባይ ያደረጉትን ጀግንነት የተሞላበት እና ብዙ ዋጋ የተከፈለበት የሰላማዊ ሰልፍ ህዘባችን የፍርሃትን ደመና ገፎ አንባገነኖችን ለመጋፈጥ ከመቼውም ጊዜ በላይ ቆርጦ መነሳቱን የሚያመለክት መልካም ጅምር ነው በማለት እኛም እንደከዚህ ቀደሙ ሁሉ ለዲሞክራሲ ፣ለፍትህ እና ለነፃነት የሚሰሩ ኋይሎችን በሞራል ፣ በቁሳቁስና እና በፋይናንስ መደጋፋችንን እንቀጥላልን በለዋል በመጨረሻም መደራጀት ህብረትን ፣ህብረት ኋይልን፣ኋይል ደግሞ ለውጥን ያመጣል ሰለዚህ እንደራጅ እና ከማንም ትእዛዝ ሳንጠብቅ በራሳችንና በምንችለው ሁሉ ለትግሉ አስተዋፆ በማድረግ ከባርነት እራሳችንን ነፃ እንውጣ ብለዋል።

2311

ግንቦት 7ን በመወከል በስብሰባው ላይ የተገኙት  የግንቦት 7 ስራ አስፈፃሚ አባል የሆኑት ዶ∕ር ሙሉዓለም አዳም በበኩላቸው “ለምን ትግሉ እረጅም ጊዜ ወሰደ” በሚል ርዕስ ሥር ስድስት ነጥቦችን በማንሳት ጥልቅ እና ሰፊ የሆነ ትንተና ያቀረቡ ሲሆን ተሰብሳቢዊው በከፍተኛ ተመስጦ ውስጥ ሆኖ ሲከታተላቸው ነበር፡ እነሱም..

1ኛ. ሰለ ነፃነት ያለን ግንዛቤ አነስተኛ መሆን ወይም ነፃነትን ከሀገር ጋር ብቻ ማያያዝ፡

2.የወያኔ ቅጥ ያጣ አፈናና መረን የለቀቀ ረገጣ፡

3.የተወሰነው የህብረተሰብ ክፍል አውቆም ይሁን ሳያውቅ የወያኔ ፕሮፓጋንዳ ሰለባ መሆን፡

4.ከቤተሰብም ይሁን ከአካባቢ የወሰድነው ጎጂ በህሪ ማለትም ይሉኝታ እና አደርባይነት፡

5.በፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ ተሰባስበው ያሉ ግለሰቦች ከሀገርና ከህዝብ ጥቅም ይልቅ ለድርጅት ፍላጎት ተገዢ መሆን እና

6.በጥናት ላይ የተመሰረተ በብስለት የታገዘ የፖለቲካ ትግል አለመኖር ናቸው ብለዋል፡

ተሰብሳቢውም ብዙ ጥያቄዎችንና አስተያየቶች ለሁለቱ እንግዶች ያቀረበሲሆን ከመድረክም ምላሽ ተሰቶባቸዋል፡ በመጨረሻም ለዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት በኖርዌ በርገን ቅርንጫፍ ዋና ሰብሳቢ አቶ አንተነህ አማረ በስብሰባው በጣም መርካታቸውን በመግለፅ እንጋዶቹንና ተሰብሳቢውን በማመስገን የስብሰባው ፍፃሜ ሆኗል።

ማርቆስ ዐብይ ከበርገን ኖርዌ

 

 

የስቃይ ድምጾች በሦስተኛ ፖሊስ ጣቢያ

$
0
0

addis ababa semayawi party 1
በላይ ማናዬ

ካዛንቺስ በተለምዶ እንደራሴ በተባለው ቦታ ቅዳሜ ህዳር 27 ቀን 2007 ዓ.ም ረፋድ ላይ የሆነው እንዲህ ነው….

በቅርቡ በሰማያዊ ፓርቲ እና በሌሎች 8 ፓርቲዎች ስምምነት የተመሰረተው የ9ኙ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ስብስብ ለአንድ ወር የሚቆይ የመጀመሪያ ዙር የትግል መርሃ-ግብር ማሳረጊያ ሊደረግ በነበረው የ24 ሰዓት የአዳር የተቃውሞ ሰልፍ ያሉ ሁኔታዎችን ለመዘገብ የሰልፉ መነሻ በሆነው የሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ ተገኝቼ ነበር፡፡ ሰልፉ ይጀምርበታል ከተባለው ጊዜ መዘግየቱን አስመልክቶ ከቢሮ ወጣ ብዬ ሁኔታውን ለመቃኘት እየሞከርኩ ነበር፡፡ ድባቡ ፍጹም ዝብርቅርቁ የወጣ ነበር፡፡ ሰልፍ ለመውጣት የወሰኑት ሰዎች በቢሮው ውስጥ መሰናዷቸውን እያደረጉ በነበረበት ሰዓት ከቢሮ ውጭ ያሉ ፖሊሶችና ሲቪል የለበሱ የደህንነት ኃይሎች ደግሞ ቁጥራቸው በየደቂቃው እየጨመረ አካባቢውን መክበብ ተያይዘውት ነበር፡፡

ሁኔታውን በአንክሮ ለተመለከተው በደቂቃዎች ውስጥ ‹ፍጥጫ› ሊጀመር እንደሚችል አመላካች ነበር፡፡ የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ የእውቅና ደብዳቤ ለአስተዳደሩ አስገብቻለሁ፣ ስለሆነም ሰልፉን ለማድረግ ወስኛለሁ ሲል መንግስት በበኩሉ ሰልፉን ‹ፈቃድ አልሰጠሁትም› ሲል አስታውቆ ነበር፡፡ ዳሩ ግን ትብብሩ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ‹ማሳወቅ› እንጂ ‹ማስፈቀድ› አይጠበቅብኝም ሲል አዋጅ ጠቅሶ ደብዳቤ ለአስተዳደሩ አስገብቶ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡

በዚህ አለመግባባት ውስጥ ተሁኖ ነበር የአዳር ሰልፉ ሊካሄድ ሽርጉድ ይባል የነበረው፡፡ በእንዲህ ያለ ሁኔታ ውስጥ ሰልፉ ከሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ ውስጥ ተጀመረ፡፡ የሰልፉ አጀማመር በራሱ የሚገርሙ ነገሮች ነበሩት፡፡ ባላሰብኩት ፍጥነት ቢሮ ውስጥ የነበሩት ሰዎች በአንዴ ሰብሰብ ብለው ቀጥታ ከበር እንደወጡ መፈክሮችን እያሰሙ በፈጣን እርምጃ ወደፊት ተስፈነጠሩ፡፡ እርምጃየን በእነሱው ፍጥነት ልክ አስተካክየ መቅረጸ-ድምጼን አበራኋት፡፡ ‹‹ነጻነት! ነጻነት! ነጻነት!….›› እያሉ መፈክሩን አስተጋቡት፡፡

ፖሊሶች በሰልፈኞች ፍጥነት ግር የተሰኙ መሰሉ፡፡ ሰልፈኞቹ በጣም ብዙ ፖሊሶች በተሰደሩበት መንገድ ፊት ለፊት ቀጥታ ገሰገሱ፡፡ ይህኔ ፖሊሶች እርምጃ ለመውሰድ ተቁነጠነጡ፡፡ ሰልፈኞች መፈክራቸውን ለወጡ፤ ‹‹ፖሊስ የህዝብ ነው! ፖሊስ የህዝብ ነው! ፖሊስ የህዝብ ነው!›› እያሉ ለፖሊሶች መልዕክት ለማስተላለፍ ሞከሩ፡፡ ይህኔ ሁኔታዎች ከመቅጽበት ተለዋወጡ፡፡ እዛ የነበረው የ‹ፀጥታ ሰራተኛ› በሙሉ እንደንብ ሰልፈኞች ላይ ሰፈረ፡፡ እንደደነበረ ፈረስ ያገኙትን መርገጥ ጀመሩ፡፡ በሰልፈኞች ላይ የሆነው ሁሉ በእኔም ላይ ሆነ፡፡ የመጀመሪያው ዱላ ካረፈብኝ በኋላ ያለውን የዱላ ብዛት አሁን አላስታውስም፡፡ ብቻ ዘግናኝ ነበር!

በእርግጠኝነት በሂደቱ ውስጥ ሊፈጠሩ የሚችሉ አንዳንድ ደስ የማይሉ ነገሮች ሊኖሩ እንደሚችሉ ቀድሜ ብገምትም፣ የሆነው ግን ከግምቴም በላይ እጅግ አሳፋሪ ድርጊት ነበር፡፡ ሴቶች እና እድሜያቸው ከ70 በላይ የሆኑ አዛውንቶች ርህራሄ አልተደረገላቸውም፡፡ እንዲያውም በእነሱ ላይ ሳይበረታ አልቀረም፡፡ ያ ሁሉ ፖሊስና ‹ሌሎች የፀጥታ ሰራተኞች› እንደአሸን የፈሉ ነበሩ፡፡ አንድም ዱላ ሳይሰነዝሩ ሰልፉን ማገት በተቻላቸውም ነበር፡፡ ግን አልሆነም፡፡ ትዕዛዝ ይመስላል፤ ዜጎችን ደብድብ የሚል ትዕዛዝ! ያሳፍራል፣ ያሸማቅቃል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች አቧራ ላይ ተጥለው ተደበደቡ፡፡ ሴቶች ሆዳቸውን ተረገጡ፡፡ አዛውንቶች ዘለፋ ከተሞላበት ኃይለ-ቃል ጋር ድብደባ ተፈጸመባቸው፡፡ ጋዜጠኛ ሰልፍ ላይ ተገኝተህ መዘገብ አትችልም ተብሎ ተቀጠቀጠ፡፡ አቶ ኤርጫፎ ኤርደሎ እና አቶ ቀኖ አባጆቭር (አባዬ) ተይዘው ከእኛው ጋር ሲንገላቱ ሳይ በእኔ ላይ የደረሰውን ሁሉ ረሳሁት፡፡ ልጆቻቸውና የልጅ ልጆቻቸው በሚሆኑ ‹የጸጥታ ሰራተኞች› የአሳፋሪው እርምጃ ሰለባዎች ሆኑ፡፡ በእርግጥ እነ አባዬ ስለእኛ እንጂ ስለራሳቸው አልተሰማቸውም፡፡ እኛ ደግሞ በእነሱ ላይ ስለሆነም የበለጠ እናዝን ነበር፡፡

ይህ ሁሉ ድርጊት በካዛንቺስ እንደራሴ አካባቢ ከመሆኑ ከደቂቃዎች በፊት ብዙ ዜጎች በመስቀል አደባባይ እና በሌሎች ስፍራዎች እየተያዙ እንደነበር አውቃለሁ፡፡ መንግስት የተቃውሞ ድምጽ የሚያሰሙ ዜጎችን ለማፈን ቆርጦ እንደተነሳ ተገነዘብኩ፡፡ በዕለቱ የሆነው ተራ እስር አልነበረም፤ አፈሳ ነበር የተደረገው፡፡ ጅምላ እስር ነበር የተፈጸመው፡፡ ካዛንቺስ እንደራሴ አካባቢ የሆነው ግን በኃይልና በድብደባ የታጀበ ነበር፡፡ በድብደባ እራሱን ስቶ የቆየው ወጣት አቤል ኤፍሬምን ጨምሮ ብዙዎች ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡

በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሆነን በመኪና እንደእቃ እንድንጫን ተደርገን ካዛንቺስ አካበቢ ወደሚገኘው ስድስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ተጋዝን፡፡ ጣቢያ እንደደረስን በአንድ ቦታ እንድንሰበሰብ ተደርገን በፎቶ እና ቪዲዮ ካሜራ ቀረጻ ተደረገብን፡፡ የሚገርመው ራሱን ስቶ ወድቆ የነበረው አቤል ሳይቀር በዚያ ሁኔታ ውስጥ ሆኖ ህክምና ሳያገኝ ቀረጻው ይደረግበት ነበር፡፡ ግራ ቀኜን ዞር ዞር ብዬ የተያዙ ሰዎችን አስተዋልኩ፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃልን ጨምሮ የተለያዩ የፓርቲ አመራሮች ተይዘዋል፡፡ አንዳንድ በዚያ ሲያልፉ የተገኙ፣ ስለጉዳዩ ምንም የማያውቁ ሰዎችም አብረው ተጀምለው ተይዘዋል፡፡ ከእነዚህ መካከል በሁኔታው ተደናግጠው የሚያለቅሱ ሰዎች ይገኙበት ነበር፡፡ እነዚህ ሰዎች ሰልፍ ይሁን ሌላ የሚያውቁት ጉዳይ አልነበረም፡፡ እንዲሁ በቦታው ስለተገኙ ብቻ የተያዙ ነበሩ፡፡

ስድስተኛ ፖሊስ ጣቢያ እያለን ከመስቀል አደባባይ የተያዙ ሰዎችም በጣቢያው እንደሚገኙ ተገነዘብኩ፡፡ በጣም ብዙ ፖሊሶች ግቢውን ሞልተውታል፡፡ ብዙዎች ሰልፈኞችን ይሳደባሉ፤ አንዳንዶች አሁንም ለመደባደብ ሲቋምጡ አስተዋልኩ፡፡ ገረመኝ! ከመደብደብ የሚገኘው ትርፍ ምንድን ነው? ቀደም ብሎ በተያዝንበት ቦታ ላይ ብዙ ከተደበደብን በኋላም ቢሆን ድብደባው እንዲቆም ትዕዛዝ የሰጡት የየካ ክ/ከተማ ፖሊስ አዛዥ ኮማንደር ዘውዴን በዓይኔ ፈለኳቸው፡፡ ግን ላገኛቸው አልቻልኩም፤ የእውነት ከድብደባው የሚገኘውን ትርፍ ማወቅ እፈልግ ነበር፡፡ ፍርሃቴ ልበለው አልያ ድንጋጤዬ ብን ብሎ ጠፍቶ ስለነበር ማናቸውንም አይነት ጥያቄ ልጠይቃቸው እፈልግ ነበር፡፡ የእውነት በወገኖቼ መካከል መገኘቴን እንኳ እጠራጠር ነበር፡፡ እንዴት ሰው አንዲት ጠጠር እንኳ በእጁ ሳይዝ፣ በሰላም ድምጹን ስላሰማ ብቻ ይህን ያህል ድብደባ በራሱ ወገኖች፣ በመንግስት ኃይሎች ይደርስበታል?

ስድስተኛ ብዙም አልቆየንም፤ የቪዲዮ እና የፎቶ ቀረጻው እንደተጠናቀቀ ወዲያውኑ ወደሌላ ፖሊስ ጣቢያ እንድንዛወር ተደረግን፡፡ የደረስንበት ፖሊስ ጣቢያ ፖፖላሬ ፖሊስ ጣቢያ ነበር፡፡ በዚህ ፖሊስ ጣቢያ ደርሰን ትንሽ ጊዜ እንደቆየን ቃላችንን እንድንሰጥ ተደረግን፤ ድጋሜ ፎቶ እንድንነሳ ሆነ፣ አሻራም ተነሳን፡፡ ይህን አድርገው ወደተለያዩ ክፍሎች ካጨቁን በኋላ ምሽት ላይ እንድንወጣ ታዘዝን፡፡ በዚህ ጊዜ በታሳሪዎች መካከል የተለያዩ አስተያየቶች ይሰጡ ጀመር፡፡ አንዳንዱ ልንፈታ ነው ሲል ሌላው ደግሞ ወደ ካምፕ ሊወስዱን ነው ይል ነበር፡፡ ቀሪዎች ደግሞ ወደሦስተኛ ፖሊስ ልንወሰድ እንደሆነ ግምታቸውን ሰነዘሩ፡፡ እነዚህኛዎቹ ልክ ነበሩ፡፡ ጉዙው ወደ ሦስተኛ ነበር፡፡ በፖለስ መኪና እና ሞተር ሳይክል ታጅበን፣ የሳይረን ድምጽ በሚያሰማ ሞተረኛ መሪነት ሦስተኛ ፖሊስ (የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ዋና መስሪያ ቤት) ተወሰድን፡፡

ወደሦስተኛ ፖሊስ እንድንዛወር የተደረግነው ታሳሪዎች ከመስቀል አደባባይ የተያዙትን አይጨምርም፤ ቁጥራችንም 44 ነበርን፡፡ ሌሎቹ እስከተፈቱበት ዕለት ድረስ እዚያው ፖፖላሬ ጣቢያ ቆይተዋል፡፡ ሦስተኛ ፖሊስ እንደደረስን በሁለት እንድንከፈል ግድ ሆነ፡፡ በአመራር ደረጃ ላይ ያሉት ወደቀዝቃዛ ክፍል (በረዶ ቤት) እንዲገቡ ሲደረጉ፣ ሌሎቹ ደግሞ በተለያዩ ክፍሎች (ጨለማ ክፍልን ጨምሮ) እንድንገባ ተደረግን፡፡ በዚያው በህዳር 27/2007 ዓ.ም ዕለት የሦስተኛ ፖሊስ ቆይታችን አሃዱ ተባለ፡፡ (በነገራችን ላይ አብዛኞቻችን ታሳሪዎች ለ24 ሰዓታት ያህል ምግብና ውሃ በአፋችን አልዞረም ነበር፡፡)

የስቃይ ድምጾች በሦስተኛ ፖሊስ

ሦስተኛ ፖሊስ አሁን ላይ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ዋና መስሪያ ቤት የሚገኝበት ስፍራ ነው፡፡ ቦታው ድሮ በሚታወቅበት ገጽታው ሳይሆን በቅርቡ በተገነባው ዘመናዊ ህንጻው ተጀቡኖ በግርማ ሞገስ የሚታይ ነው፡፡ ይህ ቦታ በፌደራል ፖሊስ የማዕከላዊ ምርመራ ጣቢያን ተጎራብቶ የሚገኝ ነው፤ (አንዳንዶች ከማዕከላዊ ጋር በምድር ዋሻ ይገናኛል ይላሉ፤ ይህን በተመለከተ እንደ ቀልድ ከእስር በወጣንበት ቀጣይ ቀን ሞባይል ስልኬን ልወስድ ወደጣቢያው ባመራሁበት ወቅት ለመርማሪዬ ፖሊስ በቀልድ መልኩ ጥያቄ አንስቼለት ነበር፡፡ መርማሪው ‹‹ማዕከላዊ እና እኛ አንገናኝም!›› ነበር ያለኝ በጥያቄየ ግር በመሰኘት አተያይ እያየኝ)፡፡ ሦስተኛ ፖሊስ በህንጻው ዘመናዊ ይሁን እንጂ በአሰራር ግን ብዙ ገራሚና አሰቃቂ ድርጊቶችን የሚያስተናግድ ቦታ መሆኑን በቆይታየ ለመታዘብ ችያለሁ፡፡

ወደ ጉዳዬ ስመለስ፣ ሦስተኛ የገባን ዕለት (ህዳር 27) በሌሊት ምርመራ ሲደረግብን ነበር ያደርነው፡፡ በፖፖላሬ ፖሊስ ጣቢያ የሰጠነውን ቃል በመድገም ሙሉ ማንነታችን ከመዘገቡ በኋላ ሌሎች ምርመራዎችም ተደረጉምብን፡፡ በምርመራው ወቅት ከሞላ ጎደል ድብደባ አልደረሰብንም፡፡ ምናልባትም በተያዙበት ወቅት የተደበደቡት ይበቃቸዋል ተብሎ ሊሆን ይችላል፡፡ በቀጣዩ ቀን ሁላችንም ፍርድ ቤት እንድንቀርብ የተደረግን ሲሆን ፖሊስ ፍርድ ቤቱን 14 ቀናት የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠየቀ፤ የትብብሩ አመራሮች በበኩላቸው በሰልፈኞቹ በኩል የተፈጸመ አንዳችም ህገ-ወጥ ተግባር አለመኖሩን በመግለጽ ፍርድ ቤቱ በነጻ እንዲያሰናብተን ጠየቁ፡፡ በተለይ የትብብሩ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ‹‹ኢህአዴግ በዘንድሮው ምርጫ ሙሉ ለሙሉ እንደምናሸንፈው ስላወቀ ነው ያሰረን፤ ይህም ህገ-መንግስቱን የጣሰ ነው›› ሲሉ አስረድተው ነበር፡፡

በዚሁ ፍርድ ቤት በቀረብን ጊዜ ብዙ አስገራሚ ነገሮችን ታዝቤያለሁ፡፡ በተለይ በታሳሪዎች በኩል የደረሰባቸውን ድብደባ ተከትሎ ህክምና አለማግኘታቸውን፣ እንዲሁም አመራሮቹ በበረዶ ቤት ስለሚገኙ ለጤናቸው አስጊ ስለሆነ የተሻለ አያያዝና ህክምና እንዲደረግላቸው ለፍርድ ቤቱ ባስረዱ ጊዜ የዕለቷ ዳኛ ያሉትን አልረሳም፤ ወደ ፖሊሶች ዞር ብላ ‹‹የጠየቁትን ህክምና እንዲያገኙ አድርጉ፣ ለእናንተም ለመቅጣት እንድትችሉ በህይወት ይቆዩላችሁ›› ነበር ያለችው፡፡ ጆሮዎቼን ማመን ነበር ያቃተኝ! ሁኔታው ሰው ቅጣት እንዲቀበል ብቻ ነው በህይወት መቆየት ያለበት ማለት ነው ብዬ ራሴን እንድጠይቅ አድርጎኛል፡፡

ፍርድ ቤት የነበረን ቆይታ አብቅቶ ወደ ሦስተኛ ተመለስን፡፡ ምርመራውም ቀጠለ፡፡ በምርመራ ወቅት ተመሳሳይና አሰልቺ ጥያቄዎች ነበር በተደጋጋሚ የሚቀርቡልን፡፡ በጣም አስገራሚው ነገር ደግሞ መርማሪዎቹ የኢሜልና ፌስ ቡክ አካውንት እስከ ይለፍ ቃል (password) ድረስ እንዲሰጣቸው መጠየቃቸው ነበር፡፡

ኢሜልና ፌስቡክ ይኖረኝ እንደሆን ጠየቀኝ፡፡ እንዳለኝ ነገርኩት፡፡ አስከትሎ አካውንቱንና ፓስወርዱን እንድነግረው ጠየቀኝ፡፡ ‹እንዴት ይሆናል፣ ይሄኮ የግል ጉዳይ ነው፤ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ እንዴት ስጠኝ ትላለህ?› ስል መልሼ ጠየቅኩት፡፡ ፈቃደኛ ባለመሆኔ አንዴ በንዴት ሌላ ጊዜ በማባበል አይነት የጠየቀውን እንድነግረው ሞከረ፡፡ በአቋሜ መጽናቴን ሲያይ፣ ‹‹ይሄኮ የመንግስት አሰራር ስለሆነ ነው፤ ባትናገርም እኮ መንግስት ያውቀዋል›› አለኝ፡፡ አልመለስኩለትም፡፡ እሱም ‹‹ኢሜልና ፌስቡክ አካውንት አለው፣ ግን ለመናገር ፈቃደኛ አይደለም›› ብሎ የምርመራ መዝገቡ ላይ ሲያሰፍር አነበብኩ፡፡

ከምርመራ ክፍል ወጥቼ ሌሎች ታሳሪዎች ጋር ስንገናኝ ተመሳሳይ ጥያቄዎችን እንዳስተናገዱ ነገሩኝ፡፡ ለመሆኑ ይሄ ምን አይነት የመንግስት አሰራር ይሆን?

የሦስተኛ የስድስት ቀናት ቆይታዬ ለእኔ ብዙ ነገሮችን እንድቃኝ ያስቻለኝ ስለነበር መታሰሬን በግድም ቢሆን ሳልወደው አልቀረሁም፡፡ ምናልባት ባልታሰር ኖሮ እኒያን ሁሉ ባለብዙ ታሪክ እስረኞች አላውቃቸውም ይሆናል፡፡ በታዳጊ ሃና ላላንጎ አስገድዶ መደፈር ምክንያት ተጠርጥረው በእስር ላይ ከሚገኙት አምስት ተጠርጣሪዎች እስከ በነፍስ ግድያና ሌሎች ወንጀሎች ተጠርጥረው እስከገቡት ወንድሞች ጋር ብዙ ታሪኮችን አደመጥኩ፡፡ በምርመራ ወቅት የደረሰባቸውን እና እየደረሰባቸው ያለውን ሰቆቃም ለመገንዘብ ቻልኩ፡፡

ሦስተኛ ፖሊስ በዘመናዊ ህንጻ ውስጥ ኋላቀር የምርመራ ዘዴ የሚተገበርበት ስፍራ መሆኑንም ከብዙ ሰዎች ላይ በደረሰው በደል አየሁ፡፡ በምርመራ ወቅት በተፈጸመባቸው ድብደባና ሌሎች የማሰቃያ ዘዴዎች ምክንያት የአካል ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች እዛ ቤት ውስጥ ይገኛሉ፡፡ በረዶ ቤት (የትብብሩ አመራሮች ታስረውበት የነበረው ቤት) አንዱ የምርመራ ወቅት ማቆያ አሰቃቂ ስፍራ ነው፡፡ ሌላው ‹ቆመህ እደር› የሚባል ሲሆን ተጠርጣሪዎች ለቀናት በዚህ ስፍራ ቆመው ውለው ቆመው እንዲያድሩ የሚደረግበት እንደሆነ በዚህ ሁኔታ ላይ ያለፉ ታሳሪዎች አጫውተውኛል፡፡ ብዙዎች በ‹ቆመህ እደር› ያለፉ ሰዎች የተለያዩ የአካላዊና ስነ-ልቦናዊ ጉዳት ሰለባ ይሆናሉ፡፡

እውነትም በሦስተኛ ፖሊስ ያለው የምርመራ ስልት እጅግ ኋላቀር ብቻ ሳይሆን ኢ-ህገ-መንግስታዊም ጭምር ነው፡፡ በዚህ ስፍራ ተጠርጣሪዎች ሰውነታቸው በስፒል ይጠቀጠቃል፣ ትልቅ ሃይላንድ ውሃ ተሞልቶ ብልታቸው ላይ ይንጠለጠላል፣ እግራቸውን ከፍተው ቆመው እንዲያድሩ ይደረጋል፣ ከፍተኛ ድብደባ ይፈጸማል፣ ከብዙዎቹ እስረኞች አፍ እንደሰማሁትና በአካላቸው ላይ የደረሰውን ጉዳት በዓይኔ እንዳየሁት፡፡ በዚህ አይነት ምርመራ የሚያልፉ ሰዎች ምርመራቸው እስኪያልቅ (ለሳምንታት) ከቤተሰብ ጋር መገናኘት አይፈቀድላቸውም፡፡ በነገራችን ላይ በሰልፉ ወቅት የተያዝን እና በሦስተኛ የነበርን ወንድ እስረኞች በሙሉ ቤተሰብ፣ ወዳጅ ዘመድ እንድንገናኝ አይፈቀድልንም ነበር፡፡

በሦስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ባለው ከባድ የማሰቃየት የምርመራ ዘዴ የተሰቃዩ ተጠርጣሪዎች አንዳንዶቹ ራሳቸውንም ለማጥፋት ሙከራ አድርገው ያልተሳካላቸውን አግኝቼ አናግሬያቸው ነበር፡፡ አንድ ተጠርጣሪ ራሱን ለማጥፋት የገፋፋውን ምክንያት እንዲህ ሲል አስረዳኝ፣

‹‹ምርመራው እጅግ ኢሰብዓዊ ነው፡፡ ራስህን ትጠላለህ፡፡ በቃ በግድ እመን ነው የሚሉት፡፡ ወንጀሉን ሳትፈጽም እዚህ ተጠርጥረህ ብትገባ በግድ ወንጀለኛ ነኝ በል ትባላለህ፡፡ ድብደባው ፋታ የለውም፡፡ በየዕለቱ ማታ ማታ እየወሰዱ ሶስተኛ ፎቅ ላይ ይቀጠቅጡሃል፡፡ ሰው አትመስላቸውም፡፡ በሀሰት የጠየቁህን አንድ ወንጀል ብታምንላቸው ሌላ ወንጀል ፈጥረው እመን ይሉሃል፡፡ በቃ መዝገቡ ክፍት ነው፤ አንተን ይጠብቃል እመን ይሉሃል፡፡ ከነገ ዛሬ ማሰቃየቱ ያበቃል ስትል ማብቂያ የለውም፡፡ ስለሆነም ከዚህ ሁሉ ስቃይ ለምን አልገላገልም ብለህ ታስባለህ፡፡ በዚህ ጊዜ ትዝ የሚልህ ደግሞ ራስን ማጥፋት ነው፡፡››

ይህ የብዙ ሰዎች አንደበት የተናገረው እውነታ ነው፡፡ ድርጊቱ በህግ ያልተፈቀደ ቢሆንም ምርመራው ግን በዚህ መልኩ እንደሚከናወን ብዙዎች አስረዱኝ፡፡ የኢፌዴሪ ህገ-መንግስት አንቀጽ 19 (5) ስለተያዙ ሰዎች እንዲህ ይላል፣ ‹‹የተያዙ ሰዎች በራሳቸው ላይ በማስረጃነት ሊቀርብ የሚችል የእምነት ቃል እንዲሰጡ ወይም ማናቸውንም ማስረጃ እንዲያምኑ አይገደዱም፡፡ በማስገደድ የተገኘ ማስረጃም ተቀባይነት አይኖረውም፡፡››

ሌላ ተጠርጣሪ በምርመራ ወቅት ያጋጠመውን ገጠመኝ የግዱን እየሳቀ አወጋኝ፡፡ ‹‹ለምርመራ በገባሁበት ክፍል ውስጥ መርማሪዎቼ በዱላ ተቀበሉኝ፡፡ ከጥያቄ በፊት ዱላ ይቀድማቸዋል፡፡ ደብድበው ደብድበው ሲደክማቸው እኔን እግሬን ከፍቼ እንድቆም በማዘዝ እነሱ ኮምፒተር ላይ ፊልም እያዩ መዝናናት ጀመሩ፡፡ ከሰዓታት በኋላ ሽንት ቤት እንዲወስዱኝ ለመንኳቸው፡፡ ተሳለቁብኝ፡፡ እየቆየሁ እየቆየሁ ስሄድ ሽንቴን መቆጣጠር እንዳልቻልኩ በመግለጽ ‹ስለወንድ ልጅ አምላክ› ስል በድጋሜ ተማጸንኳቸው፡፡ ሊሰሙኝ አልቻሉም፡፡ ከዚያ ‹በቃ እዚሁ እሸናለሁ› ብዬ ሽንቴን ለቀቅኩት፡፡ በጣም ታፍኜ ስለነበር ሽንቴ እጅግ መጥፎ ጠረን ፈጠረ፡፡ ይገርምሃል ለእኔ ሳይሆን ለቢሯቸው አዝነው እንደውሻ አባርረው ከቢሮ አስወጡኝ፡፡››

ለመሆኑ እነዚህን የስቃይ ድምጾች ሰሚያቸው ማን ይሆን?

የኢትዮጵያን ዲሞክራሲ ለመዉለድ ስንት ዘመን ይፈጃል? (ከ ቶፋ ቆርቾ)

$
0
0

ከ ቶፋ ቆርቾ

የምርጫ ወግ

electionምርጫ ደርሷል አይደል? ለዛ መሆን አለበት በአንድ በኩል EBC ‘ምርጫ ቦርድ ለምርጫ አስፈፃሚዎች ስልጠና ሰጠ … ኮሮጆ አሰራጨ’… ሌሎች መገናኛ ብዙሃን ደግሞ ‘ምናምን የሚባል ፓርቲ ሰልፍ ጠራ’ … ‘የነእከሌ ፓርቲ ትየንተ ህዝብ በፖሊስ ሃይል በሃል ተበተነ’ ….. ዱዱዱዳ…እንዲያም እንዲህም የሚሉ ወሬዎች መስማት ከመሰንበቻዉ የተለመደ ሆኗል፡፡

እኛ ሃገር ስለምርጫ አምስት ዓመት እየጠበቁ ማዉራት የተለመደ ተከታታይ ድራማ (series TV show) ይመስላል… የመጪዉ ግንቦት አምተኛዉ ምእራፍ (Season 5) መሆኑ ነዉ ማለት ነዉ? ቂቂቂቂ….! እኔ የምለዉ ግን ለይመሰል ብቻ ምርጫ ማድረግ ምን ይጠቅማል? መጨረሻዉን ቀድመዉ ያወቁትን ፊልም ማየት ወይ ‘ልብ አንጠልጣይ’ የተባለ ልብ ወለድ መፃፍ ማንበብ ጊዜ ማሳለፊያ አልያም የደራሲዉን ችሎታ ለመገምገም ካለሆነ በቀር ምኑ ይነሽጣል? እሺ አንድ ሁለቴ እያወቁ መሸወድ ያለ ነዉና ምን አይደል እንበል…. አመስቴ ስሆንስ? አራዶቹ  ቢሰሙ ‘አይከይፈፍም’ ይሉናል ከምር ኩሸት ይሆናል! ልጆች ሆነን ‘ክስክስ’ የምንለዉ አይነት አክሽን ፊልም ስናይ ‘አክተሩ’ አይሞትም ምናመን ብለንና አምነን አሳምነን ፊል ማየት እንጀምራለን እዉነትም ፊልሙ ሲገባደድ አክተሩ ጠላቶቹን ያሸንፋል በቃ አይሞትም…. የኛም ሃገር ምርጫም ልክ እንደዛዉ ነዉ….. መሪ ተዋናዩ የማይሸነፍበት አክሽን ፊልም! ልየነቱ በሚሊዮነች የሚቆጠሩ መሪ እና አጃቢ ተዋንያን የሚሳተፉበት መሆኑና ለወራት የሚወራለት መሆኑ ብቻ ነዉ! የሆነዉ ሆኖ አሸናፊዉና አጃቢዎቹ ቀድሞ ዉጤቱ የታወቀበትን ምርጫ የሚባል ድራማ መሰል ነገር ማካሄድ ለምን አስፈለጋቸዉ? ቃለ ተዉኔቱን… ዝግጅቱን… ቀረፃዉን…. ዳኝነቱን አንድ አካል ብቻዉን በተቆጣጠረበት ቲያትር ዉስጥ መግባት የሚያስገኘዉ ትርፍ ይኖረዉ ይሆን? ይመሰለኛል አለዉ…. ባይሆን ኖሮ አጃቢዎቹ ስለምን ይሄን ያህል መፈራገጥ ያስፈለጋቸዉ ነበር? ብዬ እጠይቀለሁ… በርግጥ መልሱን እነሱ ያዉቁታል!  የትወና ብቃትን ለማሳደግ ብቻ የሚያደረጉት ከሆነም ከልብ ያስገርማል …. ይቺ ይቺ በጣም አደገኛ ‘አድቬንቼር’ ነች!  የምሬን ነዉ ያለገባኝ ነገር እንዳለ አላዉቅም ግን ደግሞ እንደዉ አጉል ጉንጭ ከማልፋት… ሰዉም ከማስቸገር ምርጫ የምንለዉ ጉዳይ እዉነተኛ የፉክክር መድረክ እስኪሆን ተወት ብናደርገዉስ? ባይሆን መሰራት ያለባቸዉን መሰረታዊ ጉዳዮችን በርትተን እንስራ….፡፡

የዲሞክራሲ ሂደት?

የሆነዉ ሆነና እቺ ዲሞክራሲ የሚሏት “ዛር” ኢትዮጵያ ዉስጥ ምች ሆን ሞልቶላት የምትቆመዉ? ብትለመን ብትለምን አልወርድ አለች አይደል? ለነገሩ ብቅ ስትል ገና አስደንብረዉ እያባረሯት በየት በኩል ትምጣ? ይልቅዬ ‘ዲሞከራሲዊነት ሂደት ነዉ’ የሚባለዉ ተረት ተረት አብሮን ሊያረጅ ነዉ አይደል? ከምር 10 ዓመት ሆነዉ እኮ….! እናማ መቶ አመት እስኪሞላዉ ልንጠብቅ ነዉ ማለት ነዉ?

በነገራችን ላይ የዚህ ‘ሂደት ነዉ’ የሚሉት ማሳበቢያን ፅንሰ-ሃሳብ ከየት ይሆን ያገኟት ብዬ ሳስብ ድንገት እንግሊዝያዊዉ የኢኮኖሚክስ ሊቅ አዳም ስሚዝ ‘The Wealth of Nations’ የሚለዉ መፃሃፉ ዉስጥ ቶሸንቅሮት ኖሮ አገኘሁትና ‘እነኚ እንግሊዞች ተኮለኞች ናቸዉ….’ የሚሉት ስንኝ ወዲያዉ ትዉስ አለኝ፡፡ ለነገሩ ስሚዝ ስለዲሞክራሲ አስቦ የተናገረዉ ሳይሆን ስለእድገት ሲያወራ ያነሳዉ ሃሳብ ነዉ፡፡ እንደ ሰዉየዉ አባባል የሃገራት የኢኮኖሚ እድገት ተፈጥሮላዊ ሂደቱን ጠብቆ የሚመጣ ዝግመታዊ ለዉጥ (the natural progress of opulence) የሚለዉ አይነት ነዉ፡፡ እንዲህ ማለት ደግሞ ዛሬ የበለፀጉት ሃገራት የደረሱበት የእድገት ደረጃ ላይ ለመድረስ ዕዉደቱ ይተበቅ ከተባለ ለታዳጊ ሃገራት ከመቶ አመት በላይ ሊፈጅ ነዉ፡፡ ሃሳቡን ብዙ ሙሁራን ፉርሽ ያደረጉት ጉዳይ ቢሆንም እኛ ቤት ሲመጣ ታዲያ ዲሞክራሲዊ ለዉጥ በሂደት የሚገኝ ነዉ ከሚባለዉ ማስመሰያ ጋር መሳ ለመሳ የሆነ ይመስላል፡፡ ለምን ቢባል ይሄዉ ሃያ አራት አመታትን አስቆጠርን ያየነዉ መሻሻል የለም … እናም መቶዋን ልነደፍን ነዉ ማለት ነዉ?

ነገሩማ የሚመስለዉ ወደኋላ መመለስ የጀመርን እንጂ ወደፊት መንቀሳቀሱ ሲያምራችሁ ይቀር የተባልን ነዉ፡፡ ወደ ኋላ መንሸራተት እንደ ሃገርና እንደ ስርዓት ትልቅ ኪሳራ ነዉ… ‘የዲሞክራሲ ውርጃ’ አይነት ነገርም ይመስላል፡፡ …. ከምር እንዴት ቁልቁል እንወርዳለን? እዚህ ላይ ፖላንዳዊዉ የምጣኔ ሃብት ሙሁሩ ፖል የተናገረዉን መጥቀስ የተገባ የሆናል…. ‘ሰዉ ከሆንን ምን እንደ ዉሻ ወደ ትፋታችን ይመልሰናል ይልቁንስ የተሻለ ሁኔታን እንፈጥራለን እነጂ’… ያላትን አይነት ሽንቆጣዉን ያስታዉሷል (if we were to emerge alive, we should not return to previous status quo but … form a better world)….. እናማ በዚህ ሁኔታ ከቀጠልን ተስፋችን ምን ይሆን? ይሄ መከረኛ ትወልድ ያሰበዉን ሳይናገር… የፈቀደዉን ሳይመርጥ… አቛሙን እዳሻዉ ሳይገልፅ ዘመናትን ጠብቆ ያሰበዉ ሳይሳካ ሊያለፍ መሆኑ አሳዛኝ ነዉ፡፡

‘እና ምን ይሁን?’ የሚሉ ጠያቂዎች አይጠፉምና ለማለት የተፈለገዉን ማስረዳት ይገባል፡፡ ጉዳዩ እንግዲህ ኢንዲህ ነዉ….. ዲሞክራሲያዊ ሂደቱን የጠበቀ ለዉጥ ለማየት የግድ ዘመናትን በናፍቆት መጠበቅ የለብንም…. ሂደት ነዉ እያሉ መቀለዱን አቁመን ዛሬዉኑ መደረግ ያለበትን ማደረግ የሁሉም ወገን ሃለፊነት መሆኑን መገንዘብ ይገባል፡፡ምርጫ ማካሄድ በራሱ ግብ አይደለም! ይልቁን ዲሞክራሲያዊ ስርዓትን ለመገንባት ከሚጠበቁ  ግብዐቶች መካከል አንዱ ብቻ ነዉ:: ኢትዮጵያ ዉስጥ ለዲሞክራሲያዊ ስርዓትን እንገነባለን የሚባለዉ ለተፈላጊዉ ስርዓት መታጣት ተግዳሮት የሆኑ ነገሮችን ምንነትን ከስር መሰረቱ አጥርቶ ሳይለዩ ከላይ ከላይ በመጋለብ ነዉ:: ዋናዉን የስርዓቱን በሽታ መርምሮ ከለዩ በኌላ መፍትሄ ከመፈለግ ይልቅ የተያዘዉ ምልክቶችን ማስታመምና ግባዐቶች ላይ መረባረብ ነዉ:: እንደ ሚታወቀዉ ሃገሪቱ ሊፈቱ የማይችሉ የሚመስሉ ቅራኔ ዉስጥ ሰምጣ ገብታለች…. ታፍና ከመሞቷ በፊት የነፍስ አድን ስራዎች መሰራት አለባቸዉ፡፡

መድሃኒቱ

ቀዳሚዉና ዋንኛዉ ጉዳይ፡- ለታሪክ ቅራኒዎቻችን መፍትሄ ማበጀቱ ነዉ፡፡ በአንድ ወቅት… በወዲኛዉ ዘመን በበርካታ ቤሔርና ቤሔረሰቦች ላይ የደረሰ በደል አለ ይባላል፡፡ ይህም የመታገያ አጀንዳ ከሆነ ከአራት አስርት ዓመታት አለፉ:: እርግጥ ነዉ ኢትዮጲያ ዉስጥ የሚኖሩ ህዝቦች ሁሉ እከሌ ከከሌ ሰይባል በጭቆና ዉስጥ ነበሩ… (ምናልባት ዛሬም ያ ሁኔታ የተለወጠ አይመስልም)፡፡ እናም በተለየ መንግድ የበደል ገፈት ቀማሽ የነበሩ ቤሔሮች፣ ቛንቛ ተናጋሪዎችና የእምነት ተከታዮች ነበሩ፡፡ የዝሆን ጆሮ ይሰጠኝ አልሰማሁም ወይም አይኔን ግንባር ያደርገዉ አላየሁም ብሎ ሽምጥጥ አድርጎ ለመካድ ካልሆነ በቀር ታሪክ የመዘገባቸዉ እዉነታዎች አሉ::  በሚኖሩበት ስፍራና ቀየ ስንክሳር ያዩ… በማንነታቸዉ እንዲያፍሩና እንዲሸማቀቁ ተደርገዉ የነበሩ የህበረተሰብ አካላት ነበሩ ምናልባተም ዛሬም ቅርፁን ይለወጥ እንጂ በዚህ ሁኔታ ዉስጥ የሚያለፉ ህዝቦች አሉ፡፡ በሌለላ አነጋገር የአማራና የትግራይ ተወላጅ ያለሆኑ እንዲሁም የኦርቶዶክስ ክርስትና ተከታይ ያልነበሩ ህዝቦች ላይ በተለየ መልኩ የደረሰ በደልና ስቃይ ነበር፡፡ የአፄ ሚንሊክ የግዛት ማስፋፋትና ትልቛን ኢትዮጲያን በመፍጠር ሂደት ዉስጥ የፈጠረዉ ጠባሳ ያለተፈቀ ሃቅ ነዉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ይህ ሁኔታ ሆን ተብሎ በተፈጠረ የማጋጋያና የማጋነኛ የፈጠራ ንግርቶች ታጅቦ በህዝቦች ማካከል በጋህድ የሚታይ ቅራኔን ፈጥሯል፡፡ በዉጤቱም ግልፅ የሆኑ መናናቆችና መጠላለፎች በሁሉም የሀገሪቱ ክፍሎች በአሁኑ ወቅት እየታዩ ነዉ፡፡ ዛሬ በርካታ አስደንጋጭ  ሁነቶች እየተሰተዋሉ ነዉ …. በፊዉዳሉ ዘመን ለጋብቻ አጥንት ይቆጠር እንደነበረዉ ሁሉ በኛም ዘመን ለሁለት ጥንዶች መጋባት መፈላለጋቸዉና ማፋቀራቸዉ ብቻ በቂ አልሆነም ዘርን ማስተካከልም ተቀዳሚ ጉዳይ ሆኗል ፡፡ ይሄ ደግሞ በከተሞች ጭምር የሚያጋጥም ጉዳይ ነዉ፡፡ በግለሰቦች ደረጃ ያለዉን ማንሳቱ በህዝቦች ማካከል የቱን ያህል ስር የሰደደ የመጠፋፋትና የበቀል ስሜት እያደገ እንደሆነ የሚያመላክት አይነተኛ ሁነት በመሆኑ ነዉ፡፡ ቁምነገሩ ይህን እያወራን እና እያራገብን እስከ መቼ እንዘልቃለን የሚለዉ ነዉ፡፡ እዉነተኛዉ አደጋ አይኑን አፍጥጦና ጥርሱን አግጦ እኪመጣ ከዚያም እኪያጠፋን እተጠባበቅን ያለን ነዉ የምንመስለዉ፡፡ አሳዛኙ ጉዳይ ታድያ ይህ ሁሉ ዐደጋ በዚህና በመጪዉ ትዉልድ ላይ የተደቀነዉ ትዉልዱ በግል ላልፈፀመዉና ላልደረሰበት በደል ነገር ግን ያለፈዉ ትዉልድ ያወረሰዉ ስንክሳር መሆኑ ነዉ፡፡ የዚህን ማለቂያ የሌለዉን የመካሰስ ወጥመድ ሰብሮ መዉጣት የሁሉም ወገን ሃላፊነት መሆን ይኖርበታል:: ለዚህ ደግሞ  ድፍረት ይጠይቃል… እዉነተኛ እርቅና የወገናዊነትን መንፈስ ለመፍጠር ከበዳይም ከተበዳይም ወገን ተወላጅ የሆንን ሁሉ ደፍረን ልንቀበለዉ ጨክነን ልንጋተዉ የሚገባ እዉነታ አለ፡፡

ተወደደም ተጠላ በአንድ ሃገርና አከባቢ እንድንኖር ተፈጠሮ ግድ ብላናለች…ምንም ባንፈላለግ እንኴን ልንነጣጠል አንችልም… ይህ ቀዳሚዉ ሃቅ ነዉ፡፡ ሌላኛዉ ትላነት ለደረሰዉ ጥፋትና በደል የዚህ ትዉልድ ሰዎች ቀጥተኛ ተሰታፊዎች አይደለንም፡፡ ይሄን ታሳቢ አድርግን ቀጣዩን እርምጃ መዉሰድ ተገቢ ይሆናል:: ስለሆነም ለዚህ የዉርስ ፀብ መፍትሔ ማበጀት አለብን፡፡ ሃቁ ይህ ነዉ… አፄ ሚኒሊክና ጦራቸዉ አደዋ ላይ ወራሪዉን ጠላትን አሳፈሮ በመመለስ በሰሩት ገድል የኢትዮጲያ ብቻ ሳይሆኑ የጥቁር ህዝቦች ሁሉ ጀግና እደነበሩት ሁሉ በሌላዉ ገፅታቸዉ ደግሞ ግዛት ለመስፋፋት በደረጉት ዘመቻና በተከቱሉት ፖሊሲ ኢሰባዉነት የተሞሉ ጨፍጫፊ ነበሩ፡፡ በተለይ በአርሲ፣ በባሌ፣ በሐረር፣ በቦረና፣ በወላይታ፣ በከፋና በሌሎችም አከባቢዎች የደረሱ ዘግናኝ ጥፋቶች የማይረሱ የሃያኛዉ ክፍለ-ዘመን የታሪካችን መጥፎ ገፅታ አንዱ አካል ነዉ፡፡ ለዚህ ጥፋት የኦሮሞ ህዝብ እና ሌሎችም ቤሔሮች ብቻ የሚቆጩበት… የአማራ ህዝቦች ብቻ ለዘመናት የሚወቀሱበት ጉዳይ ሊያቆም ይገበዋል፡፡ የድርጊቱ ፈፃማዎች በዚያ ዘመን የነበሩ የስርዓቱ ጠበቂዎች ሲሆኑ በደሉ የደረሰዉ ግን በሁሉም ኢትዮጵያዉያን ላይ እንደሆነ ሊታሰብ ይገባዋል፡፡ ስለሆነም ሚኒሊክ መወገዝ ካለባቸዉ በጋራ እናዉግዝ … ለችግሩ ሰለባ ለሆኑ ሰዎች መታሰቢያ ማድረግ ካለብን በጋራ ስንዘክራቸዉ እንኑር…! ይህን ጉዳይ መቛጨት የሚቻለዉ ሃያት ቅደመ ሃያቶችህ በድለዋል የሚባሉት የአማራ ተወላጆች ሃያት ቅድመ ሃያቶቻችን መከራን ተቀብለዋል ለሚሉ ለሌሎቹ ቢሔሮች ሃዘናችሁ ሃዘናችን ነዉ … ያለፈዉ ትዉልድ ስራ ተገቢ አይደለም ብሎ በደፈናዉ ይቅር በመባባል ብቻ ከሆነ ማድረግ ነዉ፡፡ ተበድለናል የሚሉ ወገኖችም ይቅር ለማለት ዝግጁ መሆን ይኖርባቸዋል:: ይሄ ጉዳይ መፍትሄ ሳይበጅለት ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እንገነባለን ብሎ መነሳቱ አለያም ለዉጥ እናመጣለን ማለት የህልም እሩጫ ከመሆን አያልፍም::

ሁለተኛዉ ጉዳይ፡- ከመጀመርያዉ ሃሳብ ጋር የተያያዘና ተቀዋሚ ነን ብለዉ የቆሙ ሃይሎችን ይመለከታል:: ከትዉልድ ትዉልድ የተሸጋገረዉ ተቃርኖ መፍትሄ ሊበጀለት ባለመቻሉና ተያያዥ በሆኑ ጉዳዮች ላይ መስማማት ባለመፈለግ አንድ ኢህዲግን ለመገዳደር ዘጠና ምናምን ፓርቲዎች ተፈጥረዋል:: ብዙዎች ስለምን በሃገር ዉስጥም ሆነ በዉጭ ያሉ የፖለቲካ ሃይሎች የጋራ ተቀናቃኝ የሚሉትን ሃይልን ለመታገል ሲሉ መስማማት እንኳን ይሳናቸዋል የሚለዉ ጥያቄ መልስ የሚያጡበት ጉዳይ ነዉ:: መልሱ ግን ቀላል ግልጽ ነዉ::አንደኛዉ ያለፈዉ ታሪካዊ ተቃርኖ የጋራ ግብ እንዳይኖራቸዉ አድርጔቸዋል…. የጋራ ግብ ቢኖራቸዉ እንኳን ተቀራርበዉ ለመወያየትና ከልብ የሆነ ጥምረትም ይበሉት ጅኒ ቁልቋል ለመፍጠር አልተቻላቸዉም:: ትልቁ የሙግት መከፈቻና የስጋት ምንጭ ሊሆን የሚችለውም እነዚህ ገዢዉን ግንባር እንቃወማለን የሚሉ ሃይሎች እርስ በርስ መቀዋወማቸዉ ብቻ ሳይሆን በጠላትነት ስሜት መተያየታቸዉ ጭምር ነዉ::ስለተመሳሳይ ጉዳይ በተለያየ መድረክ በተመሳሳይ ቌንቌ እየተናገሩ በህብረት ግን መስራት ሲሳናቸዉ ሲታይ የሚገርም ትይንት የሚሆነዉ ያኔ ነዉ::  ሌላኛዉ ጉዳይ ስለመጪ ጊዜ ያላቸዉ አተያይ ጉራማይሌ መሆኑ ነዉ:: አይበለዉና ይህ የከፋዉና የመረረዉ ህዝቡ ነግ በግብታዊነት ተነስቶ ለዉጥ እንፈልጋለን ብሎ በሌሎች ሃገራት እንደታየዉ ስልጣን ላይ ያለዉን ሃይል ቢያባርረዉ ተቃዋሚ ነን የሚሉት ሃገሪቷን በየትኛዉ ፍኖተ ካርታና ፕሮግራም ሊመሯት ይሆን? ይህን የመሰለለዉን ተቃርኖ መፍታት ሳይቻላቸዉ በሰላማዊዉ መድረክም ሆነ በሌላ ዘዴ የስርዓት ለዉጥ እናመጣለን ብለዉ የተነሱ ሃይሎች ሃገሪቱን እና ህዝቡን ወደሌላኛዉ አዙሪት ዉስጥ ያስገቧታል የሚለዉ ስጋትን የምንጋራ ጥቂቶች አይደለንም:: ዋናዉ ጉዳይ ተቃዋሚዎች ላለመስማማት የተስማሙበትን ባህል ቀይረዉ መቀራረብና በጋራ መስራት ካልተቻላቸዉ  ስልጣንን እደንደተመኛት ሳይወርሷት እኛም ዲማክራሲን እንደናፈቅናት ሳናገኛት በምድረ በዳ መቅረታችን የምር ይመስላል::

ሦወስተኛዉ ጉዳይ ከላይ ከተጠቀሱት አበይት ሃሳቦች ጋር በቀጥታ የሚያያዝና መዳረሻ ሊሆን የሚገባዉ ነዉ::ይሄዉም ለዘመናት የተቆለሉ ፖለቲካዊ ቅራኔዎችን በሰከነና በሰለጠነ መንግድ መፍትሄ እዲያገኙ የማደረግ ሂደት ነዉ፡፡ በሌላ አነጋገር ከመቸዉም ጊዜ በበለጠ ስለ ቤሔራዊ እርቅና ስለ ሃገራዊ መግባባት መሰራቱ የተሸለ መሆኑን መረዳት የተገባ ነዉ፡፡ በርግጥ ይህን ሃሳብ ብዙዎች ያዝ ለቀቅ ሲያደርጉት ይስተዋላል፡፡ የሆነዉ ሆኖ ሁሉም መንታ ልብ መሳይ ናቸዉ፡፡ ለምን ቢባል ሲገፉበት አይታይም…. ዛሬ ስለ እርቅ በተናገሩበት አንደበት ነገ ሲያወግዙና ሲፈርጁ ይታያሉ፡፡ እረቀ ሰላምን ለማስፈን ቀዳሚዉ ጉዳይ እዉቅና መስጠትና መከባበር ነዉ፡፡ እዉቅና መስጠት እዉነታን ከመቀበል ይጀምራል፡፡ያለፈን ታሪክ ተቀብለን መፍትሄ እንደምንሻለት ሁሉ የዛሬዉንም ነባራዊ ሁኔታ በቅጡ መረዳት የተገባ ይሆናል:: ተወደደም ተጠላም ባለንበት ዘምንም ሆነ በመጪዎቹ አመታት አሁን ስልጣን ላይ ያለዉ ሃይል ባሻዉና በፈቀደዉ ምንገድ ሃገሪቱን እየመራ የመቀጠሉ ነገር  እዉን ይመስላል፡፡ ይህን ሃይል ያገለለ የእርቅ ሃሳብም ሆነ ሌላ አይነት እንቅስቃሴ መድረሻዉ የትም ነዉ፡፡ ስለሆነም ለማዉገዝና ለማጥላለት የሚያስንፈዉ ሃሳበችን ስልጣን ላይ ያለዉን ሃይል እንደ መንግሰት ተቀብሎ ያስገኛቸዉን ዉስን ነገር ግን ነባራዊና አዉንታዊ ለዉጦች ወይም እድገቶች አክብሮ እዉቅና መስጠት ተቀዳሚዉ እርምጃ ሊሆን ይገባዋል፡፡ የዚህ አይነቱ አቀራረብ ተንበረካኪ.. ተለጣፊ… ሌላለም ሌላም ነገሮችን ሊያስብል እንደሚችል ይገመታል፡፡ ይሁን እንጂ እዉነት ስለሆነ በዚህ መንገድ መጔዙ ግድ ይለናል፡፡ ፈረንጆቹ walk the talk እንደሚሉት የምናወራዉን ልንተገብረዉ ይገባል፡፡ እዚህ ላይ ለማለት የተፈለገዉ ጠላትነትን ብቻ ግብ ያደረገ ዘለቄታ የሌለዉ አካሄድ ስለሚሆን መደረግ ያለበትን ሁሉ አድርጎ እርቅና ድርድር ለመፍጠር የሚቻለባትን በር ክፍት አርጎ ቢያንስ መጠባበቁ የተገባ ነዉ::

እንደ መዉጫ

ከላይ የተዘረዘሩት ቅድመ ሁኔታዎች ባልተሟሉበት ሁኔታ ዲሞክራሲ … መብት… ለዉጥ …ትግል ቢባል እመኑኝ የትም አንደርስም፡፡ ቢሞከር እንኴን ከዚህ ቀደም እደታዩት የታሪክ አጋጣሚዎች ታጥቦ ጭቃ ከመሆን ፈቅ እንደማንል ለመተንበይ ነብይ ሞን አያሻም፡፡ ስልጣን ላይ ያለዉ ሃይል በታዓምር ዲሞክራያዊ ሊሆን እንደማይፈልግ እየታወቀ… ሰልፍ ቢወጣ… ባምርጫ ላይ ምርጫ ቢደረደር እንደዉ አጉል መፈራገጥ ለመላላጥ የሚሉት አይነት ካልሆነ በቀር ጠብ የሚል ነገር ይኖራል ማልት ቂልነት ከመሆን የሚያለፍ ነገር የለዉም፡፡ ዲሞክራሲያዊነት ደግሞ ለድርድር መቅረብ የለለበት የለዉጥ መንገድ መሆን ይኖርበታል፡፡ ሌላ ዙር ጦርነትና ወይም ሌላ ምዕራፍ አብዮት ለሃገሪቱም ሆነ ለህዝቡ የሚበጅ አይሆንም፡፡ ስለሆነም የምንፈልገዉን አይነት ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እዉን ለማድረግ የሚቻለዉ የዘመናት የታሪክ ቅራኔዎችን በቅንነት አይቶ መፍትሄ እንዲያገኙ በማድረግ፣ ተቃዋሚዎች እርስ በእርስ ከመቀዋወም ሲዎጡና በመሰረታዊ ጉዳዮች ላይ ተግባብተዉ ለለዉጥ አብረዉ መስራት ሲችሉ ነዉ::የነኝህ ሁለት መሰራታዊ ጉዳዮች እዉን መሆን ወደ ሶስተኛዉ ግብ የሚያንደረድረን ይሆናል:: ይኄዉም ከገዢዉ ሃይል ጋር ለመደራደርና መገባባት ላይ ለመድረስ የሚያስችል አቅም የሚፈጥር ሁነኛ መንገድ ተደርጎ ሊወሰድ ይቻላል:: ያኔ ሁሉንም ወገን ያሳተፈ ስርዓት መመስረት ሲቻል የምንፈልገዉ የሰዎች መብት መከበር፣ ሰላም፣ እኩልነት፣ ነፃነት፣ እድገት ብልፅግና በምንወዳት ሃገራችን እዉን ማድረግ እንችላለን:: ይሁንና ይህን ህልም የሚመስል ምኞት እዉን ለማድረግ ስንት ዘመን ይፈጅብን ይሆን? ተምኔቱን ተጨባጭ ማደረግ የሁሉም ዜጎች ሃላፊነት ሊወሆን ይገበዋል፡፡

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

 

 

 

‹‹ከዓለም የቦንድ ገበያ እንድንበደር የተፈቀደልን እስከ ሁለት ቢሊዮን ዶላር ነው›› ሚኒስትር ሱፍያን አህመድ

$
0
0

ረፖርተር

የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትሩ አቶ ሱፍያን አህመድ፣ ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፍ የቦንድ ገበያው አንድ ቢሊዮን ዶላር ብድር ማግኘቷን፣ ፓርላማው ደግሞ እስከ ሁለት ቢሊዮን ዶላር የቦንድ ገበያ ብድር እንደፈቀደ አስታወቁ፡፡

ሚኒስትሩ ማክሰኞ ዕለት በጽሕፈት ቤታቸው በሰጡት መግለጫ በቦንድ ሽያጩ በ6.625 በመቶ ወለድ ክፍያ አንድ ቢሊዮን ዶላር መገኘት መቻሉን አብራርተዋል፡፡

TPLF Police Found Millions of Birr, Dollars and Euros in Ato Gebrewahid Wolde Giorgis Houseሶቨሪን ቦንዱን ለመሸጥ በሚኒስትሩ የተመራው ቡድን እ.ኤ.አ. ዲሴምበር 5 ቀን 2014 ሽያጩን በአሜሪካ ያጠናቀቀ ሲሆን፣ ከአንድ ቢሊዮን ዶላር ውስጥ 70 በመቶውን የገዙት በአሜሪካ የሚገኙ ኢንቨስተሮች ናቸው፡፡ የተቀረውን 30 በመቶ ደግሞ በአውሮፓ የሚገኙ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡ በመጀመርያ ለመሸጥ ታስቦ የነበረው ሁለት ቢሊዮን ዶላር መሆኑንና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም እስከ ሁለት ቢሊዮን ዶላር የሶቨሪን ቦንድ ሽያጭ ማፅደቁን ገልጸዋል፡፡

ይህ ማለት ግን መንግሥት በቦንድ ሽያጩ አማካይነት በየጊዜው ይበደራል ማለት አለመሆኑንና አስፈላጊ ሲሆን ብቻ ሽያጩን በድጋሚ በማከናወን ብድር ማግኘት እንደሚቻል አብራርተዋል፡፡

የተገኘው አንድ ቢሊዮን ዶላር ለኢንዱስትሪ ዞኖች ግንባታ፣ ለኃይል ማስተላለፊያ መስመሮች ዝርጋታና ለተወሰኑ የስኳር ፋብሪካዎች ግንባታ እንደሚውል ገልጸዋል፡፡ ‹‹የተገኘው ብድር በጭራሽ ለህዳሴው ግድብ አይውልም፡፡ የህዳሴ ግድብ በኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝብ ብቻ ያለማንም ጣልቃ ገብነት የሚገነባ ነው ብሎ መንግሥት አቅጣጫ አስቀምጧል፤›› ብለዋል፡፡

የተገኘው ብድር የሚኖረውን አንድምታ በተመለከተ በሰጡት አስተያየት የውጭ ኢንቨስተሮች ወደ ኢትዮጵያ እንዲገቡ ከማበረታታቱም በላይ፣ የኢትዮጵያን ገጽታ በመቀየር ረገድ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል፡፡

‹‹ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ዕድገት ሊተቹ ይችላሉ፡፡ ቦንዱን የገዙት ኢንቨስተሮች ግን የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ዕድገት በገንዘባቸው ነው የመሰከሩት፤›› ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት ብድሩን ላይከፍል ይችላል በሚል ከተቀመጡት ሥጋቶች መካከል ከኤርትራ ጋር ጦርነት እንደሚከሰት፣ ድርቅ ኢኮኖሚውን ሊያስተጓጉል እንደሚችል፣ በ2007 ዓ.ም የሚደረገው አገር አቀፍ ምርጫ ገዢው ፓርቲ ተሸንፎ የፖሊሲ ለውጥ ሊኖር ይችላል የሚሉና የመሳሰሉት ናቸው ያሉት ሚኒስትሩ፣ የሁሉም የሥጋት ዓይነቶች ደረጃ ግን ዜሮ ስለሆነ በእዚህም ምክንያት ብድሩ ሊገኝ እንደቻለ አብራርተዋል፡፡

አቶ ሽመልስ ከማል ከአቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር በመጋጨታቸው አኩርፈው ቤት መቀመጣቸው ተሰማ

$
0
0

የመንግስት ኮምኒኬሽን ጽ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ የሆኑት አቶ ሽመልስ ከማል ከ ሚኒስትሩ ሬድዋን ሁሴን ጋር መግባባት ባለመቻላቸው አኩርፈው ቤት በመቀመጥ መደበኛ ሥራቸውን እያከናወኑ አለመሆኑን ምንጮች ገልጸዋል።

አቶ ሽመልስ ከደባል ሱስ ጋር በተያያዘ በመደበኛ የስራ ሰዓታቸው ሊገኙ ባለመቻላቸው ሚኒስትሩ ይህን ባህሪያቸውን እንዲያስተካክሉ ቢነግሩዋቸውም ሊያስተካክሉ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው የተፈጠረ መሆኑን ምንጮች ይገልጻሉ።
shimelis kemal
የአቶ ሽመልስን ሃላፊነት ደርበው እየሰሩ ያሉት በቅርቡ ከዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን ዳይሬክተርነት ተነስተው የመንግስት ኮምኒኬሽን ሚኒስትር ዴኤታ በመሆን የተሾሙት አቶ እውነቱ ብላታ ናቸው።

አቶ ሽመልስ በቅርቡ የታዩት የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት የቦርድ ሊቀመንበር በመሆናቸው በድርጅቱ ስብሰባ ላይ ብቻ ነው፡፡ የፕሬስ ድርጅት ስራ አስኪያጅ አቶ ሰብስቤ ከበደ ከአቅም ማነስና የመልካም አስተዳደር ችግር ጋር ተያይዞ በድርጅቱ ጋዜጠኞች እየቀረበባቸው ያለውን ግልጽ ትችትና ቅሬታ በተደጋጋሚ ስብሰባዎች ላይ በመገኘት ከማስተባበላቸውም በተጨማሪ ጥያቄውን የሚያነሱ ጋዜጠኞችን እስከማስፈራራት የደረሰ ንግግር ሲያደርጉ የተሰሙት አቶ ሽመልስ፣ መደበኛ ስራቸውን መተዋቸው በኮምኒኬሽን መ/ቤቱ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖአል፡፡

አቶ ሽመልስ ከማል በአቶ በረከት ስምኦን ደጋፊነት የብሮድካስት ባለስልጣን ዋና ስራአኪያጅ የነበሩ ሲሆን፣ የ97 ምርጫን ተከትሎ የቅንጅት አመራሮችና ጋዜጠኞች በተከሰሱ ወቅት አቃቤ ሕግን ወክለው ሐሰተኛ መረጃዎች እንዲቀርቡና ሐሰተኛ ምስክሮችን በገንዘብ በመግዛትና በመደለል ለኢህአዴግ ውለታ ለመስራት የጣሩ ሰው መሆናቸው ይታወቃል፡፡

ይሁን እንጅ አቶ በረከት ከጤና ጋር በተያያዘ ስራቸውን እየተዉ በመምጣታቸው አቶ ሽመልስ ብቸኛው ደጋፊያቸውን አጥተዋል። አቶ ሽመልስ አቶ በረከትን የመተካት ህልም ቢኖራቸውም ሳይሳካላቸው አቶ ሬድዋን ቦታውን እንዲወስዱ ተደርጓል። በሁለቱ ባለስልጣኖች መካከል ባለው ልዩነት የተነሳ፣ አቶ ሽመልስ ከስራቸው የሚባረሩበት ቀን እሩቅ ላይሆን እንደሚችል ወይም በገዛ ፈቃዳቸው ስራቸውን በመልቀቅ ከአገር ለመውጣት ሙከራ ሊያደርጉ እንደሚችሉ ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ ታዛቢዎች ይገልጻሉ። የአቶ ሽመልስ የስልጣን ቆይታ በከፍተኛ ህመም ከሚሰቃዩት ከአቶ በረከት ስምኦን ህልውና ጋር የተያያዘ መሆኑን ታዛቢዎች ይናገራሉ።

Source: ኢሳት ዜና

Health: 5 ቁምነገሮች ስለ ነስር – Epistaxis

$
0
0

ማንነቱ
የህክምና ሰዎች ኤፒስታክሲስ (Epistaxis) እያሉ የሚጠሩትን የሀገራችን ሰዎች ደግሞ ነስር ይሉታል፡፡ ቋንቋ ቢያለያያቸውም የምስጢር ጽንሳቸው ከአንድ ማህፀን የተገኘ ነው፡፡ ስለዚህ ነስር የሚለውን ቃል ስንፈታው ምንጩ አፍንጫን መሰረት ያደረገ ድንገተኛ መድማት ነው፡፡ ጥናቶች እንደሚያትቱት በህይወት ዘመናቸው ከ10 ሰዎች መካከል ስድስቱ ነስር አጋጥሟቸው ያውቃል ወይም ያጋጥማቸዋል፡፡ እንኳንም ይሄ ቁጥር ለካንሰር ወይም ለሌሎች በሽታዎች አልሆነ፡፡ መቼም ሳይደግስ አይጣላምና ይህ ቁጥር ለነስር ሆነ፡፡ ይህ ማለት ይህን ያህል ጊዜ ነሰረኝ ተብሎ የሚይዙትን የሚጨብጡትን የሚያጡበት ምክንያት የለም፡፡ ቢሆንም ግን በነስር ላይ ያለንን ግንዛቤ ከፍ በማድረግ እንዲሁም የተሳሳተ አመለካከት ካለ ወደኋላ ትተን የሚረባንን ነገር ይዘን ወደፊት መሄድ የምንችልበትን አቅም ማጎናፀፍ የፅሑፍ ቀዳሚ አላማ ይሆናል፡፡

Epistaxis

መንስዬዎቹ
የነስር ምክንያቶች ለማስረዳት አንድ ምሳሌ ልስጥ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ አፍንጫን በመንደር፤ ሙሉ አካላችንን ደግሞ በሀገር እንመስለው፡፡ ስለዚህ የነስር ምክንያቶች መንደራዊና ሀገራዊ ችግሮች ተብለው በሁለት አበይት ክፍሎች ልንመድባቸው እችላለን፡፡ እንግዲህ መንደራዊ ችግሮች ስል እዛው አፍንጫ አካባቢ የሚርመሰመሱትን ተግዳሮቶችን ሲያመላክት፤ ሀገራዊ ችግሮች ያልኩት በሌላ በኩል ጠቅላላ ሰውነታችን ላይ ተፅዕኖ በማሳደር ነስርን ከምልክቶቻቸው እንደ አንዱ አድርገው ያቀፉትን በሽታዎች ወይም የሰውነት ቀውሶችን ነው፡፡

መንደራዊ ችግሮች (Local Causes)
1. አፍንጫ ላይ የሚደርሱ ጉዳቶች
– አፍንጫን በጥፍር አብዝቶ መጎርጎር
– ባዕድ አካላት (በተለይ ያገኙትን ነገር ወደ አፋቸውና አፍንጫቸው መስደድ የሚቀናቸው ህፃናት ለዚህ አይነቱ የነስር ምክንያት ተጋላጮች ናቸው)
– ደረቅ የአየር ንብረት
– የአፍንጫ አጥንት መሰበር

2. ኢንፌክሽንና አለርጂ
– ጉንፋን፣ ሳይናስይትና ሌሎች አፍንጫ አካባቢ ያሉትን ህዋሳት መጎብኘት የሚወዱ በሽታዎች ለነስር የማይነጥፉ ምንጮች ይሆናሉ፡፡

3. አፍንጫ ውስጥ የሚበቅሉ ዕጢዎችና ስርዓት ያጣ የአፍንጫ ቅርፅ አወቃቀር

4. አንዳንድ መድሃኒቶች
– የአፍንጫ ውስጠና አካል ውስጥ የሚቀቡ መድሃኒቶችና በአፍንጫ በመሳብ የሚወሰዱ ለምሳሌ ኮኬይን (Cocaine) የተባለውን አደንዛዥ ዕፅ እንደ አብነት መጥቀስ ይቻላል፡፡

ሀገራዊ ችግሮች (Systemic Causes)
1. የደም ግፊት መጨመር
በዚህ ዙሪያ ላይ ውዝግብ አልጠፋም፡፡ ገሚሶቹ በነስር መንስኤነቱ ሲፈርጁት የተቀሩት ደግሞ አይ መንስኤ ሳይሆን የደም ግፊት መጨመር በሚያሳዩ በሽተኞች ላይ ነስር ቢከሰት ቶሎ ለማቆም አዳጋች ነው ባዮች ናቸው፡፡ እንግዲህ ወደፊት የሚሰሩ እና በመሰራት ላይ የሚገኙ ጥናቶች ወደፊት እውነቱን ፍንትው አድርገው መግለጣቸው አይቀሬ ነው፡፡ እኛም በትዕግስት እንጠብቃቸዋለን፡፡
2. ደምን የሚያቀጥኑ መድሃኒቶች (ለምሳሌ አስፕሪን፣ ዋርፋሪን)
3. በዘር የሚተላለፍና የደም መርጋት ስርዓት የማይዋጥላቸው በሽታዎች
4. የደም ካንሰር (‹‹ውሳኔ›› የሚለው ፊልማችንን የዚህ ምሳሌ ነው)
5. ስር የሰደዱ የጉበትና የኩላሊት በሽታዎች
እንግዲህ ነስር ሲነሳ እነዚህ ችግሮችም አብረው መነሳትና መታየት አለባቸው፡፡ በሌላ አገላለፅ ‹ነስር መጣ› ብቻ ሳይሆን ለምን መጣ? ብሎ መጠየቅ ጠቢብነት ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ ግን ከሀገራዊ ችግሮች ይልቅ መንደራዊ ችግር በነስር መንስኤነት ጎልተው ይጠቀሳሉ፡፡ እዚህ ጋር አንድ ጥያቄ ሊነሳ ይገባል፡፡ ነስር የመጨረሻ ደሙ የሚወጣበት ቦታ ወይም መገለጫ ለምን አፍንጫ ሆነ? ስሙ ስለሚጣፍጥ ወይስ ከዓይን፣ ከእጅ፣ ከእግርና ከመሳሰሉት ከተቀሩት የአካል ክፍሎቻችን ይልቅ በልጦ? ነገሩ ወዲህ ነው፡-

ለምን ነስር ከአፍንጫ ሆነ
(Why always me?)

ይህ ጥያቄ ከሁለት አቅጣጫ ሊታይ ይችላል፡፡ የመጀመሪያው የደም ቧንቧዎቹ የሰፈሩበት ቦታ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የደም ቧንቧዎቹ የአወቃቀር ሁኔታ ነው፡፡
ቦታ፣ አፍንጫ ውስጥ የደም ቧንቧዎቹ የሰፈሩበትን ቦታ ስናጤነው ለአደጋ በሚያጋልጣቸው ቅርብ ቦታ ላይ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ የደም ቧንቧዎቹ ጥቃት እንዳይደርስባቸው አስበው ራሳቸውን ጠለቅ ባለ ቦታ ላይ አለመሰረቱም፡፡ ይልቁንም የአፍንጫ መግቢያ ቀዳዳ ላይ ባለውና አፍንጫን ለሁለት በሚከፍለው ቋሚ ግድግዳ ላይ እንደ መረብ ተጠላልፈውና ተሰናስለው ይገኛሉ፡፡ በህክምናው ቋንቋ ‹‹ኪስልባች ፕሌክስስ›› ወይም የኪስልባች መረብ ይባላል፡፡ በጽሑፉ መግቢያ ላያ ያያችሁት ይሄንን ነው፡፡ ታዲያ ይህ ግድግዳ ቀደም ሲል በተጠቀሱት ችግሮች ሳቢያ በቀላሉ ደርቆ መላላጥ እና መሰነጣጠቅ ሲጀምር የእነዚህም የደም ቧንቧ ህልውና ጥያቄ ምልክት ውስጥ ይገባል፡፡ ያኔ ቅሬታቸውን በነስር መልክ ይገልፁታል፡፡
አወቃቀር፡- የደም ቧንቧዎቹ አወቃቀርን ስንመለከት ደግሞ አፍንጫን አሁንም ከሌሎች ለየት የሚያደርገው አመል አላጣውም፡፡ ይኸውም ከ4-5 የሚደርሱ የደም ቧንቧዎች ተገናኝተው የተጠላለፈ መረብ የሚፈጥሩት የደም ቧንቧ አወቃቀር ስርዓት አለው፡፡ ከዚህ የተነሳ የደም ጎርፍ ፀጋ በዛላቸው ከሚባሉት የአካል ክፍሎቻችን ውስጥ አስመድቦታል፡፡ ስለዚህ ከዚህ ቦታ መድማት ሲከሰት ገኖ የመታየት ዕድሉ ከፍተኛ ነው፡፡

ነስር ሲከፈል…
ነስር ከሚነሳበት ቦታ አንፃር በሁለት ወገን መመደብ ይቻላል፡፡ የፊትና የኋላ ተብሎ፡፡ የፊት ነስር በአፍንጫችን ፊት በኩል ባለው ቀዳዳ መውጣትን ሲያዘወትር የኋላ ነስር ደግሞ በስተኋላ በኩል በመፍሰስ ወደ አፍ የመምጣት ጠባይ አለው፡፡ ከነሰረን አይቀር በፊት በኩል ቢሆን ይመረጣል፡፡ የኋላ ነስር የሚያባክነው ደም ብዙ ከመሆኑ በተጨማሪ ለማቆምም ቢሆን ቀላል የማይባል ጥረት ሊፈልግ ይችላል፡፡ ደግነቱ አብዛኛውን ጊዜ ነስር ከፊት በኩል ስለሆነ ያን ያህል ስጋት ውስጥ አይከትም፡፡

ሲነስረን ምን ብናደርግ ይሻላል?
አብዛኛውን ጊዜ ነስርን ቤት እያሉ ማስቆም ይቻላል፡፡ እንዴት ካሉ፤
– ተቀምጠውም ሆነ ቁጭ ብለው ከሽንጦት ወደፊት ዘንበል ይበሉና በአውራ ጣትና በጠቋሚ ጣትዎ የአፍንጫዎትን ጫፍ ከ5-10 ደቂቃ ያህል ጭምቅ አድርገው ይያዙ፡፡ በእነዚህ ጊዜ ውስጥ እጅዎትን ያለማቋረጥ ይጫኑ፡፡ በየመሀሉ እየለቀቁ ማየት አይመከርም፡፡ ህዝባችን የሚያደርገው ግን ተቃራኒውን ነው፡፡ ነስር ከመጣ ወደኋላ መንጋለል ወይም አንገትን ወደኋላ መላክ ደምን ወደላይ ይመልሰዋል የሚል ፈሊጥ አለን፡፡ ይህ ግን ስህተት ነው፡፡ ይልቁንም ደም ወደ ጨጓራችን በመግባት ለትውከትና አላስፈላጊ ላልሆኑ ምልክቶች ራስን ማጋለጥ ነው፡፡ ስለዚህ በስዕሉ ላይ እንደሚታየው አፍንጫዎትን ይዘው ነስሮትን ያስቁሙ፡፡
– ከዚህ በተጨማሪ ደስ ካለዎት አፍንጫዎትን ከተጫኑበት ቦታ ከፍ ብለው በረዶ ሊያኖሩበት ይችላሉ፡፡ ይህ በረዶ የደም ቧንቧዎቹን እንዲያኮማትሩና እንዲሸበሽቡ ስለሚያደርግ ነስሮትን ሊያግድ ይችላል፡፡ ነገር ግን ይህ በረዶን ማባከን ነው፡፡ ከላይ የተጠቀሰውን ዘዴ ብቻ በመተግበር ነስርን በመጣበት እግሩ ሊመልሱት ይችላሉ፡፡

ለነስር ብለው ሆስፒታላችን መቼ ይምጡ?
– የሚፈሰው ደም መጠን ከፍተኛ ከሆነና ለመቆም አሻፈረኝ የሚል ከሆነ፤
– ነስሩን ተከትሎ የእጅ መዳፍና የእግር ውስጠኛ ክፍል መንጣት፣ ድካም ወይም ራስን የማዞር ስሜት ከተሰማዎት፤
– በቅርቡ አፍንጫዎ አካባቢ ቀዶ ጥገና አድርገው ከሆነ፤
– የታወቀ የአፍንጫ ዕጢ ካለቦት፤
– ነስሩ ከዚህ ቀደም ወይም በቅርቡ ለሌሎች ተያያዥ ምልክት ካጀቡት ለምሳሌ የአጥንት ህመም፣ ትኩሳት፣ ቆዎት ላይ ወደቀይ የሚያደሉ ነጠብጣቦች ካስተዋሉ፤
– ነስሩ አደጋን ተከትሎ የመጣ ከሆነ፤
– እንደዚሁም ደምን የሚያቀጥን መድሃኒቶች የሚጠቀሙ ከሆነ ለምሳሌ አስፕሪን፣ ዋርፋሪን፣ ክሎፒዴግሮል፤
– ነስሩ በተለያየ ጊዜ እየደጋገመ የሚመጣ ከሆነ በህክምና ባለሙያ ታይቶ መሰረታዊ ችግሩ ከስር መሰረቱ ሊፈታ ይገባል፡፡

መከላከያ አለው ወይ?

– ውሃ በጨው አፍልተው አፍንጫዎትን ማጠብ፡፡ ለማዘጋጀት ከፈለጉ አንድ የሻይ ማንኪያ ጨው በአንድ ሊትር ውሃ ለሃያ ደቂቃ አፍልተው ለስ እስኪል ድረስ ያቆዩት፡፡ ከዚያ ይታጠብበት ይህ የአፍንጫዎ ህዋሳት እርጥበታቸውን እንዲጠብቁ ያደርጋል፡፡
– ከላይ የተጠቀሰውን ማድረግ ካልቻሉ ቫዝሊን መቀባት ይችላሉ፡፡
– ሲያስነጥስዎት በአፍዎ ለማስነጠስ ይሞክሩ፡፡
– አፍንጫዎት ውስጥ የሚያስቀምጡት ነገር ካለ ያስወግዱ፡፡
– ማጨስን እርግፍ አድርገው ይተዉ፡፡
– አፍንጫዎ አካባቢ አለርጂ የሚያስቸግሮት ከሆነ ሐኪምዎን ያማክሩ፡፡
– በጥቅሉ ነስር ከብዙ በጥቂቱ ይህንን ይመስላል፡፡ ምናልባትም ለአንዳንዶቻችን ነስር የሚያስጨንቀን አጀንዳ ላይሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በ4ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ለሮማ ለመንግስት ትልቅ የሆነ ቁርጠት ሆኖ ወረራ ላደረሰባት የሀን ንጉስ አትለ ግን በሠርጉ ዕለት ምሽት ነበር በነስር ምክንያት ወደ መቃብር የወረደው፡፡ ኦ ነስር ሆይ እንዲህም ታደርጋለህ እንዴ?! መጠንቀቅ ነው፡፡


በህዝበ ሙስሊሙ የመፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ የፍርድ ቤት ጉዳይ ላይ ጠ/ሚ/ሩ የሰጠት አስተያየት እና የጠበቃ ተማም አባቡልጉ መከሰስ –የዜና ትንታኔ በሳዲቅ አህመድ

$
0
0

ልዩ የዜና ትንታኔ በሳዲቅ አህመድ
በህዝበ ሙስሊሙ የመፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ የፍርድ ቤት ጉዳይ ላይ ጠ/ሚሩ የሰጠቱት አስተያየት እና የጠበቃ ተማም አባቡልጉ መከሰስ የፍትህ ስርዓቱ መበላሸቱን አመላካች ነዉ ሲሉ የህግ ባለሙያዉ ዶክተር ፍጹም አቻሜለህ ይተነትኑታል።

ጠበቃ ተማም አባቡልጉ

ጠበቃ ተማም አባቡልጉ

የማለዳ ወግ …አስገራሚው ትዕይንት “በተስፋዋ”የአረብ ምድር በሳውዲ   !

$
0
0

ነቢዩ ሲራክ
ታህሳስ 8 ቀን 2007 ዓም

* የገቡት ይወጣሉ ፣ የወጡት ተመልሰው ይመጣሉ
* የሳውዲ መንግስት “ህገ ወጦችን” የማጽዳቱ ዘመቻ ቀጥሏል
* ስፍር ቁጥር የሌላቸው ዜጎች ከሞት ጋር ተፋጠው እየተሰደዱ ነው
* የሳውዲ መንግስት ማስጠንቀቂያና እርምጃ …

unnamed (1)
  የሳውዲ መንግስት የመኖሪያ ፈቃድ የሌላቸውንና ህጉ በማይፈቅደው መንገድ የመኖሪያ ፈቃዳቸው ካለው ሙያ ውጭ የሚሰሩ የማናቸውንም ሀገር ዜጎች በመላ ሀገሪቱ ለማጽዳት የተደራጀ ዘመቻ ከተጀመረ ወር ደፍኗል። በየቀኑ በመንግስትና በግል መገናኛ ብዙሃን የሚለቀቁት የማስጠንቀቂያ መረጃዎች ከበድ ከበድ ያሉ ናቸው ።

ዛሬ ማለዳ   ” ህገ ወጦችን ጠራርገን እናስዎጣለን ” ያሉትን የሰራተኛ ሚኒስቴር አድል ፈቂን ይዞ የወጣው አረብ ኒውስ ሚኒስትሩ ሃገራቸው ለህገ ወጥ ሰራተኞች ቦታ እንደሌላት በአጽንኦት መጠቆማቸውን ያስረዳል። የሰራተኛ ሚኒስትሩ በማከልም መንግስት ህገ ወጦችን እግር በእግር እየተከታተለ በመያዝ የማስወጣቱን ስራ እንደሚገፋበት ሲያስታውቁ 150 የሚደርሱ ተጨማሪ የሴት ተቆጣጣሪዎች ስልጠና ተሰጥቷቸው ህገ ወጦችን በማጣራቱ ስራ መሰማራታቸውን አስረድተዋል። ተቆጣጣሪዎች ስራቸው ሲከውኑ በተአማኒነት  ፣ በሃላፊት ፍትሃዊ በሆነ አግባብ ባለው መንገድና ስርአት መሆን እንደሚገባው ሚኒስትር አድል ፈቂ አሳስበዋል። የሰራተኛ ሚኒስቴር አድል ፈቂ በቤት ሰራተኛ አቀጣጣጠር ዙሪያ ያለውን ችግር ለመፍታታ ከ200 የተለያዩ ሃገር ዜጎች ጋር መምከራቸውንና በጠቃሚው ምክክር የተገኙትን መፍትሄ ሃሳቦች በቅርቡ ይፋ እንደሚያደርጉ አሳስበዋል።

ዘመቻው …

unnamed (2) ወር በደፈነው በዚህ መጠነ ሰፊ ዘመቻ ኢላማዎች ፈርጀ ብዙ በሆነ ምክንያት ሳውዲ ገብተው በህገ ወጥነት የሚኖሩትን ጨምሮ በኮንትራት ቪዛ መጥተው ከአሰሪዎቻቸው የጠፉትን ያጠቃልላል። ዘመቻው ጅዳ ደርሶ በተለያዩ አካባቢዎች በየመኖሪያ ቤቱ አሰሳው ተጠናክሮ መቀጠሉን የሳውዲ መገናኛ ብዙሃን እየዘገቡት ነው ። እስካሁን በቀጠለው በዚህ ዘመቻ በኢትዮጵያን ላይ ሲያዙ ማንገላታትም ሆነ የተለየ ጥቃት መስተዋሉን አልሰማሁም። መኖሪያ ፈቃድ ያላቸው ቢያዙም እየተጣራ ተለቀዋል። ህጋዊ መኖሪያ ፈቃድ የሌላቸውና ለአሰሪያቸው የጠፉት ግን እየተያዙ ተወስደዋል። ዘመቻው ግን አሁንም ቀጥሏል … በዘመቻው የተያዙት በርካታ ዜጎችን ስልክ እየደወሉ እንደገለጹልኝ ከሆነ  ” በፍተሻው ስንያዝ የረባ ልብስ እንኳ አልለበስንም ፣ ለአመታት ያፈራነው ንብረታችን አልሰበሰብንም ፣ የኢትዮጵያ መንግስት ተወካዮች ቢያንስ ሻንጣችን ይዘን የምንገባበትን መንገድ ያዘጋጅልን  ” ሲሉ ተደጋጋሚ ምሬታቸውን ገልጸውልኛል !

ወደ ” ተስፋዋ ምድር ” ያላባራው ጉዞ …

ወደ “ተስፋዋ” የአረብ ሃገር ምድር ወደ ሳውዲ የሚደረገው ጉዞ አላቆመምም። የእኛ ደላሎች ከሳውዲ እስከ ሀገር ቤት ትላልቅ ከተሞች፣  ገጠርና የወረዳ ከተሞች በዘለቀ የእዝ ሰንሰለት ተደራጅተው በወገናቸው ስደት ተጠቃሚ ሆነዋልና በማን አለብኝነት ሰውን እያጋዙት ይገኛሉ ። አምና ካቻምናና ዘንድሮ በአሳር በመከራ ሀገር ቤት የገቡት ኢትዮጵያውያን እነሱ ” የተስፋ ምድር ” ወደ ሚሏት ሳውዲ እየጎረፉ ነው። ባሳለፍነው ወር በተደጋጋሚ የየመን የቀይ ባህር ዳርቻ የቅርብ ርቀት ባህር ከበላቸው ወገኖች ባልተናነሰ በየበርሃው በአሸጋጋሪ ደላሎች ታግተው አሳር መከራቸውን የሚያዩትን ወገኖች የከፋ የስቃይ ስደት ህይዎት ያማል ።

እነ ሞት አይፈሬዎች የእኛ ዜጎች አሳምረው የሚያውቁትን የሞት ጉዞ ተከትለው ፣ ሞትን ዳግም ለመፋጠጥ ቆርጠው ፣ ከቀያቸው ነቅለው  የመጡ ይመስላል። እነሱን በአደጋ አስከብቦ እዚህ ስላደረዳቸው ምክንያት አብዛኞችን ስንጠይቃቸው ጣራ የነካው የኑሮ ውድነት ፣  ድህነት ፣ የተሻለ ኑሮ ፍለጋውን አማረው ይነግሩናል። አንዳንዶች ከተጠቀሰው ምክንያት አዳምረው በሀገር ቤት የፖለቲካው ትኩሳት ሙቀት የመለብለቡ ፍርሃቻን እንደ ምክንያት ያቀርቡታል። ያን ሰሞን ሃገር ቤት ለእረፍት የሄዱ የቤተሰብ አባሎቸንና ወዳጆቸን ሀገር ቤት ስላለው የኑሮ ውድነትና ኑሮ ጠይቄያቸው የእድገት ምጥቀቱን ፣ ገንዘብ ላለው ሀገር ቤት የመመቸቱንና አንገቱን ደፍቶ ልስራ ላለ ስራ ሰርቶ መለወጥ እንደሚቻል አጫውተውኛል። ታዲያ ሰው ለምን ይሰደዳል?  ለሚለው ጥያቄየ ግን መልሱ ” እሱ ግራ የሚያጋባ ነው! ” የሚል ነው ። እርግጥ ነው ይህ ምላሽ አጥጋቢ ሆኖ አላገኘሁትም … የሀገር ቤቱ እውነታ እድገት ምጥቀቱ ፣ ገንዘብ ላለው ሀገር ቤት የመመቸቱንና አንገቱን ደፍቶ ልስራ ላለ ስራ ሰርቶ መለወጥ እየተቻለ አስከፊውን ስደት የማያውቁትን ቢያጓጓም ከሞት ጋር ተፋጠው ተሰደውና ወደ ሀገር ቤት በዘመቻ ተመልሰው የገቡት እንዴት የመከራ ሰቀቀኑን የአረብ ሀገር ስደት መረጡት?  ብሎ መጠየቅ ግድ ይላል ፣ ለዚህም ሁነኛ የሆነ መልስ ሰጭ አካል አልተገኘም !  ይህ ምላሽ እስኪያገኝ ግን ወደ “ተስፋዋ የአረብ ምድር ”  የሚደረገው ስደት ተጠናክሮ ቀጥሏል …
ላለፉት ሶስትና አራት ተከታታይ አመታት የሁለት ሃገራት ውል ባልተዋዋሉበት ፣ ቅድመ ዝግጅት ባልተደረገበት ሁኔታ በኮንትራት ስራ ስም ከግማሽ ሚሊዮን የሚበልጡ አብዛኛው ሴት እህቶቻችን ወደ ሳውዲ ገብተዋል። ምንም እንኳን የተሳካላቸው በተወሰነ መንገድ እራሳቸውን ረድተው ቤተሰቦቻቸውን እየረዱ መሆናቸው ባይካድም መብት ጥበቃ የጎደለባቸው ፣  ያለተሳካላቸው ከአሰሪዎቻቸው ጠፍተው ህገ ወጥ ነዋሪነቱን ተቀላቅለው የሰቀቀን ኑሮን እየገፉ ነው። በአንጻሩ በአሰሪዎቻቸው ተቀፍድደው ተይዘው መላወሻ ያጡት የተጨነቁት ምንም ማድረግ ያልቻሉት ከጨለማው ኑሮ ከእገታው ለመላቀቅ በለየለት ወንጀል ተዘፍቀው ስማችን አክፍተውታል። የቀሩት አሁን ድረስ የገሃነም ኑሮን እየኖሩ ነው። የዚህ ሁሉ ክስተት ምክንያት ህጋዊ ውል በሌለበት ፣ የመብት ጥበቃው ባልተጠናከረበት ሁኔታ የኮንትራት ስራ መጀመሩ መሆኑን ገና ኮንትራት ሊጀመር ነው ሲባል እኔም ሆንኩ ” ያገነባናል ” ያልን ባቀረብናቸው ጭብጥ መረጃዎች እንደ ዜጋ ከነ ነባሬ መፍትሄ ሃሳቡ ጥቁመ ነበር ።  ያ ሰሚ ሳያገኝ ቀርቶ እዚህ ደርሰናል። ይህ በመሆኑ ትልቅ ስህተት ተሰርቷል ባይ ነኝ።

ዛሬም ” ከስህተቱ ተምረናል ” ብለን እያቀነቀንን ፣ ግን ከስህተቱ ያለመማራችን ጠቋሚ መረጃ እየሰማን ነው ። ከአመት በፊት የተዘጋው የኮንትራት ስራ ሊከፈት “ረቂቅ ደንብ ” ወጥቷል ተብሏል። ያን ሰሞን ኤጀንሲዎች በረቂቁ ዙሪያ ሲመክሩ በዜጎች መብት ማስጠበቅ ዙሪያ ያሉት ነገር ባይሰማም ስለሚያስይዙት ገንዘብ አማረው ሲናገሩ ሰምተናል። በውይይቱ የገንዘቡ ከፍ ማለት “ህገ ወጥ ስደቱን ያባብሰዋል” ያሉት ኤጀንሲዎች ስለየትኞቹ ህገ ወጥ ስደተኞች እንደሚያወሩ ግራ እየገባን መመጻደቁን ሰምተነዋል ። ይህን ማለቴ ህገ ወጥነትን ያባብሳል ያሉት አይገባምና ነው ፣ ለመሆኑ ባህር ቆርጠው በየመን እየገቡ ያሉት አብዛኛው ወንድ ወንድሞቻችን የገጠር ልጆች የኮንትራት ስራ ቪዛው ተጠቃሚ አድርጎ መውሰዱና አግባብ ነውን?  ይህ ማስመሰያ ምክንያት ሊታረም ይገባል ።   ያም ሆኖ በኤጀንሲዎችና በደላሎች አማካኝነት በየመን ፣  በሱዳንና በዱባይ የጉብኝት ቪዛዎች ሽፋን እየተሰጣቸው አሁን ድረስ ለሚሰደዱትን መላ አልተገኘለትምና ጉዞው አላቆመም ። የኤጀንሲዎች “ህገ ወጥ ጉዞን ያበረታታል ” ለማለት የሰጡት ምክንያት እኒህኞቹን ለመታደግ ከሆነ ደግሞ እንደ ዜጋ ኤጀንሲዎች አዲሱ ረቂቅ ከገንዘብ ማስያዙ በላይ ቀድሞውንም ባላስጠበቁት መብት ላይ መነጋገር እንጅ በየጣለባቸው ግዴታ ላለማሟላት ጉንጭ አልፋ ምክክር ማድረጋቸው አያስደስትም ።

ማጠቃለያ

የኢትዮጵያ መንግስት በአረብ ሃገሩ ስደት ጉዳይ ላይ ከፕሮፖጋንዳ ያለፈ ጥልቅ ጥናት ባላደረገበት ሁኔታ የሚሰራውን ስራ ቆሞ ሊመረምር ግድ ይለዋል !

ወገኔ ሆይ  ፣ በሃገር ቤት ወደ አረብ ሃገራት ለመሰደድ የቋመጠው ወገንም ከፊት ለፊቱ ያለውን አደጋ ሊያስተውልና ሊመረምረው ይገባል !  በባህር እና በበርሃው በባዕድ ምድር ደመ ከልብ ሆኖ ከማለፍ በወገን መካከል በሃገር የመጣውን ችሎ ማለፉ ይበጃል ባይ ነኝ  !

ባለ ጊዜ ባለጸጋዎች ደላሎች ሆይ  ፣ ላንድ አፍታ ወደ ነፍሳችሁ ተመልሳችሁ በወገኖቻችሁ በተለይል ለአቅመ አዳም በደረሱና ባልደረሱ እህቶችን ላይ ቅቤ እያነጎታችሁ በማማለል እየፈጸማችሁት ያለውን ዘመን የማይሽረው  ግፍና በደል ተረጋግታችሁ አስቡት !  ጊዜው ቢያልፍም ፣ በሰራችሁት በደል ጠያቄ እንኳ ቢታጣ ውሎ አድሮ ከማይተዋችሁ የህሊና ጸጸት ለመዳን ስትሉ ከክፉው ምግባራችሁ ራሳችሁን ለመግታት ሞክሩ  ! ሌላ ምን እላለሁ  !

ቸር ያሰማን   !

Health: ብጉር መንስኤው እና መፍትሄው ምንድን ነው?

$
0
0

በተለይ ከአፍላ ወጣትነት ዕድሜ ጋር ተያይዞ ከሚከሰቱ እና የቆዳ ውበትን በመቀነስ የስነ ልቦና ጫና ከሚፈጥሩ ነገሮች መካከል አንዱ ብጉር ነው፡፡ በተለያዩ የቆዳ ህክምና መስጫዎች ሳጠና የታዘብኩት ነገር ለህክምና ከሚመጡ ሰዎች ውስጥ አብዛኛዎቹ ወጣቶች ከብጉር ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ብዙዎቹ ቆዳቸው በብጉር ምክንያት በተከሰቱ ጠባሳዎች እና መጥቆሮች ከተጎዳ በኋላ ነው፡፡ በዚህ ደረጃ ላይ ደግሞ ህክምና ያን ያህል መፍትሄ የማይሰጥ በመሆኑ አጥጋቢ መፍትሄ ሳያገኙ ይመለሳሉ፡፡ በአገራችን በአጠቃላይ በብጉር የተጠቁ ሰዎችን ቁጥር የሚያሳይ መረጃ ማግኘት ባልችልም አንድ ማህበረሰብን መሰረት ባደረገ ጥናት ከ14 እስከ 16 ዓመት 55% ወንዶች እና 45% ሴቶች በብጉር የተጠቁ ናቸው፡፡ ከአሜሪካ ህዝብ ከ40 እስከ 50 ሚሊዮን ገደማ የሚሆኑት የብጉር ሰለባ ናቸው፡፡

acne ethiopian girl

ብጉር በብዛት የሚታየው በፊት፣ ትከሻ፣ የላይኛው የደረት ክፍል እና ጀርባ ላይ ሲሆን በሁለት የዕድሜ ክልል ውስጥ በብዛት ይገኛል፡፡ የመጀመሪያው በጨቅላነት ወይም የህፃንነት ጊዜ ሲሆን በዚህ ወቅት 20% በሚሆኑት ላይ ይከሰታል፡፡ ይህም የሚከሰተው ከእናትየዋ በእርግዝና ወቅት ወደ ህፃኑ በሚተላለፍ ሆርሞን አማካኝነት ነው፡፡

ሌላኛው ወቅት ደግሞ አፍላ ወጣትነት ሲሆን አንዳንዴ ብጉር የዚህ ዕድሜ ክልል መግቢያ ማሳያ እየተደረገ ይወሰዳል፡፡ በዚህ ወቅት በወንዶች ከ16 እስከ 19 ዓመት እና በሴቶች ደግሞ ከ14 እስከ 17 ዓመት ባሉ ላይ በብዛት ይወጣል፡፡

ብጉር ከ20 እስከ 25 ዓመት የዕድሜ ክልል (90%) በሚሆኑት ሰዎች ላይ ቀስ እያለ በመቀነስ በመጨረሻ የመጥፋት አዝማሚያ የሚያሳይ ሲሆን በጥቂት ሰዎች ላይ ግን ከ25 ዓመት በኋላ በተለይም ሴቶች ላይ እስከ ሰላሳዎቹ እና ከዚያም በላይ ሊቆይ ይችላል፡፡

ብጉር እንዴት ይፈጠራል?

ብዙ ጊዜ የሚከሰተው የዘረ መል ተጋላጭነት ከእናት ወይም ከአባት ወይም ከሁለቱም ባለ ጊዜ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ሁሌም ይከሰታል ማለት ግን አይደለም፡፡ የዘረ መሉ ውርስ ሙሉ ላይሆን እና የተወሰነ ትውልድንም ሊያልፍ (Genetic Skip) ይችላል፡፡

ከዘረ መሉ ተጋላጭነት ጋር ተዳምሮ ብጉር ለመከሰት አራት መሰረታዊ ደረጃዎች አሉት፡፡ እነዚህም፡-

1. በላይኛው የፀጉር መውጫ ህዋሳት በብዛት በመራባት እና አንድ ላይ በመያያዝ የቆዳ ቀዳዳዎችን መድፈን፤

2. ቅባት መሰል ፈሳሽ የሚያመነጩ እጢዎች በብዛት መመረት፤

3. የቆዳ መቆጣት እና

4. በተፈጥሮ በቆዳ ላይ የሚገኝ ባክቴሪያ መኖር እና በብዛት መራባት ናቸው፡፡

የቆዳ ቀዳዳዎቹ በሚራቡት ህዋሳት ምክንያት በመዘጋታቸው በብዛት የተመረተው ቅባት መሰል ፈሳሽሽ ባክቴሪያ እና ሌሎችም በቆዳ ውስጥ በመከማቸት ትንንሽ እብጠቶችን ይፈጥራሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ባክቴሪያው ትራይግላይስራይድ የሚባል የቅባት አይነት ወደ ቅንጣት ነፃ አይነት ቅባቶች በመቀየር ሰውነት እነዚህ ቅባቶች ላይ ጥቃት በሚያደርስበት ጊዜ የቆዳ መቆጣትን በማስከተል የሚያሙ ብጉሮች ይፈጠራሉ፡፡ በቆዳ ውስጥ ክምችቱ ከመጠን በላይ የሚገባ ሲሆን የሰውነትን መቆጣት በማባባስ ትልልቅ እብጠቶች አንዳንዴም መግል አዘል የሚመስሉ እብጠቶችን በቆዳ ላይ ሊያስከትል ይችላል፡፡

በአጠቃላይ ብጉር ክፍት ትንንሽ እብጠቶችን (ጫፋቸው ጠቆር ያሉ)፣ ዝግ ትንንሽ እብጠቶችን (ጫፋቸው ነጭ የሆኑ)፣ ቀላ ያሉ፣ የሚያሙ እና መግል አዘል የሚመስሉ እብጠቶችን አንዳንዴም በጣም የከፋ ሲሆን ትልልቅ እብጠቶችን ሊያስከትል ይችላል፡፡ የእነዚህም ጦስ ቆዳ ላይ ቋሚ ጠባሳና ጥቁረት መከሰት ነው፡፡

ብጉርን የሚያባብሱ ነገሮች ምንድናቸው?

– ብጉርን ማፍረጥ

ይህ ሁኔታ ብዙ ሰዎች ላይ የሚስተዋል ሲሆን ይኸውም የብጉር መንስኤ የሆነውን ባክቴሪያ ከአንድ የቆዳ ቀዳዳ ወደ ሌላ በማዛመት ብጉሩ እንዲባባስ ያደርጋል፡፡ በተጨማሪም ብጉሩ በሌሎች ቆዳ ላይ በሚገኙ አደገኛ ባክቴሪያዎች እንዲመረዝ በማድረግ እና በቆዳ ላይ ጠባሳና መጥቆር በማስከተል ዘላቂ የሆነ ችግር ይፈጥራል፡፡

– ፊትን በተደጋጋሚ እና ቆዳው እስኪጎዳ ድረስ መታጠብ

– ቆዳን የሚጎዱ የቆዳ ማፅጃዎችን መጠቀም

– ቆዳን በጨርቅ መፈግፈግ

– ቅባት አዘል የሆኑ መዋቢያዎችን መጠቀም

– ፊትን በእጅ መደገፍ ወይም ስልክ ረዘም ላለ ጊዜ ፊት ላይ መያዝ

– ጭንቀት

– ቀዝቃዛ የአየር ጠባይ

– በቅድመ የወር አበባ ወቅት ብጉር 70% የሚሆኑ ሴቶች ላይ የወር አበባ ከ2 እስከ 7 ቀን ባሉ ቀኖች ውስጥ ከመምጣቱ በፊት የመባባስ ምልክት ሊኖር ይችላል፡፡ የሚቀጥለው የወር አበባ ዑደት ሲጀምር ግን ይሻሻላል፡፡

– ለተለያዩ የበሽ አይነት የምንወስዳቸው መድሃኒቶች ብጉርን ሊያባብሱም ይችላሉ፡፡ የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያህል ኮርቲኮስቴሮይድ (በብዛት ለልዩ ልዩ የቆዳ በሽታ ይሰጣል)፣ የሚጥል በሽታ መድሃኒቶች፣ ፀረ ቲቢ መድሃኒቶች በተለይም አይሶናዚድ የሚባለው በተወሰኑ በሽተኞች ላይ ብጉር ሊያስከትል ይችላል፤ ለአዕምሮ ህሙማን የሚሰጡ መድሃኒቶች ወዘተ… ናቸው፡፡

አንዳንድ ሴቶች ላይ የብጉር መኖር የተወሰኑ በሽታዎች ማሳያ ምልክት ሊሆን ይችላል፡፡ ለምሳሌ፣ አንዲት ሴት ከብጉር በተጨማሪ የወር አበባ ዑደት መዛባት፣ የወሲብ ፍላጎት መቀየር እና ባልተለመደ ቦታ ላይ ፀጉር ማብቀል ምልክት ካላት የሆርሞን መዛባት ችግር ማሳያ ሊሆን ይችላል፡፡

መፍትሄ

የብጉርን ህክምና በሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡

1. መሰረታዊ የቆዳ እንክብካቤ ማድረግ

– የቆዳ ንፅህናን በሚገባ መጠበቅ ብጉርን በመከላከል እና እንዳይባባስ በማድረግ ረገድ ወሳኝ ሚና ይጫወታል፡፡ ይህም ፊትን በቀን ሁለት ጊዜ ሞቅ ባለ ውሃ እና ቆዳ ላይ ጉዳት በማያደርስ ሳሙና በጣታችን ጫፎች መታጠብ፡፡

– ቆዳ በሚደርቅበት ወቅት ብጉር አምጪ ያልሆኑ የቆዳ ማለስለሻዎችን መጠቀም

– በቅርብ ጊዜ ከቆዳ ብጉር ጋር ተያይዞ የሚመጣ የቆዳ መጥቆርን ለመከላከል የፀሐይ መከላከያ ወይም ‹‹ሰን ስክሪን›› ቅባቶችን መጠቀም እና ከላይ የጠቀስኳቸውን ብጉርን የሚያባብሱ መንስኤዎችን ማስወገድ ናቸው፡፡

2. በመድሃኒት ማከም

የብጉር መድሃኒቶች በሐኪም የሚታዘዙ ሲሆን የመድሃኒቶቹ ምርጫ እንደየብጉሩ አይነት እና አፈጣጠር ምክንያት የተለያየ ነው፡፡ እነዚህም በቆዳ ላይ የሚደረጉ ወይም በአፍ የሚወሰዱ ሲሆን ተግባራቸውም አንዳንዶቹ የተደፈውን የቆዳ ቀዳዳ የሚከፍቱ፣ የቆዳ መቆጣትን የሚቀንሱ እና ሌሎቹ ደግሞ የፀረ ባክቴሪያ መድሃኒቶች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡

በመጨረሻም በብጉር ምክንያት በቆዳ ላይ ቋሚ የሆነ ምልክት ከመፈጠሩ በፊት ወደ ጤና ተቋማት በተለይም የቆዳ ሐኪሞች ወደሚገኙበት በመሄድ ተገቢውን የሆነ ምክር እና ህክምና ማግኘት አስፈላጊ ነው፡፡

አክራሪ … አሸባሪ … የሰለቸን መንግስታዊ መዝሙር … የፖለቲካ የበላይነት የፈጠረው አክራሪነት/አሸባሪነት የህዝቦች ስጋት ነው፡፡

$
0
0

ምንሊክ ሳልሳዊ

ሃገሪቱን የሚያሰጋት የሃይማኖት አክራሪነት/አሸባሪነት ሳይሆን የፖለቲካ የበላይነት የፈጠረው አሸባሪነት ጽንፈኝነት እና አክራሪነት ነው:: ጥላችሁን እንዳታምኑ እየተባለ ሃይማኖት መንግሥታዊ ቅርጽ ይዞ እንዲወጣ ለማድረግ መሞከር አክራሪነት ነው፡፡

Ethiopian soldiers ride on an army truck on the road to Afgooye, south of Mogadishu«መጾም፣ መጸለይ፣ ሥርዓተ-አምልኮን መፈጸም ሃይማኖታዊ አልባሳትን መልበስ ለሃይማኖቱ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እንጂ አክራሪነት ሊባል አይችልም፤»…የአክራሪ ክርስትና ወይንም እስልምና ቡድን መኖር የክርስትና እና እስልምና ተከታዮችን በሙሉ «አክራሪ» አስብሎ ሊያስፈርጃቸው አይችልም::አክራሪ ተብሎ የሚፈረጀው የሚራመዱ የፖለቲካ ጡዘቶች በሰዎች ላይ ሌላ እምነትን በመጫን በግዳጅ እና በሃይል ሊያስገድዱ ሲሞክሩ ይህ ማለት አህበሽን እና ተሃድሶን በጥንታውያኑ እስልምና እና ተዋህዶ ላይ በኢትዮጵያ እንደተሞከረው ማለት ነው::

አክራሪነት አሉታዊ ትርጉም ሲኖረው የራስን እምነትና አመለካከት በሌሎች ላይለመጫን መሞከር ነው፡፡ ሃይማኖት መንግሥታዊ ቅርጽ ይዞ እንዲወጣ ለማድረግ መሞከር ራሱ አክራሪነት ነው፡፡ አክራሪነት የፖሊቲካ ገጽታ ያለው ነው፡፡ ኾኖም ግን ሃይማኖትን ማጥበቅ አክራሪነት አይደለም፡፡ሃይማኖት ፍጹም እውነታን በፍጹም እምነት ስለሚቀበል ከሌሎች ግላዊ አስተሳሰቦች የተለየ ነው፡፡ የሃይማኖት መገለጫዎችን መጠቀም የዚያን ሃይማኖት ጥልቀት የሚያሳይ እንጂ እንደ ችግርም የሚወሰድ ወይም አክራሪነት ሊኾን አይችልም፡፡ «መጾም፣ መጸለይ፣ ሥርዓተአምልኮን መፈጸም ሃይማኖታዊ አልባሳትን መልበስ ለሃይማኖቱ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እንጂ አክራሪነት ሊባልአይችልም፤» ይላሉ የዘርፉ ምሁራን፡፡

የአክራሪነትና የአጥባቂነት ፅንሰ ሐሶቦች በጥሩ ኹኔታ ተለይተው ተገልጸዋል፡፡ አንዳንድ ሰነዶች ወያኔም ለይስሙላ የገለበጣቸው ሰነዶቹ አክራሪነትንና አጥባቂነትን በአግባቡ ለይተውና ተንትነው ያስቀምጣሉ፡፡ በዚሁ መሠረት አጥባቂነትን፣ ‹‹የግል ሃይማኖትን ሃይማኖቱ በሚያዘው መሠረት ሳይንጠባጠብ ሁሉንም ትእዛዛት መፈጸም ነው፤» በማለት ሲፈታው አክራሪነትን ደግሞ፣ «ከራስ እምነት ወጥቶ ሌላውን መተንኮስና የሌሎችን ሃይማኖት መኖር አለማመንና አለመፍቀድወይም ሌሎቹን አስገድዶ የራስ እምነት ተከታዮች ለማድረግ መጣር ነው፤» ይላል፡፡ በተግባር ላይ አለመዋሉ እና በጣልቃ ገብነት መተርጎሙ ጉዳት አመጣ እንጂ::

ከዚህ ብያኔ ስንነሣ ክርስቲያንም ሆነ ሙስሊም ከርሱ ውጭ የኾኑትን የሌሎቹን መኖር የማይቀበልና ከግለሰቦቹ ፈቃድ ውጭ አስገዳጅ እስከኾነ ድረስ እርሱን አክራሪ ማለት ይቻላል፡፡መብትን መጠየቅ ከፖለቲካ ጣልቃ ገብነት መሸሽ አክራሪነት አይደለም:: በዚህ መልኩ አክራሪው ይህንኑ ድርጊት ሊፈጽም የተነሣውን ቡድን ብቻ እንጂ «አክራሪው ቡድን» የወጣበትን/የተገኘበትን ቤተ እምነት ሊወክል አይችልም፡፡ ስለዚህ በአለማቀፍ ደረጃ የአክራሪ ክርስትና እና እስልምና ቡድን መኖር የክርስትና እና እስልምና ተከታዮችን በሙሉ «አክራሪ» አስብሎ ሊያስፈርጃቸው አይችልም፤ ለሌላው ቤተ እምነትም እንዲሁ፡፡ ሃገሪቱን የሚያሰጋት የሃይማኖት አክራሪነት ሳይሆን የፖለቲካ የበላይነት የፈጠረው አሸባሪነት ጽንፈኝነት እና አክራሪነት ነው::

#ምንሊክሳልሳዊ

በነአብርሃ ደስታ ላይ ለታህሳስ 15 ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጠ ∙ ተከሳሾቹ የክስ መቃወሚያ አቅርበዋል

$
0
0

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችን ጨምሮ 10ሩም ተከሳሾች ለታህሳስ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
Habtamu abrhayeshiwas daniel
ዛሬ ታህሳስ 9 ቀን 2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ 19ኛው ወንጀል ምድብ ችሎት የቀረቡት የሰማያዊ፣ የአንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች የሆኑት አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ እና አቶ አብርሃ ደስታ እንዲሁም አንደኛ ተከሳሽን ጨምሮ ስድስት ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካኝነት የክስ መቃወሚያቸውን ይዘው ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡

ሆኖም ግን 7ተኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን የሰጠው የተከሳሽነት ቃል ከክሱ ጋር ተያይዞ ለጠበቃው አለመቅረቡን ተከትሎ ጠበቃው የክስ መቃወሚያ ለማዘጋጀት ባለመቻላቸው የተከሳሽ ቃልን የያዘውን ዶክሜንት ከጽ/ቤት ወስደው መቃወሚያቸውን እንዲያስገቡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

በዚህም መሰረት ፍርድ ቤቱ የተከሳሾችን የክስ መቃወሚያ መርምሮ ብይን ለመስጠት ለታህሳስ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ተከሳሾች በእስር ላይ ባሉበት ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሊጎበኟቸው የሚሄዱ ቤተሰቦቻቸውና ወዳጆቻቸው ወደ እስር ቤቱ ሲገቡ በተለየ መዝገብ እንዲመዘገቡ እየተደረጉ መሆናቸውን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ተከሳሾች ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት ቤተሰቦቻቸውና ወዳጆቻቸው በተለየ መዝገብ በመመዝገባቸው ከሌላው በተለየ ማሸማቀቅ እየተፈጸመባቸው ነው፡፡

ይህን በተመለከተ ለማረሚያ ቤቱ አቤት ቢሉም ሊሻሻል አለመቻሉን ተከሳሾቹ ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ለማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም አቤቱታቸውን ተቀብሎ በቀጣይ ቀጠሮ የማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ስለጉዳዩ ቀርቦ እንዲያስረዳ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

ምርጫ የዴሞክራሲያዊ ስርአት መገለጫ ብቻ ሳይሆን የሰላማዊ ትግል ስልት አካል ጭምር ነው!

$
0
0

ተሾመ ዳባ

ምርጫ በአንባገነን መንግስት ውስጥ?
2007 electionምርጫ የዴሞክራሲያዊ ስርአት መገለጫ የሚሆነው ነጻ፣ ፍትሃዊና ተወዳዳሪ (free, fair and contested) ባህሪያትን የተላበሰ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ በኢ-ዴሞክራሲዊ መንግስት ውስጥ የሚደረጉ ምርጫዎች በምንም መመዘኛ የዴሞክራሲ ስርዓት መገለጫዎች አይሆኑም፡፡ በሀገራችን በአጼው፣ በደርግ እና በኢህአዴግ ዘመነ-መንግስታት ተደርገው የነበሩ ምርጫዎች የአጼውን፣ የደርጉንና የኢህአዴግን የአገዛዝ ስርዓቶች የስልጣን ዘመን ለማራዛም የተደረጉ (“mechanism of regime maintenance”) ምርጫዎች እንጂ አንዳቸውም የዴሞክራሲዊ ምርጫ ባህሪያትን የተላበሱ አይደሉም፡፡ በእርግጥ በባለፉት ሁለት የመንግስት ስርአቶችም ሆነ በኢህአዴግ ዘመነ-መንግስት የተደረጉ ምርጫዎች በተለያዩ የፖለቲካ አገዛዝ ስርአቶች ውስጥ እንደመደረጋቸውና በወቅቱ ካለው የሀገራችን የፖለቲካ ዕድገት አንጻር የተለያዩ ባህሪያትን የተላበሱ ነበር፡፡ ይህ ሁኔታ ግን በኢትዮጵያ ብቻ የታየ ሳይሆን በማንኛው ኢ-ዴሞክራሲያዊ መንግስት ውስጥ የሚደረጉ ምርጫዎች አጠቃላይ ገጽታ ነው፡፡

ምርጫ እንደ ሰላማዊ ትግል ስልት?

በአንባገነን ስርአት ውስጥ የሚደረጉ የነጻነት፣ የፍትህ እና የዴሞክራሲያዊ ጥያቄዎች የአንባገነን ስርአቱን ጥቅምና ፋላጎት ባስከበረ መልኩ ሊመለሱ አይችሉም፡፡ ይህ የሚወልደው ፖለቲካዊ ግጭቶችም እልባት የሚያገኙት አንድም እጅን አጣጥፎ በመቀመጥ የአምባገነን ስርአት የፍርሃት እስረኛ በመሆን (passive submission)፣ አሌያ በትጥቅ ትግል(violent)፣ ወይም ደግሞ በሰላማዊ ትግል (non-violent) ነው፡፡ ሰላማዊ ትግልን ከትጥቅ ትግል የሚለየው የጭቆና መጠን ጉልህ ወይም ቀላል የመሆን አለመሆን ፣ ወይም ደግሞ የሰብአዊና ፖለቲካዊ መብቶች ጥሰት አናሳ መሆንና ያለመሆን ሳይሆን ልዩነቱ የሚመጣው በምንክተለው የፖለቲካ ትግል ስልት ላይ ነው፡፡ የሰላማዊ የፖለቲካ ትግል አባት የሚባለው ጄን ሻርፕ፣ የሰላማዊ ትግል ትርጓሜ ሲስቀመጥ፡- “the exercise power depends on the consents of the ruled who, by withdrawing that consent, can control and even destroy the power of their opponents” ብሎ ነው፡፡ ከዚህ የምንረዳው፣ ሰላማዊ ትግል አንደኛ፣ መሰረቱ ተገዢውና ተጨቋኙ ህዝብ ነው፡፡ ሁለተኛ፣ የትግል ስልቱ ህዝቡ ለገዢዎቹ የሰጠውን ይሁንታን በማንሳት ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ሶስተኛ፣ ህዝቡ ገዢው ፓርቲ ስልጣኑን መኪያስጠብቅበት ጉልበት ያልተናነሰ ጉልበት ለገዢዎቹ በማሳየት (by means of wielding power) ገዢዎቹን መቆጣጠር፣ ከዚህም ከላፈ የመሪዎቹን ጉልበት በማፍራረስ ነጻነቱንና ዴሞክራሲያዊ መብቱን የሚያስጠብቅበት ነው፡፡

ከሰላማዊ ትግል ዘዴዎች አንዱ የፖለቲካ ትብብርን መንፈግ (the method of political noncooperation) ነው፡፡ ከዚህ ዘዴ ውስጥም፣ ተቋዋሚ ፓርቲዎች በአምባገነኑ ስርአት ውስጥ የሚደረጉ ምርጫዎች ውስጥ እራሳቸውን ማግልለ አንዱ ስልት ነው፡፡ ሆኖም ግን፣ በተደጋጋሚ እንደታየው ከምርጫ እራስን ማግለል ውጤታማ የሆነ የሰላማዊ ትግል ስልት አይደለም፡፡ ከ1990 እስከ 2009 እ.ኤ.አ ከተደረጉ 171 ከምርጫ እራስን የማግለል ማስፈራራት እና ከምርጫው እራስን በማግለል የተገኙ ውጤቶች ሲታዩ ከምርጫ እራስን ማግልለ ሳይሆን ከምርጫ እራስን አገላለው የሚል የማስፈራራት ስልት ውጤታማ እንደሆነ መረጃዎች ያመላክታከሉ፡፡ ከምርጫ እራስን የማግለል ስልት ደካማ ጎኑ በራሱ ቁሞ ውጤት የሚስገኝ ስልት አለመሆኑ ነው፡፡ በሀገራችንም በ1985 ዓ.ም እና በ2005ዓ.ም ተሞክሮ ውጤት አልባ መሆኑን አይተንዋል፡፡

በሌላ በኩል፣ ይህን ክፍተት የተረዱ የፖለቲካ ሳይንቲስቶች ምርጫን እንደ ሰላማዊ ትግል ስልት መጠቀም የሚቻልበትን ዘዴ ቀይሰዋል፡፡ ይህን ዘዴ Democratization by Elections በሚል የሰየሙት ሲሆን፣ ዋና ዋና ሃሳቡም፡-

• ምርጫዎ ለአንባገነኑ መንግስት መጨቆንን በጣም ከባድ እና መዘዘ-ብዙ እንዲሆን ያደርጋሉ፣
• ምርጫን ማካሄድ ለአንባገነኑ መንግስት ከውጭ መንግስታት ጋር ለሚያካሂደው ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥቅም መስጠቱ፣
• ዜጎች አንባገነናዊ መንግስትን ከሚታገሉበት ስልት አንዱ መብቶቻቸውን ለማስከበር የሚያደርጉት ትግል አንዱ ነው፡፡ በምርጫ መሳተፍ (እንደ መራጭም ተመራጭም) ደግሞ የዜጎች ፖለቲካዊ መብት ነው፡፡ ይህን መብት መጠይቅ፣ ለመብታቸውም መታገል፣ ድምጻቸውን በምርጫ መስጠት፣ ድምጻቸውን እንዳይሰረቅ ማስጠበቅ አንዱና ወነኛው ስልት መሆኑ፣
• በሌላ ጊዜ አምባገነኑ መንግስት የሚዘጋቸውን በሮች ለምርጫ ሲባል ብቻ የሚከፍታቸው በሮች መኖራቸው፣
• ምርጫዎች ተቋዋሚ ፓርቲዎችን በጋራ በትብብር እንዲሰሩና ወደህዝቡ እንዲቀርቡ እንድል ስለሚፈጥሩ፣ እና
• ምርጫዎች ሰብአዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ፖለቲካዊ መብቱን የሚጠይቅ ዜጋን ለመፍጠርር መነቃቂያ መድኮች በመሆናቸው (bargaining power) ነው፡፡
በመጪው ምርጫ በመሳተፍ ይህን ዘዴ ከሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር በመቃኘት ተግባራዊ ማድረግ ይቻል ይሆን?

መነሻ ሃሳብ
1. በመጪው ምርጫ መሳተፍ ማለት ምርጫው ዴሞክራሲያዊ ነው፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ዴሞክራሲያዊ ሂደት አለ ማለት አይደለም፡፡ ኢ-ዴሞክራሲያዊ ምርጫ መሆኑን ማንም የሚገነዘበው ነው፡፡ አለምአቀፉ ማህበረሰብም የሚረዳው ነው፡፡
2. ኢህአዴግ የኢትዮጵያ መንግስት ነው፡፡ ምን አይነት መንግስት ነው? ኢ-ዴሞክራሲያዊ፣ አምባገነናዊ መንግስት ነው፡፡
3. በምርጫው እራስን በማግለል ተቋዋሚ ፓርቲዎች ሊያገኟቸው የሚችሉ ውጤቶች አናሳ (እሱም ካለ) ናቸው፡፡
4. ገዢው ፓርቲ የሚከፍታቸውን በሮችና የተገኙ እድሎችን በአግባቡ መጠቀም ተገቢ ነው፡፡
5. ባለፉት 23 ዓመታት ስለገዢው መንግስት ጨቋኝነት፣ አምባገነንነት ተወርቷል፡፡ ይሄ ምንም ውጤት አላመጣም፡፡ አሁን ደግሞ የዕይታ ለውጥ ያስፈልጋል፡፡ የተቋዋሚ ፓርቲዎች ላይ ማተኮር ተገቢ ነው፡፡ ሰላማዊ ትግል መሰረቱ የአምባገነን የጨቋኝነት አቅም ላይ የተመሰረተ ሳይሆን የተጨቋኙ አቅም ላይ የተመሰረተ ነውና፡፡
6. ማንም ተቋዋሚ ፓርቲ ብቻውን በመሮጡ ሊያሳካው የሚችለው ውጤት አናሳ ነው፣ በጋራ ሊገኝ ከሚችለው ውጤት አንጻር፡፡
7. በዚህ ምርጫ ሊገኝ የሚችለው ውጤት መንግስትን መቀየር የሚያስችል ውጤት ሳይሆን፣ ሊገኝ የሚችለው ውጤት መመዘን ያለበት ዴሞክራሲያዊ ስርአት የተገነባባት፣ ፍትህ የነገሰባት፣ እኩልነት የሰፈነባት ሃገር ለመፍጠር ምን ያህል ወደፊት ያራምደናል ከሚል መሆን አለበት፡፡

ይህን ዘዴ ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችሉ ዘዴዎች
ገዢው ፓርቲ በሚከፍተው በር ሁሉ ለመጠቀም ውስጣዊ አቅም መገንባትና ዝግጁ፡- የሬዲዮ ክርክር፣ የቴሌቭዥን ክርክር፣ በህትመት ሚዲያዎች የሚሠጡ ዕድሎችን በአግባቡ በመጠቀም በግል ሚዲያ አለመኖር የሚፈጥረውን ክፈተት ማጥበብ እንዲሁም ገዢው ፓርቲ ላይ ስራ ማብዛት፣

ተቋዋሚ ፓርቲዎች ተናቦ የመስራት ዘዴ መከተል፡- ተቋማዊ ፓርቲዎቻችን በአንድነት መስራት ከብዷቸዋል፡፡ እርስ በእርስ የሚያረጉትን ትርጉም የለሽ የፖለቲካ ሽኩቻ በማስወገድ፣ ከተቻለም በምርጫው ጊዜ የእርስ በእርስ ውድድር እንዳይኖር የዕጩዎቻቸውን የመወዳደሪያ ክልል አወሳሰን ላይ በጋራ በመስራት ከገዢው ፓርቲ ጋር በአብዛኛው የምርጫ ክልሎች ላይ መወዳደር፡፡ እንዲህ በማድረግ የገዢውን ፓርቲ ጉልበት መሳሳትና መበተን ይቻላል፣ የጭቆና ወጪውም ከፍተኛ ይሆናል፣

የምርጫ ስትራተጂ፡- የተቋማዊ ፓርቲዎች የምርጫ ስትራተጂ ህዝባዊ መሰረት ለመፍጠር፣ ከዚህ ምርጫ ባሻገር የፖለቲካ መሰረት በመጣል ለቀጣይ ስራዎች ግብዓት የሚሆኑ አደረጃጀቶች መፍጠርንም ማካተት ይሆናል፡፡ የሚፈጠሩት አደረጃጀቶች ለቀጣይ ሰላማዊ ትግል መሰረት ይሆናሉ፡፡

በምርጫው ሂደት ንቁ ተሳታፊ መሆን፡- የምርጫ ታዛቢዎች ምርጫ ላይ፣ የምረጡኝ ቅስቀሳ ላይ እና በሁሉም የምርጫው ሂደት ውስጥ ንቁ ተሳታፎ ማድረግ፡፡ እንዲህ በማድረግም በተቻለ አቅም ለገዢው ፓርቲ ምርጫ ለማጭበርበር የማያመች ሁኔታ መፍጠር

ሰነዶችን የመያዝ አካሄድ፡- በምርጫው ወቅት የሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶችን፣ የምርጫ ማጭበርበርን፣ ህገወጥ የሆነ የገዢውን ፓርቲ እንቅስቃሴ የሚያሳዩ ሰነዶችና መረጃዎች በአግባቡ በማሰናዳት የምርጫዉን ኢ-ዴሞክራሲያዊነት ማሳየት ይቻላል፡፡

ሊጠበቁ የሚችሉ ውጤቶች
የአጭር ጊዜ ውጤቶች
ተቋማዊ ፓርቲዎች ያላቸውን አነስተኛ የፋይናንስ፣ የሰው ኃይል እና ድርጅታዊ አቅም በአግባቡ መጠቅም ያስችላቸዋል፡፡
በህግ ማውጫው ምክር ቤት ውስጥ በመሳተፍ አማራጭ ፖሊሲዎቻቸውንና የመፍትሄ ሃሳቦቻቸውን ለማቅረብ የሚችሉ ይሆናል፡፡ የህዝቡን ብሶት፣ የመብት ጥሰት የሚያሰሙበት መድረክ ይኖራቸዋል፡፡

የረጅም ጊዜ ውጤቶች
በጋራ አምባገነኑን መንግስት መገዳደር ይችላሉ፡፡ ከአምባገነኑ ስርአት መውደቅ በኃላ ለሚፈጠረው ስርአት ግብዓት የሚሆን በመተባበር ላይ የተመሰረተ ተቋዋሚ ፓርቲዎች ግንኙነት ይፈጠራል፡፡
ሊደርስባቸው ከሚችልው የገዢው ጭቆና በጋራ የመከላከልና የመደጋገፍ ባህል ያጎለብታሉ፡፡
ትግሉን ከዲያስፖራ ወደ ሀገር-ቤት ወዳለው ህዝብ ይመለሳል፡፡ ይህም ለተቋዋሚዎች የበለጠ የመንቀሳቀሻ እድልና የስራ ነጻነት ይሰጣቸዋል፡፡ ይህም የድል ቀኑን ያቀርበዋል፡፡ “ድል ሁል ጊዜም የህዝብ ነው” እንዲሉ አበው፡:

የባህርዳር ህዝብ አደባባይ በመውጣት ተቃውሞውን በማሰማት ላይ ነው

$
0
0

9783_596573470488802_1311708396556689267_n

ነገረ ኢትዮጵያ እንደገለጸው ዘገባ

‪#‎Update‬
የባህርዳር ህዝብ ተቃውሞውን እየተቀላቀለ ነው

ዛሬ ጠዋት ባህርዳር ከተማ ላይ የተነሳውን የህዝብ ተቃውሞ ፖሊስ በኃይል ለመበተን ጥረት እያደረ ቢሆንም ህዝቡ በብዛት ተቃውሞውን እየተቀላቀለ መሆኑን ከቦታው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

በአሁኑ ወቅት ከቀበሌ 10 አባይ ማዶ ያለው መንገድ ተቃውሞውን በተቀላቀለው ህዝብ የተዘጋ ሲሆን ወደ ጎንደር የሚወስደው መንገድም መዘጋቱ ታውቋል፡፡ የቀበሌ 8፣ 10ና 11 ነዋሪዎች እንዲሁም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ተቃውሞውን እየተቀላቀሉ ነው ተብሏል፡፡ የአፈ ጉባኤ ጽ/ቤት አካባቢም በርካታ ህዝብ የተገኘ ቢሆንም ርዕሰ መስተዳደሩን ጨምሮ ሌሎች ባለስልጣናት የሉም እንደተባሉ ገልጸውልናል፡፡

ባህርዳር ከተማ ውስጥ 04 ቀበሌ እየተባለ የሚጠራው አካባቢ የሚገኘውን የጥምቀት ታቦት ማደሪያ ለባለሀብት ይሰጣል መባሉን ተከትሎ ህዝቡ አደባባይ ወጥቶ ተቃውሞውን በማሰማት ላይ መሆኑን የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ገለጸዋል፡፡

ምንጮቹ እንደገለጹት እጅግ በርካታ ህዝብ አደባባይ የወጣ ሲሆን፣ ሰልፈኞቹ በእምነታቸው እየተደረገባቸው የሚገኙትን ጣልቃ ገብነቶችና ሌሎቹንም ስርዓቱ እየፈጠራቸው የሚገኙትን ችግሮች የሚቃወሙ መፈክሮች እያሰሙ ይገኛሉ፡፡

1937456_312016248996709_1054682142798199146_n

 


ለሚመለከተው ሁሉ! የሽዋስ አሰፋ (ከቂልንጦ እስር ቤት)

$
0
0
yeshiwas

የሽዋስ አሰፋ

በአዲስ አበባ ቂሊንጦ እስር ቤት በ3 ዞኖች ውስጥ የሚገኙ ተጠርጣሪ እስረኛ የአዕምሮ ህሙማን ወንድማችን አስቸኳይ የሆነ እርዳታ የሚሹ ስለሆነ በምትችሉት ፍጥነት መጥታችሁ እንድትጠይቋቸው በፈጣሪ ስም እለምናለሁ፡፡ የእነዚህ ወንድሞቻችን ችግር የህክምና፣ የምግብና የልብስ እንዲሁም የንፅህና ቁሳቁስ እጥረት፣ ወገን፣ ጠያቂ፣ አለኝታና ተስፋ ማጣት፣ መገለልና መገፋት፣ የሌሎች መሳቂያና መጫዎቻ መሆን ወ.ተ.ተ ስለሆነ መጀመሪያ እንደችግራቸው አይነት እንድታነጋግሯቸው ስማቸውን እንደሚከተለው ዘርዝሬዋለሁ፡፡

ዞን 1
1. አሸብር መለሰ
2. ኢሳያስ መስፍን
3. መላኩ ስለሺ
4. አማኑኤል ተክለወልድ
5. ኢብራሂም ውብሸት
6. ዮናስ ዩንኩራ
7. ሙሉጌታ መኮንን
8. ጀማል ሙስጠፋ
9. ጳውሎስ ቴወድሮስ
10. እሸቱ እና ሌሎችም አሉ
ዞን 2
1. መለሰ አለማየሁ
2. ሽፈራው ገዛኸኝ
3. አብረሃም አለበል
4. መስፍን ሽሬ
5. በርሄ ፍፁም
6. ሰይፉ ገዛኸኝ
7. ሚኪያስ ጌታቸው
8. ወንድወሰን
9. ብሩክ ተስፋዬ
10. ፍቃዱ ጥላሁን
11. ናርዶስ
12. እንዳልካቸው ታደሰ
13. ክፍሉ ሱመርጋ
14. ጅንካ ወሌ
15. ቴወድሮስ ፀጋዬ
16. አዲሱ ብርሀኑ
17. አሰፋ በየነ
18. የማነ ዘነበ

ዞን 3
1. የኑስ ሸምሱ
2. ካሳሁን ወንዱሙ
3. ታደሰ ቦጋለ
4. ሚፍታህ መሀመድ
5. ጌታሁን በለጠ
6. ሙሉጌ ፈለቀ
7. ሳሙኤል አረጋው
8. ሲሳይ እጅጋየሁ
9. እንዳልካቸው ገብሬ
10. ምናለሸዋ ፈይሳ
11. አብሉ አምዱ
12. ጥላሁን አለሙ
13. ሀብታሙ ዳምጠው
14. ጥላሁን ድጋፌ
15. ገመቹ ድሪባ
16. አብዱለሀብ ምደታ
17. በየነ አጋ
18. ዮናስ ተስፋዬ
19. አበበ ወ/ሀዋሪያት
20. አሽረቃ ሙደርሲር
21. መለስ ገዛኸኝ
22. ሀይለ ሚካኤል ገ/ማርያም
23. ሙሴ ሀይሌ

ተደራጅ 2007 ለለውጥ‬ (Andnet’s Youths – UDJ)

$
0
0

ለለዉጥ ተደራጅ ሲባል!!!!

ለለዉጥ ተደራጅ ሲባል በዋነኝነት በአንድነት ፓርቲ ዉስጥ ታቀፍ፤የፓርቲ ሃላፊነት ወስደህ ለዚህ ክቡር ህዝብ፤ ለዚህች ጥንታዊትና ነጻ ሀገር ዘላቂ አንድነት፤ሰላምና እድገት ባለህ አቅም ሁሉ ተረባረብ ማለት ነዉ፡፡ተደራጅ ሲባል የፓርቲዎች ዉህደትና ትብበረንም ያጠቃልላል፡፡ ተደራጅ ሲባል በአገር ዉስጥና በዉጪ ሃገር ለሰላማዊ የስርአት ለዉጥ የሚሰሩ ሙሁራንና ወገኖች ጋርም አብረን እንስራ ማለት ነዉ፡፡ተደራጅ ሲባል የመብት ጥያቄ አንስተህ በዚህ ስርአት ያለተመለሰልህ ጥያቄዉን ወደ ፖለቲካ ቀይረዉና አብርን ፍትሃዊ ስራት እንመስርት ማለት ነዉ፡፡

ተደራጅ ሲባል በኢህኣዴግ የተበሉ ተበሉብህን ተቋማት ለማስመለስ ሰላማዊ ትግሉን ደግፍ ማለት ነዉ፡፡ተደራጅ ሲባል አግርና ህዝብ የምታከበሩና ቅድሚያ ለወገናችሁ የምታሰቡ ግን አፋኙ ፓርቲያችሁ አቅመ ቢሰ ያደረጋችሁ የአህኣዴግ አባላት ዉስጡን በመብላት መቅን አልባ አድርጉት ማለት ነዉ፡፡ተደራጅ ሲባል በመረጥከዉና በሚስማማህ ፓርቲ ታቅፈህ ለአብሮነትና ለሰላማዊዉ የስርአት ለዉጥ ታገል ማለት ነዉ፡፡ተደራጅ ሲባል አንድነትን እናጥነክርና ለህዝባችን መተማመንን እንፍጠር ማለት ሲሁን የተደራጀ፤የነቃና መተማመንን የፈጠረ ህዝብ የአፋኝን መንግስት ስርአት ለመለወጥ ቀናት ሲበቁት በአላም ላይ በቂ ተሞክሮ አይተናል፡፡

ጥሪያችን ኑ አብርን እንስራ ነዉ፡፡ለለዉጥ ተደራጅ!!!!

Andnet’s Youths – UDJ


UDJ Youth

እስማኤል አሊ ስሮ ለረዥም ጊዜ በክልል ፕረዝድንትነት የቆዩ ብቸኛ የኢህአዴግ አገልጋይ የሆኑበት ምክንያት ምንድነው ?

$
0
0

አኩ ኢብን ከአፋር

የቀድሞው የትግራይ ክልል ፕረዝደንት የነበሩት አቶ ገብሩ አስራት በ 2006 ዓ.ም በጻፉት ሉዓላዊነትና ዲሞክራሲ በኢትዮጲያ በተሰኘው መጽሀፍ ላይ ሰለ እስማእል ዓሊ ሲሮ ሲገልፁ እንዲህ ይላሉ….

(አፋር ክልልን ፍልሥሥ ብሎ የሚመራው ኢስማኤል አሊስሮ ይህ ነው)

(አፋር ክልልን ፍልሥሥ ብሎ የሚመራው ኢስማኤል አሊስሮ ይህ ነው)


በ1993 በኢህአዴግ ውስጥ ቀውስ በተፈጠረበት ወቅት የአፋር ብሔራዊ ዴሞራሲ ፓርቲ ሊቀመንበርና የክልሉ ፕረዝድነት የነበሩ ዓሊ ሲሮ አፈንጋጮችን ደግፎ ለተወሰኑ ቀናት የመለስን ቡዱን ተቃውሞ ነበር።

መለስ ድል አድረግያለሁ የባለንጣዎች ጃኬትም አውልቀያለሁ ካለ በኃላም ዓሊ ሲሮ ደስተኛ አልነበረም።
ሰለሆነም ከክፊፊሉ በኃላ ዓሊ ሲሮ መገምገም ነበረበት ከመገምገምም አልፎ ላሳየው ተቃውሞ መቆንጠጥ ነበረበትና በወቅቱ የፈዴራል ሚኒስትር የነበረው አባይ ፀሐዬና የክልሎች ዴስክ ኃላፊ የነበረው ዘርኣይ አሰገዶም የአፋር ዴሞክራሲ ፓርቲን አመራር ዓሊ ሰሮን ጠርተው ቁም ስቅሉን አሳይተውት ነበር።

ዓሊ ሲሮም ከአፈንጋጮች ጎን ተሰልፈው እንደነበረ እንዲያምን ብዙ አስለፍልፈውታል።
ሁለት አወያዮች ይህን ካደረጉ በኃላ ዓሊ ሲሮ ከስልጣን እንዲወርድ ለመለስ ሀሳብ ቢያቀርቡም አለቃ ፀጋይ በአቆራጭ መለስን ተማጽኖ ከመባረር አድኖታል።

የአለቃ ፀጋይ ዓሊ ሲሮ በስልጣን እንድቆይ መማጸን ከማናውቀው ማላእክ የሚናውቀው ሰይጧን (ሸይጣን) ይሻለናል ከሚል እንደነበረ ምንጮቻችን ነግሮናል።

እውነትም ሁኔታዎች በተለዋወጡበት ሁኔታ እንኳን አብዴፓና መሪው ሌላም አፋር ለውጥ ለማምጣት የሚቸገር ነበረና ዓሊ ሲሮ ባለበት እንድቆይ ተወስኖ ኢህአዴግን ከአስራ ሁለት አመታት በላይ ሊያገለግል ችሏል ይላል መጽሀፉ።

እዚህ ለይ እኔም የራሴ ትንሽ ልጨምረበትና በእርግጥ የእስማእል ዓሊ ሲሮ የአገልግሎት ላይ መቆየት ምክንያት አለቃ ፀጋይ ነው።
ይህም በ1993 ባደረገለት ተማጽኖ ብቻ ሳይሆን መለስ ከሞተ በኃላም ያልተቆረጠ ድጋፍ ከአለቃ ፀጋይ አላቸው።
ይሁን እንጂ መለስ ከሞተ በኃላ አለቃ ፀጋይ እራሱ ይህ የሚባል ስልጣን ባይኖረውም አቆያህለሁ እያለ ከአቶ እስማእል ብዙ ሚሊዮን ብሮች እንደሚያገኝ ይነገራል።

አለቃ ፀጋይ የትግራይ ክልል ፕረዝደንት በነበሩበት ጊዜ ዓሊ ሲሮ መቀለ ሳይዘይሩ (ሳይሳለሙ) ሳምንት አያሳልፉም ነበር።
አሁን ግን ሁለቱም መሀይሞች የሚገናኙት አዲስ አባባ ወይም ሰመራ ቢሆንም አቶ ሲሮ ስልጣን ላይ ለመቆየት ከአለቃ ፀጋይ ሌላ አዲስ ሽማግሌ የቀጠሩ የመስላሉ።

እርሱም የጀቡት ፕረዝደንት የሆኑት እስማእል ኡማር ገሌ ስሆኑ ካለፉት ሦስት ሳምንታት በፊት አቶ እስማእል አሊ ስሮ በማያገባቸው የሁለት አገር ድምበር ከተሞች የፀጥታ ኃላፊዎች በተጠሩበት ሰብሰባ ምክንያት በማድረግ ወደ ጀቡቲ ሄደው ነበር።
በዛን ጊዜ ሁለት እሰማእሎች ተገናኝተው የበሩ መሆኑን ኦና ኢህአዴግ ከእስማእል ኡመር ገሌ የሚፈለገው ብዙ ነገሮች ሰላለው ኢህአዴግን እንዲማጸኑለት እስማእል ዓሊ ሲሮ ጠይቀው ነበር።

ያነ የኢትዮጲያ ኢሳ ጎሳ ተወላጅ የሆኑት ገሌ እስማኤል ዓሊ ሲሮ ለኢሳዎች ልዩ ቀበለዎች እንዲሰጡ ወይም የኢሳ ጎሳ በአፋር ክልል በሰላም እንዲኖሩ እንዲያመቻቹ ጠይቀው አቶ ሲሮ የሁለቱም ጥያቀዎች መልስ ያለው በኢህአዴግ እጅ ውስጥ እንደሆነና እርሰዎ እንድጠይቁ በማለት በሚስጥር ከተሰማሙ በኃላ ወደ ሰመራ ተመልሷል።

ከሳምንት በኃላ የጀቡቲ ፕረዝደንት በአሶሳ በተከበረው የበሔር በሔረሰቦች ቀን ላይ ተግኝተው ወደ አገራቸው ተመልሰዋል።
ከዛም ከሳምንት በኃላ የፈደራል ሚኒረስትር በአፋር ክልል በአዋሽ ከተማ በሁለት ክልሎች ጣልቃ ገብተው የአፋር መሬት ለኢሳ አሳልፈው ስጥተዋል።

በአዲስ አበባ በኑር (በኒ) መስጅድ ህዝበ ሙስሊሙ ድንገተኛ ተቃውሞ አደረገ

$
0
0

bbn
(ዘ-ሐበሻ) በአዲስ አበባ በኑር (በኒ) መስጅድ ህዝበ ሙስሊሙ ድንገተኛ ተቃውሞ በማድረግ አስገራሚ ተቃውሞውን ገለጸ::

ድንገት በተደረገው በዚህ ተቃውሞ ላይ የተለያዩ መፈክሮችን የያዙ ፊኛዎች ወደ ተውለብለበዋል ያሉት ዘገባዎች ፊኛዎቹ የተለያዩ መፈክሮች የተጻፈባቸው ሲሆን ከነዚህም መካከል : -” ትግሉ ይቀጥላል ፍትህ ነጥፏል ፤ሂጃብ መለያችን፤ኒቃብ ውበታችን ፤ትግላችን ቀጥሏል ፍትህን ማዘግየት ፍትህን መንፈግ ነው ፤ትግላችን እንደቀጠለ ነው” የሚሉ እንደሚገኙበት ዘግበዋል;;

በተጨማሪም “ፍትህ ፍትህ ፍትህ ;We Need Justice ፤Hijab Is Beauty ፤ justice Is Denied የሚሉት መፈክሮች ይገኙበታል፡፡” ያሉት ዘገባዎቹ በርካታ ፊኛዎች የተውለበለቡና ወደ ሰማይ የተለቀቁ ሲሆን ተቃውሞው በከፍተኛ ድምቀት ተከናውኗል ሲሉ ገልጸዋል::

የዛሬው የበኑር መስጅድ ተቃውሚ መንግስት በሴኩላሪዝም ሽፋን እየፈጸመ ያለውን የሂጃብ ገፈፋ የሚያወግዝ ሲሆን በተጨማሪም በህዝበ ሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች ላይ እጸፈጸመ ያለውን የፍትህ መዛባት ፤ በማረሚያ ቤቱ የሚፈጸሙ ግፎችን ለማውገዝ ነው የሚሉት አስተባባሪዎቹ መንግስት ሙሉ በሙሉ ተቋሞውን በሃይል አስቁሚያለሁ ሲል የነበረ ሲሆን ህዝበ ሙስሊሙ ግን ድንገተኛ ተቃውሞ በማድረግ አስገራሚ ተቃውሞውን ገልጹዋል፡፡

ስለዛሬው ስልፍ ቢቢኤን በሰበር ዜናው ያስደመጠውን ያድምጡ

ዛሬ በኑር መስጅድ ከፍተኛ የተካሄደውን ተቃውሞ በምስል ይመልከቱ

$
0
0

 

http://youtu.be/370C_Jyh0BE

በአሁኑ ጊዜ በኑር መስጅድ ከፍተኛ ተቃውሞ ተቃውሞ ተካሄደ ፡፡  የተለያዩ መፈክሮችን የያዙ ፊኛዎች ወደ ተውለብለበዋል
ፊኛዎቹ የተለያዩ መፈክሮች የተጻፈባቸው ሲሆን ከነዚህም መካከል
ትግሉ ይቀጥላል ፍትህ ነጥፏል ፤ሂጃብ መለያችን፤ኒቃብ ውበታችን ፤ትግላችን ቀጥሏል
ፍትህን ማዘግየት ፍትህን መንፈግ ነው ፤ትግላችን እንደቀጠለ ነው

Viewing all 15006 articles
Browse latest View live